Tuesday, October 23, 2012

ከኦሮሞ ህዝብ ጀርባ...


(ከተመስገን ደሳለኝ)
እንደ መግቢያ
1975 ዓ.ም.፡፡ በመሀል ሀገር የነበረው የፖለቲካ ግለት ከብዙ ደም መፋሰስ በኋላ ወደ ጠረፍ እና የገጠር
ከተሞች አፈገፈገ፡፡ በ‹‹ምርጥ መኮንኖች›› የተመሰረተው መንግስትም አንፃራዊ ሰላም ያገኘ መሰለ፡፡ አስቀድሞ
‹‹ወታደራዊ ክንፍ›› አቋቁሞ የነበረው የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ፓርቲ (ኢህአፓ) በሀገሪቱ ዋና ዋና
ከተሞች ለማቀጣጠል ሞክሮት የነበረው አብዮት ከፍተኛ ዋጋ አስከፍሎት ከሸፈ፡፡ ለክፉ ቀን ‹‹አማራጬ››
ያለው ወታደራዊ ክንፉም ቢሆን ለሶስት በመከፈሉ በእጅጉ ተዳከመ (ትግል በቃን ብለው ወደ ምዕራብ ሀገራት
ለመሰደድ በወሰኑ፣ ኢህአፓን ይዘን እስከመጨረሻው እንፋለማለን ባሉና ‹‹ኢህአፓ ዴሞክራት አይደለም››
በሚል ተገንጥለው ‹‹ኢህዴን›› የተባለ አዲስ ድርጅት በመሰረቱ) ከዚህ በተቃራኒው በመገንጠል እና በብሄር
ጥያቄ ዙሪያ የተሰባሰቡት ሻዕቢያ፣ ህወሓት እና በሽብርተኝነት የተፈረጀው ኦነግ የተሻለ ድርጅታዊ አቅም
መፍጠር ቻሉ፡፡
…በሁለት ወጣት ታጋዮች የሚመራ ከህወሓት የጦር ሰፈር (ደደቢት) የተነሳ አንድ ልኡክ ከኢትዮጵያ መንግስት የመረጃ ሰራተኞች እና
የገጠር ካድሬዎች አይን ተሸሽጎ በከፍተኛ ጥንቃቄ ጉዞ ጀምሯል፡፡ መድረሻ ነጥቡ ‹‹ደባዜን›› የተሰኘች ከተማ ነች፡፡ ልኡኩ ከብዙ ቀናት
በኋላ የኦሮሚያ ገጠር ከተማ በሆነችው ደባዜን ደረሰ፡፡ በወቅቱ ደባዜን የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር /ኦነግ/ ወታደራዊ ቤዝ ስትሆን ትግረኛ
ተናጋሪ ታጋዮቹ ወደ አካባቢው የመጡት በድርጅታቸው ህወሓት እና ኦነግ መካከል በተፈረመ ስምምነት መሰረት ነው፤ የስምምነቱ ይዘት
‹‹የህወሓት ታጋዮች ለኦነግ ታጋዮች ወታደራዊ ስልጠና እንዲሰጡ፣ ካድሬዎችን እንዲያነቁ እና ሁለቱ ድርጅቶች በትጥቅ ትግሉም ሆነ
ከትጥቅ ትግሉ በኋላ በጋራ እንዲሰሩ›› የሚል ነው፡፡ ሆኖም በሁለት የህወሓት አመራር አባል የተመራው ልዑክ ደባዜን ከደረሰ በኋላ
ከኦነግ የጠበቀው አቀባበል የስምምነቱ ተቃራኒ ሆነ፡፡
ኦነግ በግልፅ ከህወሓት የተላኩትን ‹‹መርሲነሪዎች›› (ቅጥረኛ ነፍሰ ገዳዮች) ሲል አውግዞ ከወታደራዊ ሰፈሩ በፍጥነት እንዲወጡ አደረገ፡
፡ በሁለቱ የአመራር አባላት የተመራው ቡድንም ወደ ትግራይ ተመለሰ፡፡ የቡድኑ መሪዎችም መላው የህወሓት የአመራር አባላት
በተገኙበት ሪፖርታቻውን አቀረቡ፡፡ ሁለቱ የአመራር አባላት ክንፈ ገ/መድህን እና ሙሉጌታ ጫልቱ ነበሩ፡፡ ከዚህ ሪፖርት በኋላም
ህወሓት ከኦነግ ጋር ለመስራት የነበረው ተስፋ መከነ፡፡
የኦሮሞን ድርጅት ፍለጋ
ህወሓት ከኦነግ ጋር መስራት (በርሱ መጠቀም) እንደማይችል ከተረዳ በኋላ ‹‹ኦሮሞን የሚወክል ‹አሻንጉሊት› ድርጅት መመስረት››
የሚል ድምዳሜ ላይ ደረሰ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የትጥቅ ትግሉ እየተስፋፋ በመሄዱ ከትግራይ አልፎ ወደሌሎች የሀገሪቱ ከተሞችም ይሳብ
ዘንድ የግድ ኦሮምኛ ተናጋሪ ድርጅት በማስፈለጉ ነው፤ እናም የኦሮሞ ተወላጆች የሆኑ ታጋዮችን ያስሱ ጀመር፡፡ በአሰሳውም የደርግ
ወታደር ሆነው በተሰለፉበት ግንባር በሻዕቢያ ተማርከው በኋላ ለኢህዴን የተሰጡ ጥቂት ኦሮሞዎች ተገኙ፡፡ እነዚህን ኦሮሞዎች በወቅቱ
ከሻዕቢያ የምርኮኛ ማጎሪያ ያመጧቸው የኢህዴን የወቅቱ ሊቀመንበር ያሬድ ጥበቡ ሁኔታውን ለዚህ ፅሁፍ ሲገልፁ ‹‹እ.አ.አ. በ1983
ዓ.ም ትህሳስ ወር ወደኤርትራ ከታደሰ ጥንቅሹ ጋር ሄድን፤ በጊዜው ‹የኤርትራ ህዝብ ነፃ አውጭ ግንባር /ሻዕቢያ/› ሊቀመንበር የነበረውን
ሮመዳን መሀመድ ኑርን አገኘሁትና የጦር ምርኮኞችን መጎብኘት እንደምፈልግ ጠይቄው ተፈቀደልኝ፡፡ በወቅቱ ወደዘጠኝ ሺህ ምርኮኞች
በእጃቸው ላይ ነበሩ፡፡ መንገድና ድልድይ ያሰሯቸው ነበር፡፡ እኔም ለእነዚህ ምርኮኞች ስለኢህዴን ማብራሪያ ሰጠኋቸው፡፡ አብዛኛዎቹም
ትግሉን ለመቀላቀል በጣም እንደሚፈልጉ ነገሩኝ፡፡ እንደገና ተመልሼ ሮመዳንን አገኘሁትና ከምረኮኞቹ ውስጥ ከእኛ ጋር መታገል
የሚፈልጉትን ይዤ ለመሄድ እንደምፈልግ አስረዳሁት… ህዝባዊ ግንባር በሃሳቡ ተስማምቶ ይዣቸው ለምሄደው 300 ምርኮኞች፣ 300
ክላሽንኮቭ መሳሪያ፣ ጥቂት PRC77 የረጅም ርቀት መገናኛ ራዲዮ እና ከ100 ሺህ በላይ ጥይቶችን እንደሚሰጠን ነገረን፤…በዚህ ሁኔታ
ነበር የኦህዴድ መስራቾች ኢህዴንን የተቀላቀሉት፤ በደንብ የሰለጠኑ ወታደሮች ነበሩ፣ ልዩ ችሎታም ያላቸው ነበሩበት፤ ጄነራል ባጫ ደበሌ
ጎበዝ ጊታርና ኪቦርድ ከመጫወቱም በላይ የኦሮምኛ ዘፈን ይዘፍንልን ነበር፤ ከመሀላቸው በሻዕቢያ ዕስር ቤት ሳሉ ፉርኖ ዳቦ መጋገር
የለመዱ ነበሩና ለእኛም ይጋግሩልን ነበር›› በዚህ ቀመር መሰረት በ1982 ዓ.ም. በኢህዴን/ኢህአዴግ ውስጥ ሆነው በትግል ሜዳ የነበሩ
የኦሮሞ ተወላጆች ተሰባስበው እንዲደራጁ ተደረገና ‹‹የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ኦህዴድ/›› ተመሰረተ፡፡ ኩማ ደመቅሳ፣
አባዱላ ገመዳ፣ ባጫ ደበሌ፣ ዮናታን ዲቢሳ፣ ዲሪባ ሀረቆ…
…ኦህዴድ ዘንድሮ በወረሃ መጋቢት ሃያ ሶስተኛ ዓመት የምስረታ በአሉን ያከብራል፡፡ በድህረ-መለስ ዜናዊ የፖለቲካው ርዕሰ ጉዳይ ከሆኑት
መሀከልም አንዱ መሆን ችሏል፡፡ ኦህዴድ ለሶስት ተከፈለ (በአባዱላ ገመዳ፣ በኩማ ደመቅሳ እና በጁነዲን ሳዶ የቡድን አባትነት) ከሚለው
ተመስገን ደሳለኝአንስቶ የኦህዴድ አመራር ‹‹የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቦታ ለእኛ ነው የሚገባን›› በሚል በኢህአዴግ ውስጥ ልዩነት ፈጠሩ እስከሚለው ወሬ
ድረስ እየተሰማ ነው፡፡ ሁናቴውን ይበልጥ ያከረረው ደግሞ ባለፈው ሳምንት በአሜሪካ ድምፅ የኦሮምኛ ፕሮግራም ላይ ድምፃቸውን
ቀይረው ቀርበው የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ነኝ ያሉት ግለሰብ ‹‹የጠቅላይ ሚንስትሩ ቦታ ለእኛ ነው የሚገባው›› ማለታቸው ነው፡
፡ ወሬው እውነት ከሆነ ወይም ንግርቱ ከሰመረ በቅርቡ ‹‹ሶስተኛውን አብዮት›› የማየት አጋጣሚ ሊኖር ይችላል፡፡ ምክንያቱም ይህ
አይነቱ የፖለቲካ ጥያቄ ለኦህዴድ አዲስና ያልተለመደ ነው፡፡ ኦህዴድ የተመሰረተው የራሳቸውን የፖለቲካ አጀንዳ ባነገቡ ታጋዮች
ካለመሆኑም በላይ ያለፉትን ሃያ አንድ የስልጣን አመት የራሱ የሆነ የፖለቲካ ቁመና ለመያዝ አልታደለም፡፡ በእርግጥ የኦህዴድ ችግር ይህ
ብቻ አይደለም፤ ከኦነግ ጋር በተያያዘ ብዙ ሺ የኦሮሞ ተወላጆች ወደእስር ቤት ሲላኩና እንደወጡ ሲቀሩ ‹‹በህግ አምላክ›› ብሎ
ከመቃወም ይልቅ መንገድ መሪና ዋነኛ ተዋናይ መሆኑ ነው፡፡ ጳውሎስ ሚልኪያስ የተባሉ የፖለቲካ ተንታኝ በአንድ ጥናታቸው ኦህዴድ
የተመሰረተበትን ምክንያት የገለፁት “The TPLF leadership to utilized it as a Trojan horse” (የህወሓት አመራር እንደ ትሮይ
ፈረስ ሊጠቀምበት ፈልጎ ነው) በማለት ነው፡፡
ይህንን ሁኔታ ይበልጥ የሚያጠናክረው ኦህዴድ በነቢብ ያነሳቸው (እንዲያነሳቸው የተደረገው) ጥያቄዎች ከመገንጠል በቀር በሙሉ ኦነግ
አስቀድሞ ያነሳቸውና የኦሮሞ ተወላጆችን ልብ ማማለል የቻለባቸው ብቻ ተመርጠው መሆናቸው ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ የድርጅቱ ባንዲራ
ሳይቀር ከኦነግ ጋር እንዲመሳሰል ተደርጓል፡፡ ዛሬ ኦህዴድ የሚያስተዳድረው የኦሮሚያ ክልል መጠሪያ ቃል ስረወ ግንዱ ራሱ ኦነግ ነው፤
ምክንያቱም ‹‹ኦሮሚያ›› የሚለው ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ በስራ ላይ የዋላው ኦነግ እ.እ.አ በ1974 ዓ.ም በህቡዕ በበተነው ‹‹The voice
under tyranny››  በሚለው ፅሁፍ ላይ ከተጠቀመበት በኋላ ነውና፡፡ የቁቤ ክርክርንም በማራመድ የሚታወቀው ኦነግ ነበር (ጀማሪው
ሀይሌ ፊዳ ቢሆንም ቅሉ)፤ እነዚህ ‹‹በጎበዝ ተማሪ›› ተሰርተው ለኦህዴድ የተሰጡ የቤት ስራዎች የመጀመሪያና የመጨረሻ ግባቸው ከድል
በኋላ ‹‹ኦነግን ከኦሮሚያ ክልል ማስወጣት›› የሚለውን የህወሓትን ያደረ አላማ ማሳካት ብቻ በመሆኑ ግባቸውን ከመቱ በኋላ ጥያቄዎቹ
በኢህአዴግ መዝገብ ቤት በሰላም ያርፉ ዘንድ ተደርገዋል፡፡ ኦህዴድም ቢሆን ሲጀመርም ከእነዚህ ጥያቄዎች ጋር ዝምድና ስለሌለው
‹‹ከወዴት ደረሱ?›› ብሎ የጠየቀበትና ያፈላለገበት ሁኔታ የለም፡፡ ለዚህም መሰለኝ መለስ በ1986 ዓ.ም የኦህዴድ ድርጅታዊ ጉባኤ ላይ
‹‹ከኦሮሞ ጋር ለመገናኘት ህልም ነበረን፡፡ ተሳክቶልናል በቁጥር አነስተኞች ነበሩ፡፡ የትግል ልምድ አልነበራቸውም፤ የኃይል ምንጩ
መሳሪያ ወይም ቁጥር አልነበረም፡፡ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ መስመር ነው›› ሲሉ እውነታውን በገደምዳሜ የነገሩን፡፡
የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ምንድር ነው?
የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄን በሁለት ከፍለን ልናየው እንችላለን፡፡ ፖለቲከኞቹ የሚያነሱት እና ብዙሃኑ የብሄሩ አባላት የሚያነሳው ብለን፡፡
የመጀመሪያውና በአብዛኛው አደገኛ ጎኑ የሚያመዘነው የኦሮሞ ‹‹የብሄር ፖለቲከኞች›› (Ethnic-nationalist elites) የሚያነሱት ነው፡
፡ በዚህ ማእቀፍ ውስጥ የሚመደቡት የጥያቄያቸው መቼት ከአፄ ምንሊክ ‹‹የግዛት ማስፋፋት ዘመቻ›› ጋር የሚተሳሰር ሲሆን፣ የእነዚህ
ሊሂቃኖች ጥያቄ ብዙውን ጊዜ ‹‹ከጭቆና እና ከወረራ›› ጋር ተያይዞ ሲጎን ይታያል፡፡ እንደመጨረሻ መፍትሄ የሚያስቀምጡትም ‹‹ነፃ
የኦሮሚያ ሪፐብሊክን›› መመስረት የሚል ነው፡፡ (በእርግጥ በቅርቡ የዳውድ ኢብሳ ኦነግ ‹‹የኦሮሚያ ህዝብ ይወስን›› ሲል፣ የከማል ገልቹ
ኦነግ ደግሞ ‹‹መገንጠል የለብንም›› በሚል አቋማቸውን እንዳሻሻሉት ተናግረዋል)
በሁለተኛው መደብ የሚካተቱት ብዙሃኑ የብሄሩ አባላት ናቸው፡፡ የጥያቄያቸው ማዕቀፍም የኦሮሞ ባህሎች ተደፈጠጡ፣ በቋንቋችን
መማር መቻል አለብን፣ በሀገሪቱ ፖለቲካ የቁመታችንን ያህል እንወከል፣ ፌደራሊዝም ያለጣልቃ ገብነት ይተግበር እና የመሳሰሉት የሚሉ
ናቸው፡፡ (ይህ ክርክር መገንጠልን እንደአማራጭ አያስቀምጥም) እንግዲህ የኦሮሞ ህዝብን እንወክላለን በሚል የተመሰረቱ ድርጅቶች
በሙሉ ‹‹የሚሸጥ ሃሳብ›› የሚያዘጋጁት ከእነዚህ ጥያቄዎችና ፍላጎቶች አንፃር ነው፡፡ ሆኖም በብሄሩ ስም ከተመሰረቱ በርከታ ድርጅቶች
መካከል ጥያቄዎቹን ለመመለስ በህወሓት/ብአዴን ድጋፍና እርዳታ ስልጣን በመያዝ በለስ የቀናው ኦህዴድ ቢሆንም በውስጣዊና
ውጫዊ ድክመቶቹ የተነሳ ለጥያቄዎቹ መልስ ሊሰጥ ቀርቶ በግልባጩ በኦሮሚያ ላይ የስጋት ምንጭ በመሆኑ የኦሮሞን ብሄርተኝነት
መምቻ ‹‹ዱላ›› ሆኗል፡፡
  የኦህዴድ ውስጣዊ ተግዳሮቶች
ኦህዴድ ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን እንደድርጅት ተመስርቶ ለስልጣን ከበቃ በኋላ ራሱን የሚያጠናክርበት ወይም ከህወሓት ተፅእኖ ነፃ
የሚወጣበት በርካታ አጋጣሚዎች ቢፈጠሩም ለመጠቀም አልቻለም፡፡ ለዚህ ክሽፈትም ጥቂት ምክንያቶችን ማንሳት ይቻላል፡፡
ምክንያት አንድ
ኦህዴድ የተመሰረተው በኢህዴን ውስጥ ተራ ታጋይ በነበሩ (ምርኮኛ ወታደሮች) በመሆኑ ለስልጣን ከበቃ በኋላ በነበረው የበታችነት
ስሜት የኦሮሞ ልሂቃኖችን ወደ ድርጅቱ እንዳይገቡ አግዶ መያዙ ነው፡፡ ከዚህ በተቃራኒው የስልጣን ሸሪኮቹ ህወሓት እና ብአዴን
(ኢህዴን) ለቀድሞ መንግስት ያገለግሉ ከነበሩ ምሁራን ውስጥ የየብሔራቸውን ተወላጆች ወደ ድርጅታቸው ሲቀላቅሉ ኦህዴድ ከዚህ
ትምህርት ወስዶ ፈለጋቸውን ከመከተል ይልቅ ‹‹ኢሠፓ፣ ኦነግ፣ ኢህአፓ…›› እያለ በማውገዝ በርካታ የኦሮሞ ምሁራኖችን ከፖለቲካውእንዲገለሉ አድርጓል፡፡ በእርግጥ ለዚህ ተግባሩ ተገቢውን ዋጋ የከፈለ ይመስለኛል፤ ዛሬም ድረስ በድርጅታዊ አቅምና የፖለቲካ ቁመና
መጠናከር ባለመቻሉ ማለቴ ነው፡፡
ምክንያት ሁለት
የኦህዴድ አመራሮች በነበራቸው ዝቅተኛ የትምህርት ዝግጅት ምክንያት ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ከአስተዳደሪነት ይልቅ ‹‹አዲስ ገዥ
ኦሮምኛ ተናጋሪ መደብ›› የመሆን ዝንባሌያቸው በተደራጁለት የኦሮሞ ተወላጆች ዘንድ ተቀባይነት እና ድጋፍ እንዳያገኙ አድርጓቸዋል፡፡
ምክንያት ሶስት
ኦህዴድ ኢህአዴግን ከመሰረቱት ከሌሎቹ ሶስቱ ድርጅቶች በተለየ መልኩ የአመራር አባላቱ በተለያየ ጊዜ ለቀው መውጣታቸው ለከፍተኛ
ችግር አጋልጦታል፡፡ ሀሰን አሊ፣ ዮናታን ዲቢሳ፣ (ሁለቱም የስራ አስፈፃሚ አባላት ናቸው) ነጋሶ ጊዳዳ፣ አልማዝ መኩ፣ ዱባለ ጀሌ፣ ዲሪባ
ሀርቆ እና ያሲን የተባሉ የአመራር አባላት እንደምሳሌ ይጠቀሳሉ፡፡ (ዮናታን ዲቢሳ እና አልማዝ መኩ ኦነግን ተቀላቅለዋል)
ምክንያት አራት
ኦህዴድ ከሌሎች የግንባሩ ፓርቲዎች በበለጠ መልኩ አብዛኛው ከፍተኛ ካድሬዎቹ በተለያዩ ጊዜያት ለሙስና መጋለጣቸው ደካማ ድርጅት
ሆኖ እንዲዘልቅ አድርጎታል (በ1989 ዓ.ም. ብቻ ከነበሩት 10,300 ካድሬዎች ውስጥ/መካከል 10ሺውን በሙስና ማባረሩ ይታወቃል)
እንዲያውም አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች በኦህዴድ ውስጥ ያለውን ሙስና እና የጥቅም ትስስር መነሻ በማድረግ ድርጅቱን ‹‹የጥቅመኝነት
ፖለቲካ›› ምን እንደሚመስል ማሳያ አድርገው ሲያቀርቡት ይታያል፡፡
ምክንያት አምስት
ኦህዴድ ከህወሓት/ብአዴን ተፅእኖ (ቁጥጥር) ነፃ ያለመሆኑ ነው፡፡ ቅድሚያም የሚሰጠው ለኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ሳይሆን ለሁለቱ ድርጅቶች
ፍላጎት ነው፡፡
ምክንያት ስድስት
የኦህዴድ መስራቾችም ሆኑ በዚህ ወቅት ፓርቲውን የሚመሩት በየትኛውም መንግስት (ዘመን) የኦሮሞን ጥያቄ አንስተው የማያውቁ
መሆናቸው በራሱ ጥያቄውን ከእነመልሱ እንዳያውቁት አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ድርጅቱ እንደድርጅት እንዳይቆም እንቅፋት
ሆኖበታል።
የኦህዴድ የውጭ ተግዳሮቶች
ኦህዴድ ከምስረታው ጀምሮ በህወሓት ተፅዕኖ ስር የነበረ ሲሆን ካለፉት አስር አመታት ወዲህ ደግሞ ብአዴንም በኦህዴድ ላይ ተፅዕኖ
የማሳደር ችሎታን (ፖለቲካዊ ጉልበት) አዳብሮአል፡፡
ብአዴን እና ህወሓት ኦህዴድን በተለየ መልኩ ለመቆጣጠር ያላቸው ፍላጐት ‹‹ከፍራቻ የመነጨ›› እንደሆነ ይነገራል፡፡ ምክንያቱም
ኢህአዴግ የተመሰረተው በብሄር ፖለቲከኞች ከመሆኑ አኳያ የሚከተለው ፌደራላዊ አስተዳደር ቀመር ‹‹በህዝብ ብዛት፣ በሀብት
ተመጣጣኝነት እና ከመልከዐ-ምድራዊ አስተዳደር አመችነት…›› ከመሆን ይልቅ ‹‹ቋንቋን›› መሰረት ያደረገ ሲሆን፤ ኦህዴድ ደግሞ
ከአባል ፓርቲዎች በህዝብ ብዛት፣ በምጣኔ ሀብት፣ በቆዳ ስፋት እና በመሳሰሉት በእጅጉ የሚልቅ ሆኖ በግንባሩም ሆነ በመንግስት ውስጥ
ያለው ስልጣን ከቁመቱ ጋር ያልተመጣጠነ መሆኑ ምን አልባት አንድ ቀን እንደእሳተ ጎመራ ሊፈነዳና ሊታረም የማይችል ጉዳት
ሊያስከትል ይችላል የሚል የስጋት ቀጠና ስለሆነባቸው ነው፡፡ በተለይም በኢትዮጵያ ያለው ፌደራሊዝም ከመሰረታዊ ባህሪያቶቹ አንፃር
በትክክል ቢተረጎም ኢህአዴግ ‹‹Ethnic Congress Party›› (የመድብለ-ዘውግ ስብስብ) ከመሆኑ አኳያ ኦህዴድ የሚያነሳው የስልጣን
ጥያቄ ህገ-መንግስታዊ ድጋፍ እንዳለው እነህወሓት/ብአዴን ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡
ከአራቱ የግንባሩ አባል ፓርቲዎች ውስጥ በፓርላማው የበለጠ መቀመጫ ያለውም ኦህዴድ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ድርጅቱ የወከለውን ህዝብ
‹‹ታሪካዊ የስልጣን ጥያቄ›› ይዞ ቢነሳ እና በግንባሩ ፓርቲ አባላት መካከል ልዩነት ቢከሰት በቀላሉ የኦህዴድ ሊቀመንበር ጠቅላይ
ሚኒስትር የመሆን እድሉ ይሰፋል፡፡ህወሓት፣ ብአዴን እና ደኢህዴን በተለያየ ጊዜ የኢህአዴግ ሊቀመንበር እና የም/ሊቀመንበርነቱን ቦታ ሲፈራረቁበት ኦህዴድ አንድም ጊዜ
ተራ ደርሶት አያውቅም፡፡ እዚህ ጋር ‹‹የህዝብ ብዛት›› የሚለውን መስፈርት ትተን ብዙውን ጊዜ ህወሓት እና ብአዴን ስነ-አመክንዮ
የሚያደርጉትን ‹‹የትግል ተሞክሮ›› እንኳ እንደመስፈርት ቢወሰድ፣ ኦህዴድ ቢያንስ ከደኢህዴን የተሻለ ‹‹የቆይታ ታሪክ›› ያለው ከመሆኑ
አኳያ ኢህአዴግን በሊቀመንበርነት አለመምራቱ በኦሮሞ ተወላጆች ዘንድ እምነት እንዳይጣልበት አድርጎታል፡፡
የሆነ ሆኖ ለኦህዴድ ድክመት የህወሓት አመራሮች የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡ ምክንያቱም ህወሓቶች ኦህዴድ በራሱ እንዳይቆም
ከማድረጋቸውም ባሻገር በተለያዩ መድረኮች የአመራር አባላቱን በጋራ እና በተናጥል ሲያሸማቅቁት ይታያል፡፡ በተለይም ጠንካራ የኦሮሞ
ብሄርተኛ የሆነ የኦህዴድ አመራር ሲመጣ ‹‹ኦነግ›› እያሉ ማሸማቀቅ የተለመደ የግንባሩ የፖለቲካ ጨዋታ ነው፡፡ ይህንን አይነት
የማጠቋቆር ፖለቲካ በአብዛኛው ይጠቀም የነበረው የህወሓት አመራር ነው፡፡ አቶ መለስ ‹‹ህወሓት እና ብአዴን ንብ ሆነው ማር ሲሰሩ፤
ኦህዴድ ደግሞ ማሩን ሊልስ የመጣ ዝንብ ነው›› ሲሉ ድርጅቱን ከማጣጣላቸውም ባሻገር በትምህርት ዝግጅታቸውና በፖለቲካ
ንቃታቸው የተሻሉ የሚባሉትን የአመራር አባላቱን በተናጥል ያሸማቅቁ ነበር፡፡ ለምሳሌ ግርማ ብሩን ‹‹ጎበዝ! ነገር ግን የሸዋ ፊውዳል
ባህሪ የተጠናወተው›› ሲሏቸው፤ ዶ/ር ሙላቱ ተሾመን ደግሞ ‹‹ሙስና ውስጥ ባይገባም ሠነፍ ነው›› ያሉበትን አጋጣሚዎች ማንሳት
ይቻላል፡፡ አቦይ ስብሃት ነጋም በአንድ ወቅት ‹‹ከሜዳ ሰብስበን አምጥተን ሚንስትር አደረግናችሁ›› በማለት የኦህዴድ አመራርን
የፖለቲካ ጉልበት ‹‹የለህም›› ሲሉ በግልፅ ተናግረዋል፡፡ የቀድሞ የኦህዴድ የአመራር አባል ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ‹‹አቶ መለስ የአሜሪካ
አምባሳደር (በ1980ዎቹ አጋማሽ የነበረው) ‹የኦህዴድ አመራር አባላት ሆሊጋንሲቲክ ነው› ብሎኛል ብለው በተዘዋዋሪ ይሰድቡን ነበር››
ሲሉ ያስታውሳሉ፡፡
በእንዲህ አይነት ሁኔታም ኦህዴድ ውስጥ አቅም ያላቸው ሰዎች እየደበዘዙ እንደሄዱ ይነገራል፡፡ ነጋሶ ጊዳዳ፣ ሽፈራው ጃርሶ፣ ግርማ ብሩ፣
ሙላቱ ተሾመ… በተወሰነ ደረጃ የኦህዴድን ነፃነት ለማስመለስ የሞከሩ አመራሮቹም ‹‹በጠባብነት››  እና ‹‹የኦነግ አመለካከት ተሸካሚ››
በሚሉ ተቀጥያዎች ተወንጅለው ተገምግመዋል፡፡ እስከመጨረሻው የህወሓትን ጣልቃ ገብነት ከተቃወሙት ውስጥ ነጋሶ ጊዳዳ እና
ሽፈራው ጃርሶ ይጠቀሳሉ፡፡ ነጋሶ በ93ቱ የኦህዴድ ግመገማ ላይ በታዛቢነት ለመገኘት የመጡትን የህወሓት የአመራር አባል ስብሃት ነጋን
በይፋ ከመቃወምም አልፈው ‹‹እናንተ በዚህ አይነት መልኩ በእኛ ጉዳይ ጣልቃ እየገባችሁ የምትቀጥሉ ከሆነ አንፈቅድም፤ እኛ ሞተን
ቢያንስ ለልጆቻችን ነፃነትን እንሰጣቸዋለን›› እስከማለት ደርሰው ነበር፡፡ ኦህዴድ የተጓዘው በዚህ መልክ በመሆኑ ተቆርቋሪ አባላቱን
በየመንገዱ አራግፎአል፡፡
ለዚህም ነው በአሁኑ ወቅት ኦህዴድን ከሚመሩት ውስጥ አብዛኛው ከ1993 ዓ.ም በፊት የወረዳ ካድሬ የነበሩ እና በአስቸጋሪው ዘመን
ያላለፉ በመሆናቸው ከፍተኛ ልምድ ያላቸውን የህወሓት/ብአዴን አመራርን መገዳደር የማይችሉ የሆኑት፡፡ ለምሳሌም ሙክታር ከድር
በወለጋ ጊንቢ የድልመጂ ወረዳ ካድሬ የነበሩ ሲሆኑ፣ አለማየሁ አቱምሳም እዛው ወለጋ የአንድ ወረዳ ኃላፊ ነበሩ፤ አስቴር ማሞ ደግሞ
በጅማ ዞን የኦህዴድ ሴቶች ሀላፊ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ከ93ቱ የኦህዴድ ‹‹ፈርሶ መሰራት›› በኋላ ሙክታር የጅማ ዞን ሀላፊ ተደርገው ተሾሙ፤
አለማየሁ አቱምሳ ደግሞ የምዕራብ ወለጋ የድርጅት ቢሮ ኃላፊ ለመሆን ቻሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት አለማየሁ አቱምሳ የኦህዴድ ሊቀመንበር
እና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዘዳንት ናቸው፡፡ ሙክታር ከድር ደግሞ የኢህአዴግ ጽ/ቤት ኃላፊ፡፡ ይህ ሁኔታ ከሌሎቹ የግንባሩ ፓርቲ አባል
ድርጅቶች አንፃር ሲታይ የተለየና ጤናማ ያልሆነ መተካካት በመሆኑ ኦህዴድን ደካማ ከማድረጉም በላይ ልምድ በሌላቸው ወጣቶች
መዳፍ ስር እንዲወድቅ አስገድዶታል፡፡
የኦነግ ተፅእኖ
ኦህዴድ ከህወሓት/ብአዴን በተጨማሪ ከኦነግ የሚነሳበት ተፅእኖ ለድክመቱ የሚጠቀስ ነው፡፡ ኦነግ ከዚህ ቀደም በኦሮሚያ ላይ በነበረው
ተፅዕኖ እና በብሄሩ ያለውን ተቀባይነት እየመነዘረ ኦህዴድ ላይ ያደርግ የነበረው ማጥላላት፣ ኦህዴድ ሊቋቋመው ያልቻለው ሌላኛው
ተግዳሮት ነው፡፡
የኦነግን ጥቃት የከፋ የሚያደርገው ኦህዴድን የሚወነጅለው በሚከተለው ርዕዮተ አለም ሳይሆን በኦህዴድ የአመራር አባላት ማንነት ላይ
መሆኑ ነው፡፡ ሁሉም የኦህዴድ መስራቾች በመደበኛ እና ብሔራዊ ወታደር ሆነው በኤርትራ ምድር ላይ በሻዕቢያ ተማርከው ኦህዴድን
እንዲመሰርቱ መደረጉ ለኦነግ ትችት መደላድል ፈጥሯል፡፡ እናም ኦነግ ሁናቴውን ለበርካታ ዓመታት መጫወቻ ካርድ አድርጎታል፡፡
ከዚህም ባሻገርን ኦነግ ከመንግስታዊ ስልጣን የወጣሁት ‹‹አሻንጉሊት ለመሆን ባለመፍቀዴ ነው›› የሚለው ፕሮፓጋንዳው ኦህዴድን
በብሔሩ እንዳይታመን አድርጎ ተጠቅሞበታል፡፡ እንግዲህ ለደካማው ኦህዴድ ‹‹ባለበት መርገጥ›› የኦነግ በኦሮሞ ህዝብ ዘንድ መታመን
የራሱ ተፅዕኖ ነበረው፡፡ ኦነግ ይህንን ጉዳይ ለጥጦ የኦህዴድ መስራቾችን ‹‹ስማቸውን በኦሮሞ ስም የቀየሩ›› እስከማለት በመድረስ
የኦህዴድ ሰዎች ኦሮሞ መሆናቸውንም ጭምር ጥርጣሬ ላይ የጣለበት ሁኔታ አለ፡፡ በእርግጥ ኦህዴድ ለዚህ ምላሽ ይሆን ዘንድ የኦነግን
አካሄድ ‹‹የጠባቦች መንገድ›› ቢልም የሰማው አላገኘም፡፡ አልፎ ተርፎም በ1986 ዓ.ም ‹‹ፕሮግራሜ›› ሲል ባሰራጨው ሰነድ ላይ
‹‹ኦሮሞ በብሄሩ ውስጥም ሆነ በመላ ኢትዮጵያ ደረጃ የሚገኙትን መደባዊ ጠላቶቹን ለመምታት በሚያስችለው ዴሞክራሲያዊ አቋም ላይየተገነባ ስልት ሊያካሄድ ይገባዋል›› ሲል የገለፀው ከኦነግ ፕሮግራም ጋር ፍቅር በወደቁ የኦሮሞ ተወላጆች ዘንድ እንደ‹‹መናፍቅ››
እንዲታይ አድርጎታል፡፡
አዲሱ ትውልድ
የኦህዴድ የአመራር አባላት ከላይ በተጠቀሰው ችግር ውስጥ የወደቁ ቢሆኑም በአሁኑ ወቅት በከፍተኛና የበታች ካድሬነት ኦህዴድን
የተቀላቀለው አዲሱ ትውልድ ‹‹ጣልቃ ገብነትን›› ለመቀበል የተዘጋጀ አይመስልም፡፡ ይህም ሁኔታ የኦህዴድን አመራር አጣብቂኝ ውስጥ
ከቶታል፤ ምክንያቱ ደግሞ ‹‹የብሄር ፌደራሊዝሙ በትክክል ከተተገበረ የጠቅላይ ሚንስትሩ ቦታ የኦህዴድ ነው›› የሚል
ለህወሓት/ብአዴን አደገኛ የሆነ አዝማሚያ ያላቸው የኦሮሞ ወጣቶች ከቀን ወደቀን መበራከታቸው ነው፡፡ በአናቱም በኦነግ አንድም
ተስፋ የቆረጡ፣ ሁለትም የኦነግ አቋም ፋሽኑ አልፎበታል ወደሚል ድምዳሜ የተጠጉ ሆኖም ‹‹መንፈሱ››ን እንተገብራለን የሚሉ የብሄሩ
ልሂቃኖችና በድህረ-97 ፓርቲውን የተቀላቀሉ ወጣቶች ‹‹ኦህዴድን ከውስጥ መቀየር ይቻላል›› በሚል ስሌት በድርጅቱ ዙሪያ
መስፈራቸው ለአመራሩ ሌላ ራስ ምታት ሳይሆን እንዳልቀረ ይገመታል፡፡
የመስከረሙ ኦህዴድ
በዚህ በአዲሱ ዓመት ኦህዴድ በውስጣዊ አብዮት እየታመሰ ነው፡፡ ገና ከጅምሩም ከኃላፊነታቸው ዝቅ ያሉ አመራሮችን እያየን ነው፡፡
እንደአዲስ የካርታ ጨዋታ ‹‹የተፐወዙ››ም አሉ፤ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዘዳንት አብዱልአዚዝ መሀመድ ወደፌደራል ሲመጡ፣
አስቴር ማሞ ደግሞ ከፌደራል ወደክልል ወርደዋል፡፡ (እዚህ ጋ የህወሃት/ብአዴን የቼዝ ጨዋታ ችሎታ ከደመርንበት ምንአልባት አስቴር
ማሞ የክልሉ ፕሬዘዳንት ወይም ምክትል ፕሬዘዳንት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ንጉሱ አለማየሁ አቱምሳ ህመምተኛ ሆነዋል፤ አንሰላሳዊው የቼዝ
ተጫዋች በንግስቲቱ በሚገባ እየተጠቀመ ነው፡፡ ንጉሱንም እያሳደዷቸው ነው-በቼዝ ጨዋታ፡፡ አቶመለስ በህይወት በነበሩበት ጊዜ አስቴር
ማሞን ለፕሬዘዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ቦታ አጭተዋቸው ነበር፡፡) የማታ ማታም ወደእስር ቤት የሚላኩ የኦህዴድ አመራሮች ሊኖሩ
እንደሚችል እየተነገረ ነው፡፡ በእርግጥ በግሌ ይህ የአብዮት ሰይፍ የተመዘዘው ከኦህዴድ ጽ/ቤት ነው ብዬ አላምንም፡፡ አራት ኪሎ
ከሚገኘው የኢህአዴግ ጽ/ቤት ነው ብል ግን ማጋነን አይሆንብኝም፡፡ ይህንን የሚያረጋግጡ አንዳንድ ምክንያቶችንም መጥቀስ ይቻላል፡፡
የጁነዲን ጥፋት…        
የቀድሞ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዘዳንት ጁነዲን ሳዶ ተገምግመው ተገኘባቸው በተባለ ጥፋት ከኦህዴድ የአመራር አባልነታቸው ተነስተው
ተራ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ተወስኖባቸዋል፡፡ በእርግጥ የጥፋቱን አንድምታ ገምግመን በቀላሉ ከዚህ ውሳኔ ጀርባ ‹‹እነማን አሉ?››
የሚለውን ማየት ወይም መገመት የሚቻል ይመስለኛል፡፡ መቼም የኦህዴድ ሊቀመንበር ተብለው በተሾሙ ማግስት ታማሚ የሆኑት
ዓለማየሁ አቱምሳ እና እነሙክታር ከድር በዚህ ደረጃ ገፍተው ቀዳሚ አባል የነበሩትን ጁነዲንን ለማባረር በራሳቸው የሚቆሙ
አይመስለኝም፡፡ በአናቱም በጁነዲን ላይ የቀረበው ክስ በቀጥታ የሚገናኘው ከኢህአዴግ እና ከመንግስት ጋር ነው፡፡ ምክንያቱም ጁነዲን
በጋዜጣ የተቃወሙት ‹‹ባለቤቴን በግፍ አሰረብኝ›› ያሉትን መንግስት እንጂ የራሳቸውን ድርጅት ጓዶች አይደለም፡፡ (በነገራችን ላይ
መንግስት ‹‹ዋሀቢያ›› እያለ የሚያሸማቅቃቸው ሠለፊዎች በሳውዲ አረቢያ እንደሚደገፉ ሲነገር፤ ከአሀባሽ ጀርባ ደግሞ የአሜሪካ
መንግስት እጅ አለ በሚባለው መላ-ምት ከተስማማን እና የጁነዲን ባለቤት የተያዙት ከሳውዲ አረቢያ ኤምባሲ 50 ሺህ ብር ከበርካታ
ቅዱስ ቁራን ጋር በዕርዳታ ተቀብለው መሆኑን ደምረን ቀላል ሂሳብ ካደረግነው፤ የኦህዴድ የመስከረም አብዮት በትክክልም ባለቤቱ ማን
እንደሆነ ግልፅ ይሆናል)
ከአራቱ ድርጅቶች ‹‹በተከፋፈለ አመራር›› ስር በመውደቅ ኦህዴድ ሪከርዱን እንደያዘ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ የተፈጠረው በኦህዴድ ውስጣዊ
ድክመት ብቻ አይደለም፡፡ የህወሓት አመራር በሀገሪቱ ላይ ይከተለው የነበረው የማኪያቬሊ አስተምህሮት (ከፋፍለህ ግዛን) በኦህዴድ
ላይም በመተግበሩም ጭምር ነው፡፡ ምክንያቱም ሌሎቹ ድርጅቶች በዚህ ችግር ውስጥ ሲገቡ አይታዩም፡፡ ህወሓት በ1993 ዓ.ም. ለሁለት
ሲከፈል ከተፈጠረው ችግር ውጭ ማለቴ ነው፡፡ የብአዴን ወይም የደኢህዴን የአመራር አባላት አንድም ጊዜ እርስ በእርስ ሲወነጃጀሉ
የታየበት አጋጣሚን አላስታውስም፡፡ ኦህዴድ ግን ብዙ ጊዜ በእንዲህ ዓይነት ማዕበል ተመቶ ሲንገላታ ተመልክተናል፡፡ የእርስ በእርስ
ክፍፍሉ ምን ያህል በተናጥል ወይም በግለሰብ ደረጃ እንደወረደ የሚያሳየው ምሳሌ በ93ቱ ተሃድሶ የኦህዴድ የአመራር አባል የነበሩት
አልማዝ መኩ በወቅቱ ከህወሓት ጋር ችግር ውስጥ ገብተው የነበሩትን ነጋሶ ጊዳዳን ‹‹ሂሳብህን አወራርድ!›› እያሉ ተችተው
ሲያበቁ፣ በአንድ ወር ውስጥ ጥብቅና የቆሙለትን ስርአትም ሆነ ቀሪውን የኦህዴድ የአመራር አባላት ከድተው ከሀገር መኮብለላቸውን
ስናስተውል ነው፡፡ በእርግጥም በርካታ አመክንዮችን እየጠቀስን የኦህዴድ አመራር ተመሳሳይ አቋም ኖሮት አያውቅም፣ ወይም ሆነ ተብሎ
ጠንካራ አመራር እንዳይኖረው ተደርጓል ብለን መከራከር እንችላለን፡፡ በዚህ የእርስ በእርስ መጠላለፍም ዋነኛ ተጠቃሚው
ህወሓት/ብአዴን መሆኑን መከራከር ጉንጭ አልፋ ነው፡፡ኦህዴድ ብዙ ጊዜ ፈርሶ ተሰርቷል፡፡ ከኦሮሞ ህዝብ ጋር አይንና ናጫ እንደሆነም ነው ዛሬ ላይ የደረሰው፡፡ ኦነግ ከክልሉም ተባሮ ኦህዴድ
የኦሮሞን ህዝብ መማረክ አልቻለም ነበርና በወቅቱ አቶ መለስ ‹‹ዝንብ›› እያሉ የሚያጣጥሉትን ኦህዴድ ጠንካራ መሆኑን ገልፀው ሲያበቁ
የኦሮሞ ህዝብ ይቀበለው ዘንድ እንዲህ ሲሉ ማስታወቂያ ሰርተውለት ነበር ‹‹ማዕበሎች ከቀኝም ከግራም ተነስተው ነበር፡፡ በማዕበሉ
የተናደደና የተሸረሸረ ባይጠፋም፡፡ ኦህዴድ ልክ እንደዋርካው ወደ መሬት ገብቶ ስለነበር አልተነቃነቀም›› …ዛሬ ግን ይህን የሚል የለም፡፡
እናም የኦሮሞ ተወላጆች እየደረሰባቸው ያለው መከራ፣ መሰረታዊ ጥያቄያቸው፣ እንዲሁም የ‹‹ዋርካው›› ዕጣ ፈንታ ከመስከረሙ አብዮት
ፊት ለፊት የቆሙ ይመስላል፡፡ ኦህዴድ ደግሞ ችግርህ የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄን መመለስ አለመቻልህ ሳይሆን ‹‹መደባዊ›› ነው ተብሎ
ስለተነገረው ‹‹ኪራይ ሰብሳቢ›› እና ‹‹ልማታዊ›› በሚሉ አጀንዳዎች ተጠምዷል፡፡