Tuesday, December 4, 2012

ሰማያዊ ፓርቲ የአቡነ ጴጥሮስን ሀውልት መፍረስ ተቃወመ


ሰማያዊ ፓርቲ የአቡነ ጴጥሮስን ሀውልት መፍረስ ተቃወመ

ኢሳት ዜና:-ፓርቲው ባወጣው መግለጫ ማንኛውም ልማት ወጪን ቆጣቢ ሆኖ መሰራት እንዳለበት የሚታመን ቢሆንም በዋጋ ሊተመኑ የማኢችሉ ቅርሶችን በማጥፋት ግን ወጪን ለመቀነስ ማሰብ የእብደት አስተሳሰብ ነው ብሎአል።ህዳር ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ይልቃል ጌታሁን ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ  ኢህአዴግ ከፍ ብሎ ለመታየት ባለው ፍላጎት የተነሳ ከዚህ በፊት የተሰሩትን ስራዎች ሁሉ ለማሳነስ እንደሚሞክር ገልጠው፣ የአቡነ ጴጥሮስን ሀውልት ለማፍረስ ቀድሞውን ነገር መታሰብ አልነበረበትም ብለዋል
የመንግስት ባለስልጣናት የአቡነ ጴጥሮስን ሀውልት ለማፍረስ ሲወስኑ አጥር እንደማፍረስ አድረገው እንደቆጠሩት የተናገሩት አቶ ይልቃል ፣ ህዝብ ባይጮህ ኖሮ መልስ ለመስጠትም አይፈልጉም ነበር ብለዋል
የግራዚያኒ ሀውልት ጣሊያን ውስት ሲሰራ በዛው ሳምንት የአቡነ ጴጥሮስ ሀውልት መፍረሱ የታሪክ ምጸት ነው በማለት የመንግስትን የታሪክ አረዳድ አቶ ይልቃል ተችተዋል
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሉሲ በመጪው የፈረንጆች አመት አጋማሽ ላይ ወደ ኢትዮጵያ እንደምትመለስ መንግስት አስታውቋል።
የህወሀት/ኢህአዴግ ንብረት የሆነው ፋና ብሮድካስቲንግ እንደዘገበው  የ5 ዓመታት ቆይታ ለማድረግ ወደ አሜሪካ ያመራው የሉሲ ቅሪተ አካል በመጪው የፈረንጆች ዓመት አጋማሽ ላይ ወደ ኢትዮጵያ ይመለሳል።
ቅሪተ አካሉ ከመመለሱ በፊት የመጨረሻ ኤግዚቪሽኑን በካሊፎርኒያ ለማካሄድ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ራዲዮው ዘግቧል።
በመጪው የ2013 የፈረንጆች አመት አጋማሽ ላይ ከሉሲ ጋር አብረው የሄዱትን ፥ ሌሎች 149 ቅርሶች በተሸኙበት መልኩ በጥሩ ሁኔታ ለመቀበል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮናስ ደስታን ዋቢ አድርጎ ራዲዮው ዘግቧል
ከሉሲ ጉብኝት የሚገኘው ገንዘብ በፕሮጀክቱ ስም በተከፈተው አካውንት ገቢ በመደረግ ላይ መሆኑንና ፥ ፕሮጀክቱ ከተጠናቀቀ በኋላ ሙዚየሞችን ለማሳደግና ለማስፋፋት እንደሚውል ራዲዮው ዘግቧል።
ይሁን እንጅ የሉሲ አጽም ትክክለኛው ይመለስ ቅጅው አይታወቀም። በሉሲ አማካኝነት ስለተገኘው ገንዘብ ዝርዝር ማብራሪያም አልተሰጠም። ራዲዮው  በሚቀጥለው የፈረንጆች አመት አጋማሽ ላይ አለ እንጅ በየትኛው ወርና ቀን ሉሲ ወደ አገሯ እንደምትመለስ አልተገለጸም።