Sunday, January 13, 2013

አፄ ቴዎድሮስ - የትንሳዔው ሰማዕት ምጥን ዳሰሳ በወሰንሰገድ ገ/ኪዳን (ጋዜጠኛ)


አፄ ቴዎድሮስ - የትንሳዔው ሰማዕት
ምጥን ዳሰሳ
በወሰንሰገድ ገ/ኪዳን (ጋዜጠኛ)
“…ተስፋ ባጣ ምድረ በዳ
ያንድ እውነት ይሆናል ዕዳ
እና ትንፋሼ አልሆነሽም - ሆኜብሽ መራር መካሪ
‹ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ›
እውነት ላንቺ መች ተስፋ ናት - ጉስቁል ልሳንሽ ነክሳሽ
ክንድሽን ካዛለ ቅርስሽ- መጠላለፍ ሲሆን እጣሽ
ከእንግሊዝ የሞት አማልክት - መተናነቅ ሲሆን ድርሻሽ
መልመጥመጡ መሽቆጥቆጡ - መስሎሽ ድንገት የሚያዋጣሽ
የእኔ እውነት ሆኖብሽ ዕዳሽ፡፡….”
ጸጋዬ ገ/መድህን
“እሣት ወይ አበባ” 1966 ዓ.ም
ይህንን ቅንጭብ የሎሬት ጸጋዬ ገ/መድን ቅንጭብ ግጥም ስናነብ፣ በኢትዮጵያ የብዙ ሺህ ዘመናት ታሪክ ሂደት ውስጥ “ለየት ያለ” ታሪክ ያላቸውን ንጉሥ ማስታወሳችን አይቀርም፡- አፄ ቴዎድሮስን፡፡
አፄ ቴዎድሮስ፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ከነገሡት ነገሥታት ሁሉ “የተለዩ” የሚያደርጓቸው በርካታ ሁኔታዎች አሉ፡፡ ከነዚህ ሁነቶች አንዱና ዋንኛው በትውልድ ዘር ሃረግ ይተላለፍ የነበረውን የሥልጣን ቅብብሎሽ በኃይላቸው ያቋረጡ በመሆናቸው ነው፡፡ በሌላ አባባል ከተራ ሽፍትነት ተነስተው የሃገሪቱን መንበረ ሥልጣን የተቆናጠጡና ለንጉሠ ነገስትነት የበቁ በመሆናቸው ነው፡፡ በዚህም የተነሳ የአፃ ቴዎድሮስ የንግስና ዘመን፤ ኢትዮጵያ ከቀደመው ታሪኳ በተለየ መልኩ፣ ወደ አዲስ የታሪክ ምእራፍ የተሸጋገረችበት ጊዜ ተደርጎ እንደሚታመን የዘርፉ ምሁራኖች ያትታሉ፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፤ ሌላም ሌላም ታሪካቸው ከሌሎች ነገሥታቶች በተለየ መልኩ እንዲታዩ ምክንያት መሆኑ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ የሆነ ሆኖ ይህ የአሁኑ ትውልድ ከቀደመው ትውልድ በተሻለ መልኩ የአፄ ቴዎድሮስን ታሪክ ያውቃል ማለት ይቻላል፡፡ ታሪካቸው በተለያዩ የትምህርት መማሪያ መፅሐፍቶች ውስጥ ተቀንጭበው ቀረበውለታል፡፡ በተለያየ ወቅት በሬድዮና በቴሌቪዥን ተተርኮለታል፡፡ በኢትዮጵያውያን ፀሐፍት የተዘጋጁ ዳጎስ ዳጎስ ያሉ መፅሐፎች ለህትመት በቅተውለት አንብቧል፡፡ ስለዚህ ይህ ትውልድ በደምሳሳው ወይም በግርድፉም ቢሆን የአፄ ቴዎድሮስን ታሪክ ያውቃል ብንል ስህተት አይሆንም፡፡ ይሁን እንጂ የአፄ ቴዎድሮስን ታሪክ በምልዐት ያውቃል ወይም እናውቃለን ብሎ መደምደም አይቻልም፡፡
የአፄ ቴዎድሮስን ዘመነ መንግስት ከጅማሬው እስከፍፃሜው የሚተርኩ መፅሐፎች የታተሙ ቢሆንም፣ በእኛው ሰዎች (በኢትዮጵያውያን) የተዘጋጁ መፅሐፎች ቁጥር አነስተኛ ወይም በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ በሌላ አገላለፅ ስለአፄ ቴዎድሮስ ያለን ዕውቀት፣ የዘመነ መንግስታቸው ተጨባጭ ሁኔታ የሚያሳዩ ታሪካዊ ሰነዶች፣ የግለሰብ ምስክርነቶች፣ የደብዳቤ ልውውጦች….ወዘተ በተመለከተ ያሉን መረጃዎች ውስን ናቸው፡፡ አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በ18ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ የአፄ ቴዎድሮስን እና የመንግስታቸውን ተግባራት የሚተርኩ የተለያየ ይዘት ያላቸው 60 ያህል መፅሐፍቶች በእንግሊዘኛ እና በጀርመንኛ ቋንቋ ለህትመት በቅተዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ምክንያቱ አፄ ቴዎድሮስ በተለየ መልኩ ከሚታወቁበት የመቅደላ ዘመቻ አስቀድሞ ወደ ኢትዮጵየ መጥተው የነበሩ አውሮፓውያን የአፄውን ባህርይ፣ የአስተዳደር ዘይቤ፣ እንዲሁም በወቅቱ የነበረውን የሥልጣን ሽኩቻ የወለዷቸውን የአመፅ እንቅስቃሴዎችን …ወዘተ በተመለከተ በርካታ መረጃዎችን መያዝ (ማኖር) መቻላቸው ነው፡፡
እንዲህም ተባለ እንዲህ የአፄ ቴዎድሮስ “ታሪካዊ ምስጢርነት” እስካሁን ድረስ በተለያዩ ፀሐፊዎች እየተገለጠ ይገኛል፡፡ ለዚህ አባባላችን አስረጅ የምናደርገው ከ5 ዓመት በፊት (እኤአ በ2007) በፈረንጅ አፍ ተፅፎ ለህትመት የበቃውን “THE BAREFOOT EMPERIOR” መፅሐፍ ነው፡፡ የዚህ መፅሐፍ ደራሲ በጉዞ መፅሐፍት ደራሲነቱ “ተመራማሪው ባለ ንስር ዓይን” የሚል ዝና ያተረፈው ፊሊፕ ማዲሰን ነው፡፡
በእርግጥም ደራሲው “ባለንስር ዓይን” ሊባል የሚገባው ነው ብለን ለመመስከር እንገደዳለን፡፡ “የማናውቃቸውን” አፄ ቴዎድሮስ በህይወት ያሉ እስኪመስለን ድረስ ታሪካቸውን በአስደናቂ ሁኔታ ከትቦልናልና፡፡ እዚህ ላይ ታዲያ አንባቢያን “የማናውቃቸውን” የሚለውን አገላለፅ ልብ እንዲልልኝ እሻለሁ፡፡ ለምን? ለማስረዳት ልሞክር፡፡
ፊሊፕ ማዲሰን “THE BAREFOOT EMPERIOR” በሚል ርዕስ የፃፈው የአፄ ቴዎድሮስ ታሪክ፣ ለባለታሪኮቹ ኢትዮጵያውያን ይደርስ ዘንድ ወደ አማርኛ ቋንቋ ተመልሶ በታህሣሥ ወር 2005 ዓ.ም መጀመሪያ ለህትመት በቅቷል፡- በጋዜጠኛ ብሩክ መኮንን ተክለየስ ተርጓሚነት፡፡
በኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ታሪክ ውስጥ በቀደምትነት ላቅ ያለ ሙያዊ ተግባር ከተወጡት ጋዜጠኞች መሀል አንዱ የሆነው ጋዜጠኛ ብሩክ መኮንን ተክለየስ፣ “አፄ ቴዎድሮስ - የትንሳዔው ሰማዕት” የሚል ርዕስ ሰጥቶ ነው የፊሊፕ ማዲሰንን መፅሐፍ የተረጎመው፡፡ጋዜጠኛ ብሩክ መኮንን ከዚህ ቀደም ሶስት ደጎስ ደጎስ ያሉ መፅሐፍቶችን ተርጉሞ ለአንባቢያን አበርክቷል፡፡ ይህ መፅሐፍ አራተኛው የትርጉም ሥራው መሆኑ ነው፡፡
መፅሐፉ 310 ገጾች ያሉት ሲሆን፣ በ11 ክፍሎች፣ በ83 ምዕራፎች እና በ2 “ማሳረጊያ” ትረካዎች ነው ደርዝ የተበጀለት፡፡ ከመጀመሪያው ገፅ አንስቶ የመፅሐፉን የመጨረሻ ገፅ ቅጠል እስክናጥፍድረስ ህሊናን ሰቅዞ የሚይዝ፣ ከገፅ ገፅ፣ ከምዕራፍ ምዕራፍ በእጅጉ የሚመስጥ፣ የአተራረኩ ፍሰትና የቋንቋው ለዛ የሚያመረቃ፣ እጅግ ልብ አንጠልጣይ የተዋጣላት መፅሐፍ ነው፡- “አጼ ቴዎድሮስ - የትንሳዔው ሰማዕት”፡፡ ለዚህም ነው “የማናውቃቸው” የሚለውን አገላለፅ አፅንኦት እንድሰጠው የተገደድኩት፡፡ ምክንያቱም የመፅሐፉ አተራረክ አጼ ቴዎድሮስን የማናውቃቸው ያህል እንዲሰማን ግድ ይላል፡፡ የታሪኩ ፍሰት፣ የታሪክ ሽግግሩ፣ የታሪክ ምልሰት ዘይቤው ከ150 ዓመታት በፊት ከአፄው ጋር በአካል የተገኘን ያህል፣ ሁነቶችን ሁሉ በዓይናችን ብሌን የተመለከትን ያህል እንዲሰማን ያደርጋል፡፡ ልክ እንደተንቀሳቃሽ ፊልም አፄውን ዘመናቸውን ቁጭ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው ብል ቅንጣት ማጋነን እንደሌለበት አምናለሁ፡፡
በታሪክ ምሁራን ዘንድ የአጼ ቴዎድሮስ ታሪክ “ሁለት መልክ” ያለው መሆኑ ይነገራል፡፡ ይህ “ሁለት መልክነት” በተርጊሚው የመግቢያ ፅሁፍ እንደሚከተለው ተጠቅሷል፡-
“….ብዙዎች አጼ ቴዎድሮስ በዘመነ መንግስታቸው አንድ ጠንካራ ማዕከላዊ መንግስት ለመመስረት የቻሉ፣ አሁን ላለችሁ ኢትዮጵያ መሠረተ-ድንጋይ ያስቀመጡ፣ የባርያ ንግድን ለማስቆም የጣሩ፣ ሠራዊታቸው በደመወዝ እንዲተዳደር፣ዝርፊያና ውንብድና እንዲቆም ለማድረግ የሞከሩ፣ መድፍ (ሴባስቶፖል) እና ሌሎች የጦር መሳሪያዎች ለመስራትና ለመጠቀም የጣሩ፣ በጣና ሐይቅ ላይ የሚንሳፈፉ ጀልባዎችን፣ መለስተኛ መርከብ ለመስራት የሞከሩ ፋና ወጊ ንጉስ ናቸው ይላሉ፡፡…
“…. በሌላ ወገን ያሉ ደግሞ አጼ ቴዎድሮስ ያከናወኗቸው ተግባራቶች የሚካድ ባይሆንም፣ በሃገሪቱ የመሬት ስሪትን በተመለከተ ግብር ለመሰብሰብ ያደረጉት ሙከራ ከቤተ-ክህነት በደረሰባቸው ተቃውሞ የገጠማቸው…ያሳቡትን ሊያሳኩ አልቻሉም፡፡ …በዚህም ሰበብ በጊዜው የወሳዷቸው እርምጃዎች የተነሳ… ማዕከላዊ መንግስት የመመሰረት አቅም አልነበራቸውም፡፡…የአንድን ሰው ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝን ተግባዊ ያማረጉ ናቸው ይላሉ፡፡…..” (ገፅ) የአጼ ቴዎድሮስን ታሪክ “ሁለት መልክነት” ያመላክታል፡፡
በጋዜጠኛ ብሩክ መኮንን ተክለየስ ተተርጉሞ ለህትመት የበቃውን “አፄ ቴዎድሮስ - የትንሳዔው ሰማዕት” የተሰኘውን መፅሐፍ ስታነቡ ከፍ ብሎ የተጠቀሰውን ሁነት ሁሉ በቦታው፣ በስፍራው፣ በዘመኑ ተገኝታችሁ ያያችሁ ያህል ይሰማችኋል፡፡ የአፄ ቴዎድሮስ ሁለት ዓይነት ስብዕና ማለትም ጀግንነትና አልበገር ባይነታቸው፣ ለአገራቸው ያላቸው ቀናዒነትና ምኞት፣ ቁጡነታቸውንና ሩህሩህነታቸውን፣ ፍፁማዊ ጭካኔያቸውንና ይቅር ባይነታቸውን፣ ዕብደታዊ ተግባራቸውንና የመጠቀ ፍልስፍናቸውን… በሚመስጥ የትረካ ስልት ትመለከታላችሁ፡፡
“ዕብደታዊ” የሚለውን አገላለፅ ስጠቀም ከመፅሐፉ ውስጥ ያነበብኩት እጅጉን የገረመኝ ታሪክ ታወሰኝ፡፡ በጥቂቱ ላካፍላችሁማ፡፡ አፄ ቴዎድሮስ ራሳም የተባለውን እንግሊዛዊ እንዲህ ሲሉ ጠየቁት፡-
“….‹ዴዎጋን የለየለት ዕብድ ነበር ወይስ ንክ?› አሉት፡፡…‹ታላቁ እስክንድር ዴዎጋንን ጠርቶ ምን ላድርግልህ? ምን ትፈልጋለህ? ብሎ ጠይቆት ነበር፤ ያን ጊዜ ዴዎጋን፣ ይልቅስ ፀሐይ ልሙቅበት፣ ከምትከልለኝ ዞር በልልኝ› አለው ይባላል ሲል ራሳም ነገራቸው፡፡”
“ቴዎድሮስ ‹እኔ የታላቁ እስክንድር ዝርያ እንደሆንኩ ታውቃለህ? የሜቄዶንያ ንጉሥ የታላቋን ኢትዮጵያ ግዛት ጎብኝቶ ነበር፤ ቆይ በደንብ ልግለፅልህ› አሉና ከንቲባ ኃይሉን ‹መፅሐፉን አምጣና ያንን ዜና እስክንድርን አንብብልን› ሲሉ አዘዟቸው፡፡…” (ገፅ 156)
ታሪኩ ይቀጥላል፡፡ ከንቲባው የታዘዙትን ዜና እስክንድር መፅሐፍ አምጥተው ማንበብ ጀመሩ፡፡
“…ታላቁ እስክንድር ንግስት ህንደኬን ለመጎብኘት ወደዚህ ምድር መጣ፡፡…ወደ ቤተመንግስቱ የሚያደርሱ መንገዶች በአልማዝ፣ በኤመራልድ የተጌጡ መሆናቸውን በደስታ ብዛት በአድናቆት አለቀሰ፡፡….”
ዜና እስክንድር ወደ ቤተመንግስት የሚወስደው መንገድ ወደ ገነት ገነት እንደሚያስገባ፣ ቤተመንግስቱ ተጣጥፎ ወደ ተፈለገው ቦታ ተወስዶ በአንድ ሰዓት ወስጥ እንደሚገነባ የሚተርከውን ክፍል አነበቡ፡፡ ቀጠሉ፡፡
“….‹ንግስቲቱ የለበሰችው ቀሚስ ከአልማዝ ማግ፣ ከዕንቁ ድር ሆኖ ጥለቱ በወርቅ የተዘመዘመ መሆኑን አስተዋለ፡፡… ሀንደኬ የእስክንድርን እጅ ይዛ ከተነጠፈው ውድ አልጋ ላይ አስቀመጠችው፤ በራሷ አድርጋው የነበረውን ዘው ጭንቅላቱ ላይ ደፋችለት፤ ስለተፈቃቀዱ አብረው አንድ አልጋ ላይ አደሩ፤ በነጋታው የማለዳ ፀሐይ እስክትወጣ ድረስ በህንደኬ ዕቅፍ ውስጥ ነበር ታላቁ እስክንድር የቆየው፡፡› እያሉ ቴዎድሮስ ዝም ብለው ያዳምጡ ነበር፡፡….”
ከዚያስ?
“…‹ስለታሪኩ ምን ተገነዘብክ? ምንስ አየህበት?› ሲሉ ቴዎድሮስ ጠየቁት፡፡ ራሳም ታሪኩ የሚታመን ስላልሆነለት፣ ቢያወጣውም ቢያወርደውም ከአፈ-ታሪክ በቀር ምንም ሊባል እንደማይችል በማመን ‹እውነቱን ለመናገር ጃንሆይ ታላቁ እስክንድር ወደ ገነት መግቢያውን በር አግኝቶ በዚያ የተወሰነ ሰዓታት ቢያሳልፍም፣ እንደ እኔ እምነት እዚያው መቅረት ሲገባው ወደ ምድር መመለሱ ሞኝ እንደነበር ያሳየኝ ታሪክ ነው› አላቸው፡፡…”
“አፄ ቴዎድሮስ አምቀውት የነበረውን ሳቃቸውን ለቀቁት፤ ከተቀመጡበት ወንበር እስቂወድቁ ድረስ ሲስቁ ከቆዩ በኋላ ‹አቶ ራሳም እኔ እንዲህ መሰሉን ቡትቶ ተረት ተረትን እውነት ነው ብዬ የምቀበል ይመስልሀል? ብለው እንደገና ሆዳቸውን ይዘው መሳቅ ቀጠሉ፡፡…›
(156- 157)
እንዲህ ያሉ በርካታ መሳጭና ስዕላዊነት ያላቸው ትረካዎችን ያጨቀ ነው “አፄ ቴዎድሮስ- የትንሳዔው ሰማዕት” መፅሐፍ፡፡ ደራሲው ፊሊፕ ማዲሰን መፅሐፉን ከመፃፉ በፊት የሰበሰባቸውን ሰነዶችና መረጃዎች ካጠናከረ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ አፄ ቴዎድሮስን እና ሴባስቶፖል የረገጡትን ምድርን ተከትሎ፣ የወጡትን ተራራ ወጥቷል፤ የወረዱትን ቁልቁለት ወርዷል፡፡ ደራሲው ታሪኩ የተፈፀመበትን ቦታ በአካል ተገኝቶ ጥናታዊ እይታ ማድረጉ እያንዳንዱን ትረካ ክፍል ስዕላዊ በሆነ መንገድ ለማሳየት (ለመቅርፅ) ሃያል ጉልበትና ብርታት የሆነው ይመስላል፡፡ ለዚህም ነው መፅሐፉ የልብ ወለድ ትረካ ያህል ጥርት ያለ ስዕላዊ ድባብ የተላበሰው ቢባል ስህተት አይደለም፡፡
ይህንን የምለው ወይም ያልኩት እኔ ብቻ አይደለሁም፡፡ ዝነኛ የተባሉ የባህር ማዶ ጋዜጦችና መፅሄቶች ጭምር አስደናቂ ምስክርነታቸውን የቸሩት መፅሐር ነው፡፡ የጥቂቶቹን ምስክርነት መጥቀስ እንችላለን፡፡ እነሆ፡-
“..እጀግ አስደናቂ ከገፅ ወደ ገፅ እያነበቡ በተጓዙ ቁጥር ሙለ ትኩረትን የመሳብና የመቆጣጠር አቅም ያለው መሳጭ ታሪክ የያዘ መፅሐፍ ነው፡፡ እንዲህ ያለ መፅሐፍ ካነበብን ብዙ አመታት አልፎናል፡፡..የመፅሐፉ ደራሲ ፊሊፕ ማድሰን በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ ብዙም ያልተሰማውን፣ በብዙዎች ያልታወቀውን እጅግ መሳጭ አሳዛኝና ስልጣን ከያዙ ጀምሮ ሃገራቸውን ከተቀረው ዓለም ጋር ለማገናኘት ጥረት ሲያደርጉ የነበሩርን የአቢሲኒያ ንጉሥን የሥልጣን ጉዞ ይተርካል፡፡… ”
- ስፔክታተር
“…ፊሊፕ ማዲሰን ኢትዮጵያን፣ በጊዜው የነበረውን አስገራሚ ክንውን በእያንዳንዱ የመፅሐፉ ገፅ ውብና ማራኪ በሆነ የታሪክ አወቃቀር በመገንባት ውብ በሆነ የአተራረክ ስልት አንብቡት ብሎ አቅርቦልናል፡፡..”
- ኒኮላስ ሼክስፒር (ዴይሊ ቴሌግራፍ)
“….በጣም ጥቂቶች ናቸው እንደ ፊሊፕ ማዲሰን ተሳክቶላቸው ከ150 ዓመት በፊት የነበረውን ክስተት ልብን እያንጠለጠለጠሉ መተረክ የሚችሉ፡፡ ፊሊፕ ከነዚህ ስኬታማ ደራሲዎች አንዱ መሆኑን አስመስክሯል፡፡….”
- ጀምስ ዳንሊንግ ፖል (ሜል ኦን ሰንደይ)
ሌሎች እውቅ ሃያሲያንም ደራሲውን አወድሰው ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡ ይገባዋልም፡፡ እኛም መፅሐፉን ተርጉሞ ለባለታሪኮቹ እንዲደርስ ያደረገውን ተርጓሚውን ጋዜጠኛ ብሩክ መኮንን ተክለያስን በእጅጉ ልናደንቅ ግድ ነው፡፡ ከኢትዮጵያውያን ነባራዊ ባህል ጋር አጣጥሞ ውብ በሆነ የቋንቋ አጠቃቀምና ለዛ ጋር አዋህዶ፣ እስከመጨረሻዋ ገፅ ድረስ የታሪኩን ፍሰትና ልብ አንጠልጣይነት ጠብቆ መተርጎም እጅግ አድካሚ፣ ፈታኝና ታላቅ ክህሎትን የሚጠይቅ፣ በአያሌው የሚደነቅ ተግባር ነውና፡፡  በመጨረሻ ይህንን ዳሰሳዊ ፅሁፍ የምቋጨው ጋዜጠኛ ብሩክ መኮንን ተክለየስ “አፄ ቴዎድሮስ - የትንሳዔው ሰማዕት” በሚል ርዕስ ተርጉሞ ለህትመት ያበቃውን በ50 ብር ብቻ በመሸጥ ላይ ያለውን መፅሐፍ ለአንባቢያን በመጋበዝ ነዉ፡፡ መልካም ንባብ!!

“ሲ ዋን” - የግንቦት ልባቦት


  • “ሲ ዋን” - የግንቦት ልባቦት
    በንፍታሌም
    የመጽሐፉ የመጀመሪያ ህትመት ለአንባቢያን የቀረበው በሀገረ-አሜሪካ ነው፡- ከወር በፊት፡፡ እነሆ በወርሃ ሕዳር የመጨረሻ ሳምንት ለሀገር ቤት ተደራሲያንም ይዳረስ ዘንድ ለገበያ ቀረበና እጄ ገባ፡፡
    ዳጎስ ያለ መጽሐፍ ነው፡፡ “ሲ ዋን” የሚል ርዕስ ተሰጥቶታል፡፡ የመፅሐፉ ሽፋን በአብዛኛው ጭልጥ ባለ የባህር ምስል ለብሷል፡፡ በጉልህ ከተፃፈው ርዕስ ሥር እስከ አንገታቸው ድረስ በውሃ የተዘፈቁ፤ እርስበርስ ተሸካክመው፣ ተደጋግፈውና ተቃቅፈው የሚጓዙ ሰዎች ይታያሉ፡፡ በመፅሃፉ ሽፋን ግርጌ ደረቅ መሬት ላይ ኩርምትምት ብለው ተቀምጠው ወደሰፊው ባህር የሚመለከቱ በርካታ ሰዎች ተኮልኩለዋል፡፡ ከርዕሱ በላይ (አናት) እንክትክቱ የወጣ ተራ ጀልባ እና ግዙፍ መርከብ፣ እንዲሁም ከባህሩ ማዕበል ጋር ትንቅንቅ የገጠሙ በርካታ ሰዎች ምስል ይታያል፡፡ የባህሩ መጨረሻና ሠማይ የተገጣጠመ ይመስላል፡፡ ሽፋኑ ላይ የሚታዩት ምስሎች የመፅሐፉን ውስጣዊ ይዘት የሚያሳብቁ ዓይነት ናቸው፡፡ እንዲያም ይሁን እንጂ ርዕሱ ሥሜት የሚሰጥ አልሆነልኝም፡፡
    ቢሆንም ወደውስጥ ዘልቄ ታሪኩን ማንበብ አለብኝ፡፡ ጥቂት ገፆች እንኳ መግፋት አልቻልኩም፡፡ ደራሲው ወደዋናው ታሪክ ከመዝለቁ በፊት በፃፈው “መግቢያ” መፅሐፉን በማስታወሻነት ያበረከተላቸውን ሰዎች እያሰብኩ እንባ ተናነቀኝ፡፡ አብዛኞቹን በአካል አውቃቸዋለሁ፡፡ የሙያ አጋሮቼ ነበሩ፡- የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች፡፡ ከሙያ አጋርነት ባሻገር የሕይወት ግጥምጥሞሽ ያቆራኘን፣ የእስር ቤትን የመከራ ጠበል (ላብ) አብረን የተራጨን፣ መራራውን መከራ በቀልድ እያዋዛን በገጠመን ችግር የተሳለቅን፣ በተረብ የተሞሸላለቅን…ጓደኛሞች ነበርን፡፡ ጥቂቶቹ በአስጨናቂ ሁኔታ ራሳቸውን ለማጥፋት (ለመሞት) የተገደዱ ናቸው፡፡ ከፊሎቹ ሳይወዱ በግድ በእግርም በጢያራም ከሀገር የተሰደዱ ናቸው፡፡ እናም በህይወት ያሉትንም የሌሉትንም አንድ በአንድ አስታወስኳቸው፡፡
    “ሲ ዋን” የተሰኘ አዲስ መፅሐፍ ለአንባቢያን ያበረከተውጋዜጠኛ ዳንኤል ገዛኸኝ ከሀገራቸው ከተሰደዱት የቀድሞው ነፃ ፕሬስ አባላቶች አንዱ ነው፡፡ መፅሐፉን አንብቤ የጨረስኩት በጥልቅ ሐዘን ተውጬ ነው፡፡ የመጽሐፉን የመጨረሻ ገፅ ሳጥፍ ደግሞ ደጋግሞ ወደ ህሊናዬ የመጣው የሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን “የቴዎድሮስ ስንብት በመቅደላ” የሚለው ግጥም ነው፡፡ የሚከተለው፡-
    “…ታዲያ እንግዲህ አንቺ ኢትዮጵያ እኛስ ልጆችሽ ምንድነን
    አመንኩሽ ማለት የማንችል ፍቅራችን የሚያስነውረን
    ዕዳችን የሚያስፎክረን
    ግፋችን የሚያስከብረን
    ቅንነት የሚያሳፍረን ቂማችን የሚያስደስተን፡፡
    ኧረ ምንድነን? ምንድነን?
    አሜኬላ የሚያብብን
    ፍግ የሚለመልምብን፡፡…..”
    አዎ “ሲ ዋን” መፅሐፍ እንዲህ ያሰኛል፡፡ የዚህች ምሰኪን ሀገር ምስኪን ልጆች መከራ የሚያበቃው መቼ ነው? ያሰኛል፡፡ ደራሲው ጋዜጠኛ ዳንኤል ገዛኸኝ ለበርካታ ዓመታት በ“ሞገድ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጅነት ያገለገለ ነው፡፡ በሌሎች የቀድሞ ነፃ ፕሬስ የሕትመት ውጤቶች (ጋዜጦችና መፅሔቶች) በአምደኝነትና በሪፖርተርነት ሠርቷል፡፡ በ1997 ዓም ምርጫ በተከሰተው ሁኔታ ነው ሃገሩን ጥሎ ለመሰደድ የተገደደው፡፡
    “ቅድመ ስደት” በሚል ንዑስ ርዕስ ሥር ባሰፈረው ምጥን ሀተታ “…እስራትን፣ መጋዝን፣ ያለአግባብ መቁሰል፣ መድማትን ለዓመታት ኖሬበታለሁ” ይላል ዳንኤል፡፡ በዚህም የተነሳ ያንገፈገፈውን መከራ ለመሸሽ ሲል “ካሳለፍኳቸው መከራዎች የባሰ ወደሚመረው ስደት ለመግባት ተገድድኩ፡፡” ሲል በአፅንኦት ይገልፃል፡፡ እናም ከሬት መራርነት በላይ የሚጎፈንነውን የሥደት ህይወት በ279 ገፆች ይተርክልናል፡፡
    ዳንኤል ታሪኩን በአራት ክፍሎች (ምዕራፎች) ከፋፍሎታል፡፡ ከአዲስ አበባ - ትልቁ አውቶብስ ተራ ተነስቶ የሥደት ጉዞውን ይጀምራል፡፡ ጉዞውን ለየት የሚያደርገው መውጫ መንገዶች ሁሉ ታጥረውበት ሥደትን መምረጡ ነው፡፡ በመርፌ ቀዳዳ እንደመሹለክ ዓይነት የሥደት ምርጫ፡፡ ከአ/አበባ ጅጅጋ፣ ከጅጅጋ ቦሳሶ ሶማሊያ፣ ከቦሳሶ የመን፣ በየመን ደግሞ ሌላ የስደት መከራ…የነፍስ ውጪ ነፍስ ግቢ ትረካው ይቀጥላል፡፡ በርሃ ለበርሃ በእግር ጉዞ እያቆራረጠ፣ በባህር ብቅ ጥልቅ እያለ፣ እየሰመጠ፣ የገፋውን የሥደት ህይወት እያንገሸገሸው ይነግረናል፡፡
    ጋዜጠኛ ተስፋዬ ገ/አብ የዳንኤልን ታሪክ አንብቦ ከመፅሐፉ ጀርባ ያሰፈረው አስተያየት ሁኔታውን ጠቅለል ባለ መልኩ ቅልብጭ አድርጎ የሚያሳይ ይመስለኛል፡፡ እነሆ የተስፋዬ ገ/አብ አስተያየት፡-
    “…ዳንኤል ገዛኸኝ ትረካውን ሲጀምር ‘ብታምኑም ባታምኑም እኔ ከሞት ጋር ተያይቻለሁ፤ ሞትን ተመልክቻለሁ’ ይላል፡፡ ፊት ለፊት ብቻ ሳይሆን፣ መልዓከ ሞት እና ጋዜጠኛው ዳንኤል የህይወት ቁማር እየቆመሩ አብረው ሰንብተዋል፡፡ በምድርም በባህርም አብረው ተጉዘዋል፡፡ ሆኖም ተራኪው ጋዜጠኛ ከሞት ጋር ጉሮሮ ለጉሮሮ ተናንቆ አሸንፎ ለመውጣት ችሏል፡፡ ከሶማሊያ ወደየመን በተራ ኮንትሮባንድ ጀልባ ስለመጓዝ አስባችሁ ታውቃላችሁ? ዳንኤል ፈፅሞታል፡፡ እንደተደነቅሁና ልቤ እንደተሰቀለ፤ ሕንድ ውቅያኖስ ላይ በማዕበል ከምትንገላታው ከርካሳ ጀልባ ጋር እኔም አብሬ እየተንገላታሁ ታሪኩን አንብቤ ጨሻለሁ፡፡ ‘ሰው ብርቱ - ድመት ጠንካራ’ የሚባለው እውነት ኖሯል?...”
    በእርግጥም ተስፋዬ ገ/አብ እንዳለው፣ ደራሲው ጋዜጠኛ ዳንኤል ገዛኸኝ ሞትን ከአንድም ሁለት ሶስት ጊዜ ተጋፍጦታል፤ ተናንቆታል፡፡ “በሰሜን ሶማሊያ ዲሽሽ” በሚለው ርዕስ ሥር ያሰፈረውን ታሪክ ለአብነት እንኳ ብንጠቅስ ስቅቅ ይለናል፡፡ በዚያ ቅልጥ ባለ ነዲድ በርሃ ውስጥ፣ የውሃ ጠብታ ማግኘት እንደፅድቅ በሚቆጠርበት በዚያ ምድረበዳ፣ በርካታ ስደተኞች በቡድን በቡድን ሆነው እየተጓዙ ሳለ በአጋጣሚ ምንጭ አጠገብ ደረሱ፡፡ በዚያ በርሃ ድንገት ከየቁጥቋጦ ውስጥ ብቅ በሚሉ የሶማሊያ ታጣቂዎች ያላቸውን ሁሉ እየተነጠቁ ባዶ እጃቸውን የሚንከላወሱት ስደተኞች በሰቆቃ እያዘገሙ ሳለ፣ ከንፈራቸውን ለማርጠብ እየቋመጡ ሳለ አምስት ታጣቂዎች ከየት መጡ ሳይባል ከበቧቸው፡፡ ያ ምንጭ “በአቅራቢያው ከሚገኝ መስጊድ የሚመጡ ሙስሊሞች ከስግደት በፊት ‹ውዱ› የሚያደርጉበት (የሚጠቀሙበት) እንጂ የማንም ካፊር የሚያረክሰው አይደለም” አሏቸው፡- በቁጣ ክላሽ እየወደሩባቸው፡፡
    ከስደተኞቹ መሃል የእስልምና ኃይማኖት ተከታይ የሆነው ወጣት በተሳሰረ አንደበት ሙስሊም መሆኑን እየነገራቸው ተማፀናቸው፡፡ በአላህ ስም እንዲምል አፋጠጡት፡፡ አላመኑትም፡፡ ዋሽተሃል ብለው ጮሁበት፡፡ በአረብኛ ቋንቋ በእስልምና ኃይማኖት መባል ያለበትን አለላቸው፡፡ ይህ ግን የአንዱን ታጣቂ ጣት ቃታ ከመሳብ የሚገታው አልሆነም፡፡
    “…አሸሃዱ አላ…ህ … የጀመረውን ቃል ሳይጨርስ ልጁ አንገቱን መቆጣጠር ተስኖት ወደ መሬት ድፍት አለ፡፡… ከእሱ ሰውነት ጎርፎ እየሰራ የወረደው ደም እኔን ማራስ ጀምሯል፡፡…ተጠራጠርኩ፤ እኔንም የጥይቱ አረር የነደለኝ መሰለኝ፡፡…የዚያ ልጅ ደም የለበስኩትን ጃኬትና የውስጥ ልብሴን አርሶታል፡፡ …የትኛውን የአካሌን ክፍል ነድሎት ይሆን?” ይላል ጋዜጠኛ ዳንኤል ገዛኸኝ በትረካው፡፡ (ገፅ 106 - 114)
    ከሞት ጋር የገጠመው ፍጥጫ በዚህ አያበቃም፡፡ ከኢትዮጵያ ጠረፍ አንስቶ እስከ ሶማሊያ ጠረፍ፣ ብሎም በባህር ላይ በርካታ ጊዜ ከሞት ጋር ተያይቷል፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን በየበርሃው ወድቀው መነሳት አቅቷቸው አሸዋ ስር ተቀብረዋል፡፡ በዚህ የመከራ ስደት ያልተሸነፉት የመጨረሻ አቅማቸውን አሟጠው ባህር ለመሻገር መቧቸር ቀጥለዋል፡፡ በመቶ የሚቆጠሩ ከሰው ተራ የወጡ ኢትዮጵያውያን በአንዲት ከርካሳ መርከብ ተፋፍገው ወደ የመን ለመሻገር ጉዞ ጀምረዋል፡፡ ጉዞው ቀንና ለሊት ነው፡፡ ካለእረፍት በውሃ ላይ እየጋለቡ በውሃ ጥም የተቃጠሉ ኢትዮጵያውያን ውሃ ከያዙ ወገኖቻቸው በኮዳ ክዳን ውሃ በ50 ብር ለመግዛት ለምነው አጥተዋል፡፡ አየር እንኳ መሳብ ያቃታቸው ተጓዥ ስደተኞች በሞትና በሕይወት መሃከል በጣር እየቃተቱ ጉዞው ቀጥሏል፡፡ ወገን ለወገን መተጋገዝ፣ መረዳዳት እንኳ በዘር፣ በብሔርና በቋንቋ ሆኗል፡፡ ከዚህ በኋላ ያለውን ቃል በቃል ከመፅሐፉ ትረካ እንቋደስ፡-
    “…ከጉድጓድ መሳይዋ የጀልባ ክፍል ውስጥ ያሉ ልጆች ጩኸት በረከተ፡፡ ሳሚ ነገሩን ለናኩዳዎች (ለባህር አስተላላፊዎች) አስተረጎመ፡፡ እኔ ግን ማየት አልቻልኩም፤ አቃተኝ፡፡ …ጨፈንኳቸው፡፡ ወዲያው የዘጋኋቸውን ዓይኖቼን ገለጥኳቸው፡፡ ልጆቹን ከውስጥ ተረዳድተው አውጥተው ወደ ባህሩ ወረወሯቸው፡፡ ጣሰው ‹አለ፤ አለ…አንደኛው አልሞተም፤ ነፍሱ አልወጣችም፤ ሩሁ ገና ነች›” አለ፡፡ የሚሰማው አልነበረም፡፡ ልጁ (ወደ ባህሩ የተወረወረው) ዓይኖቹ እንደተከፈቱ ናቸው፡፡…ከሁሉ በላይ የሚያስፈራው ሞት አይደል እንዴ? ሕዝባችንን እንዴት ጨካኝ ሆነ?...” (ገፅ 163) ይላል ዳንኤል በትረካው፡፡ ዳንኤል ሕዝባችን እንዴት ጨካኝ ሆነ ሲል የሚጠይቀው ነፍሱ ከስጋው ያልተላቀቀችውን ሰው ወደባህር የሚወረውሩት ኢትዮጵያ ወገኖቹ በመሆናቸው ነው፡፡፡
    ከዚህ በላይ ሞትን መጋፈጥ ከዚህ፤ በላይ የሞት ሞት ምን አለ? በዚያ የሥደት የጣዕር የስደት ጉዞ ውስጥ አንዲት ኢትዮጵያዊ ወጣት ከአንድም በሁለት ሶማሊያውያን የባህር አስተላላፊዎች ፊት ለፊታቸው ስትደፈር ማየቱን ይነግረናል፡፡ ይህንን ማየት በራሱ የሞት ሞት አይደል እንዴ? ከዚህ በላይ ኢትዮጵያዊ ስብዕናን ማጣት፣ ከዚህ በላይ ውርደት ምን አለ? ይህንን ሁሉ ግፍ እና መከራ የምንጋትበት ምክንያት ምንድነው?
    ደራሲው ጋዜጠኛ ዳንኤል በመፅሐፉ ውስጥ የሚተርከው ወደ 500 የሚጠጉ ኢትዮጵያውያንን የሥደት ሥቃይ ነው፡፡ መነሻው የእሱና የሙያ ጓደኞቹ የሥደት ጉዞ ቢሆንም፤ አጠቃላይ ይዘቱ የኢትዮጵያውንን መከራ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው፡፡
    የሞተው ሞቶ፣ የተረፈው ተርፎ የየመንን ምድር ከረገጡ በኋላ የሊገጥማቸው ሥቃይ ከሬት በላይ የሚጎመዝዝ ነው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ ሃገር ጥለው በሥደት የመከራ ሕይወት ውስጥ የሚቃትቱት ኢትዮጵያውያን በብሔር፣ በኃይማኖት፣ በፖለቲካ አመለካከት ተቧድነው እርስ በር መጠላለፋቸው ነው ይበልጥ የሚያሳዝነው፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ማነን? በመከራ ሰዓት እንኳ የማንስማማ ምንድነን? ምን ዓይነት ልክፍት ነው የተጣባን የሚያሰኝ ነው፡- “ሲ ዋን” መፅሐፍ፡፡
    በነገራችን ላይ ደራሲው ለመፅሐፉ የሰጠው “ሲ ዋን” የሚለው ርዕስ ከዕብራይስጥ ቋንቋ የተወሰደ ሲሆን፣ ትርጉሙ ግንቦት የሚል እንደሆነ በመግቢያው ተጠቅሷል፡፡ ይህ የርዕስ ሥያሜ ግን ለዚህ ዳሰሳዊ ፅሁፍ ጦማሪ አልተዋጠለትም፡፡ የመፅሐፉን የመነበብ ዕድል በእጅጉ የሚያኮሰምን የርዕስ አመራረጥ ነው ብሎ ያምናል፡፡ በውስጡ ከያዘው መራር ዕውነት አኳያ ርዕሱ ገላጭነት የለውም ብሎ ያምናል፡፡
    እንደ እኔ እንደእኔ የመፅሐፉ ርዕስ “የግንቦት ልባቦት” ቢባል የበለጠና የተሻለ ትኩረት ይሰጥ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡ ምክንያቱም ዳንኤልና የሙያ ጓደኞቹ የስደት ምክንያት በወርሃ ግንቦት ተካሄዶ የነበረው ምርጫ ነው፡፡ ግንቦት ለእነዳንኤል ስደት ምክንያት የሆነው የኢህአዴግ መንግስት ስልጣን የተቆናጠጠበት ወር ነው፡፡ ግንቦት ከወራት ሁሉ እጅግ ሞቃታማ ወር መሆኑን “ልባቦት” የሚገልፀው ቃል ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በመፅሐፉ ውስጥ የተካተቱት ትርክቶች ሁሉ የግንቦት ወር ፖለቲካዊ ሙቀት የፈጠራቸው ተግዳሮቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ “የግንቦት ልባቦት” ቢባል የበለጠ ገላጭ ርዕስ በሆነ ነበር ብዬ አምናለሁ፡- ያውም ከነኢትዮጵያዊ የቋንቋ ለዛና ኃያልነት ጋር፡፡
    ከዚህ ውጭ የጋዜጠኛ ዳንኤል ገዛኸኝ “ሲ ዋን” መፅሐፍ በ279 ገፆች የያዛቸው ጉዳዮች የኢትዮጵያን እና የኢትዮጵያዊነትን ተግዳሮቶች ነቅሶ የሚያሳይ፤ ራሳችንን እንድንፈትሽና እንድንመረመር ግድ የሚል፤ መርመረንም መፍትሄ እናበጅለት ዘንድ የሚሞግት የተዋጣለት ሥራ መሆኑን መመስከር ግድ ነው፡፡ ለዛሬው በዚሁ እንሰነባበት፡፡ ቸር ክራሞት!!