Sunday, April 14, 2013

የኢሳት 3ኛ አመት ክብረ-በዓል የሙስሊሞች ብቻ ነው እንዴ? ስለክብረ-በአሉ እንግዶች፤ ስለመንግስትና ሀይማኖት መለያየት፤ ልጅ ተክሌ


1-ጽሁፍ ካላበሳጨ ወይ ካላስጨበጨበ አይመቸኝም። ላለፉት ጥቂት ሳምንታት የሚያበሳጭ ወይ የሚያስጨበጭብ ርእስ ስጠብቅ ሳልጽፍ ቆየሁ። የኢትዮጵያውያን፤ በተለይም የአማርኛ ተናጋሪ፤ ኢትዮጵያዊያን ከቤንሻንጉል መባረር በራሱ በቂ አናዳጅና አሳዛኝ ክስተት በመሆኑ፤ እንዲሁም ሌሎች ስለጻፉበት እሱ ላይ ብዙ አልደክምም። ስለዚህ ሌላ አናዳጅ ርእስ ናፈቅኩ። እነሆ ባያናድድም፤ ምን ነካቸው የሚያስብል ርእስ ከኢሳት አገኘሁ።
2-ባለፈው ሰኞ፤ ከአድካሚው ውሎዬ እረፍት ለመውሰድ ወደኢሳት ድረ-ገጽ አመራሁ። የደንቡን አድርሼ ከኢሳት ድረገጽ ወጥቼ ለመሄድ ጣቴን ጠቅ ለማድረቅ ስንቀለቀል፤ በአይኔ የቀኝ ጠርዝ፤ በኢሳት ድረገጽ የግራ ማእዘን ላይ፤ ስድስት ሰባት ወንዶች የተደረዱበት ምስል አየሁና ተመለስኩኝ። አንዳንዶቹ የተለመዱ ፊቶች ናቸው። “ሲሳይ አጌና፤ ታማኝ በየነ፤ ሻምበል በላይነህ፤ ሄኖክ የሺጥላ …”። ሌሎቹ ግን በቃለምልልስ ካልሆነ በስተቀር፤ ከኢሳት ጋር በተያያዘ ለሚደረግ ዝግጅት አዳዲስ ናቸው። የኢሳት ሶስተኛ አመት ዝግጅትን ለማድመቅ የተመረጡ እንግዶች ናቸው። የሚያበሳጭም ባይሆን፤ እነሆ የሚያወያየው ርእስ የነዚህ ሰዎች ለእንግድነት መመረጥ ነው።
3-ከኤፕሪል 13 እስከ ሜይ 26 የኢሳት 3ኛ አመት ክብረበዓል በተለያዩ ከተሞች ይካሄዳል። ነጂብ ሞሀመድ፤ ከታማኝ በየነና ሄኖክ የሺጥላ ጋር ቅዳሜ ሎስ አንጀለስ ይገኛል። እሁድ እዚያው ሳንዲየጎ ይጓዛሉ። እነዚሁ ሰዎች።ታማኝ በየነና ሻምበል በላይነህ ካሊድ ኦማርን ይዘው እሁድ ኤፕሪል 20 ሳን ሆዜ ይገኛሉ። ታማኝ በበነጋው እሁድ ኤፕሪል 21 መንሱር ኑርን ይዞ ሲያትል ይታያል። ነጂብና ታማኝ እንደገና እሁድ ኤፕሪል 28 ናሽቪል፤ ቴነሲ ይገኛሉ። ጃክሰንቪል ፍሎሪዳ ታማኝና ሻምበል ሜይ 18 ይገኛሉ። በስድስት ከተሞች በሚካሄዱ የኢሳት ዝግጅቶች ላይ አምስት የሙስሊም የሀይማኖት መሪዎች የመጋበዙ አመንክዮ ትንሽ ግራ አጋብቶኛል? በኔ አስተያየት፤ ኢሳት የሁሉም ኢትዮጵያውያን ከሆነ፤ ነውም፤ በኢሳት ሶስተኛ አመት ዝግጅቶች ላይ ከስድስቱ ከተሞች ውስጥ በአምስቱ የሙስሊም ሀይማኖት መሪዎች ዋንኛ ተጋባዥ እንግዶች መሆናቸው ብልሀት ያነሰውና ያልተጠና ነው። ይሄ አካሄድ ያለውን ፖለቲካዊ አንድምታና የሚያስተላልፈውን መልእክት የኢሳት አስተዳደር የተረዳው አልመሰለኝም።
4-ሙስሊም ኢትዮጵያዊያን፤ በተለይም በአገር ቤት ያሉቱ የሚያደርጉትን ሰላማዊና በሳል ትግል ብደግፍም፤ የኢሳት 3ኛ አመት ዝግጅት ግን ሀይማኖታዊ አንድምታ በሚኖረው መልኩ መሆኑ ትክክል አይመስለኝም። ምክንያቱም ኢትዮጵያዊያን ዜግነትን ሳይሆን ሀይማኖትን መሰረት አድርገው እንዲደራጁ የማበረታታት ተጽእኖ ያሳድራልና።ሙስሊሞች ባንድ በኩል ሙስሊሞች ለመብታቸው መታገላቸው የሚደገፍ፤ የሚያስቀና፤ የሚኮረጅ ነው። ሙስሊሞችም ይሁኑ ሌሎች በሀይማኖት ዙሪያ የተደራጁ ሀይሎች በኢትዮጵያ ውስጥ እንደአንድ ፖለቲካዊ ጎራ ወይም ቡድን ይታዩ፤ ወይንም እንደ አንድ ፖለቲካዊ ቡድን (Political Block) ሆነው እንዲወጡ እናበረታታቸው ወይንም እውቅና እንስጣቸው የሚለውን ሀሳብ በጽኑ እቃወመዋለሁ። እንደዚያ ብለው የሚያስቡ ሙስሊሞችም ሌሎች ኢትዮጵያዊያንም ሊኖሩ ይችላሉ። ኢሳት ግን ሙስሊሞችንም ይሁን ማናቸውንም የሀይማኖት ድርጅት ፖለቲካዊ ሀይል አድርጎ በሚያወጣ ጉዞ ውስጥ አባል መሆን የለበትም ብዬ አምናለሁ። ዜግነትን መሰረት አድርጎ የሚንቀሳቀስ እንደኢሳት ያለና ብዙዎቻችን በሀይማኖታችን ሳይሆን በዜግነታችን የተከተልነው ተቋም አንዱ ላይ አይደለም፤ ሁለቱም ላይ አይደለም፤ አምስት ዝግጅቶች ላይ የሙስሊም ሀይማኖት መሪዎችን ነጥሎ መጋበዙ ምን ማለት እንደሆነ አልገባኝም።
5-አንዳንድ በጓዳ ብቻ የምንላቸውን ነገሮች በጨዋ ደንብና በሰለጠነ መንገድ እስከሆነ ድረስ በአደባባይም መነጋገር አለብን። ብዙዎቻችን በኢሳትም በኩል ይሁን በሌላ መስመር የሙስሊሞቹን ትግል ብንደግፈም፤ ድጋፋችን የሚቀጥለው ግን የኛን ብሄራዊ የጋራ ትግል እስካገዘና፤ በመጨረሻ እንደ ሀይማኖት ቡድን የሚያደርጉት ትግላቸው በኛ የጋራ ጥቅም ላይ ችግር እስካልጋረጠ ድረስ ነው። የሙስሊሙ አንድ ወጥ ፖለቲካዊ ሀይል ሆኖ መውጣት፤ ሀይማኖታችንን ሳይሆን ዜግነትን ብቻ መሰረት አድርገን ለምንንቀሳቀስ ሀይሎች ጠንቅ ነው። በተለያየ ሀይማኖት ተከታዮች መካከል ያለውን አለመተማመንና ጥርጣሬም ያባብሳል። በስድስት ከተሞች ከሚካሄዱ ስድስት የኢሳት 3ኛ አመት ልደት ዝግጅቶች ላይ በአምስቱ ላይ፤ ኢሳት ሙስሊሞችን ብቻ እንግዶች አድርጎ መጋበዙ የኢሳትንም ጥቅም በሀይማኖቶች መካከል ያለውን ጥርጣሬና ፍራቻም ከግምት ያስገባ አይደለም።
6-የሙስሊሞቹን ትግል ስንደግፍና ከሙስሊሞቹ ጎን ስንቆም፤ ሀይማኖትና መንግስት የተለያዩ ናቸው፤ መንግስት Secular ይሁን፤ የሚለውን መሰረታዊ የፖለቲካ መርህ አምነንበት፤ የመንግስትን ጣልቃገብነት በኦርቶዶክሱም ሆነ በእስልምናው ሀይማኖት ስለቀመስነው ነው እንጂ፤ የሙስሊሞች አንድ ፖለቲካዊ ሀይል ሆኖ መውጣትን ተቀብለነው አይመስለኝም። መንግስት በማናቸውም ሀይማኖቶች ጉዳይ ገብቶ መፈትፈት የለበትም ከሚለው መሰረታዊ ሁላችንንም ከሚያስማማ የሰለጠነ ሀሳብ በመነሳት ነው። እንጂ ሙስሊሞች ተደራጅተው፤ አንድ የፖለቲካ ሀይል እንዲሆኑ የማድረግ ፖለቲካዊና አገራዊ ግዴታ አለብን ከሚል የሀላፊነት ስሜት በመነሳት አይደለም የሙስሊሙን ትግል የምንደግፈው።
7-እንግዲህ ጫፍ ጫፉን እንደሰማሁት ከሆነ፤ የኢትዮጵያ ተራማጆች መንግስትና ሀይማኖት ይለያዩ ሲሉ ትግል የጀመሩት ከዛሬ 50-60 አመታት በፊት ነበር። ያ ትግላቸው ተሳክቶ መንግስትና ሀይማኖት ካለፈው የ66 አብዮት ጀምሮ ተለያይተው ከርመውም ነበር። እነሆ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ በሁዋላ፤ ላለፉት 20 ምናምን አመታት ደግሞ መልሶ ከሀይማኖት ተቋማት ጉያ አልወጣም ብሏል። አሁንም መንግስትና ሀይማኖት ይለያዩ፤ መንግስት በሙስሊሞች ጉዳይ ጣልቃ አይግባ ስንል ያ ብዙ ወጣት ኢትዮጵያውያን የሞቱለት መርህ ይከበር ማለታችን ነው። መንግስት በኦርቶዶክሱም ይሁን በሙስሊሙ፤ በመጅሊስም ይሁን በሲኖዶስ፤ ጣልቃ አይግባ ማለታችን ነው። በሙስሊሙም አይግባ ስንል፤ መንግስትና ሀይማኖት አይለያዩ ማለታችን ነው እንጂ ሙስሊሞች ወይም የማናቸውም ሀይማኖት ተከታዮች ፖለቲካዊ ሀይል ሁነው ይውጡ ማለታችን አይደለም።
8-ይሄ የአምስቶ ከተሞች የሙስሊም መሪዎች ብቻ እንግዶች ሆነው የሚገኙበት አካሄድ ግን፤ ሙስሊሞች ተጽአኖ መፍጥር የሚችሉ አንድ ትልቅ የፖለቲካ ቡድኖች አድርጎ የመፍጠር አዝማሚያ የያዘ ነው። ያ አንደኛ መንግስትና ሀይማኖት ይለያዩ የሚለውን መርህ ይሽራል፤ ምክንያቱም ሀይማኖት በመንግስት ጣልቃ እንዲገባ ሊያደርግ ይችላልና። ሁለተኛ፤ ያንን ሚዛናዊ የሚያደርግ ወይም የሚፎካከር ጠንካራ የኦርቶዶክስም ይሁን የፕሮቴስታንት ድርጅት በሌለበት ሁኔታ፤ በኢትዮጵያ ውስጥ የሙስሊሞች ብቻ ሀይማኖትን መሰረት ያደረገ ጠናካራ የፖለቲካ ጎራ ሆኖ መውጣት ለኢትዮጵያ አደጋ ይጋብዛል። ኢሳትም፤ በሙስሊሞች ላይ የሚደርሰውን በደልና ግፍ ከመዘገብና ከማጋለጥ አልፎ፤ አስተዳደሩ ሙስሊሞችን ብቻ የክብር እንግዳ አድርጎ ወደመጋበዝ ሲያመራ ማንም ህጻን ሊያደርገው የማይሳነውን ጥንቃቄ ማድረግ አለበት።መንገስት ሴኩላር ይሁን ስንል፤ ይሄንን መንግስት ለመጣል የምፈልግ ሀይሎችም ሴኪውላር መሆን አለብን። እንጂ፤ የምንሰራው ስራ በሀይማኖታዊ አንድምታ እንዲተረጎም አድርገን መሆን የለበትም።
9-የኢሳት ሶስተኛ አመት ክብረበኣል ስግጅቶች ላይ ከስድስቱ ከተሞች በአምስቱ የተጋበዙት፤ ከታወቁቱ መደበኛ እንግዶች በስተቀር፤ በአትሌትነት፤ በሯጭነት፤ በሙዚቀኛነት፤ በደራሲነት፤ የማንንም ሀይማኖት በማይወክል በፖለቲካ መሪነት አይደለም የተጋበዙት። በጎበዝ የሀይማኖት መሪነታቸው የምናውቃቸው ሙስሊሞች ከሚኖሩበት ከተማ ውጪ በክብር እንግድነት ኢሳትን ወክለው መጋበዛቸው ብዙዎችን ግራ ሊያጋባ፤ ሊያሸሽም ይችላል። እነዚህን ሰዎች በመጋበዝ ልናመጣ ያሰብነው ትርፍ፤ በግልጽ ላንሰፍረው የማንችለው ትልቅ ኪሳራ እንደሚያመጣብን፤ አደገኛ አካሄድ እንደሆነም አላስተዋልንም የሚል ራእይ ተገልጾልኛል። ተደርጎ ቢሆን ኖሮ፤ የጋዜጠኛው ሳዲቅ መጋበዝ አይከነክንም። በጋዜጠኝነት ኢሳትን ሲረዳ የቆየ ሰው ነውና፤ ልክ ሲሳይ በአጋጣሚ ለኢሳት የሚሰራ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ጋዜጠኛ እንደሆነው ወይንም ታማኝ ለኢትዮጵያ የቆመ ኢሳት ውስጥ የሚሰራ ክርስቲያን እንደሆነው፤ ሳዲቅም በቅጥርም ባይሆን በፈቃደኝነት ለኢሳት የሚያገለግል ሀይማኖቱ እስልምና የሆነ ጋዜጠኛ ነው። አሁን የሆነው ግን ያ አይደለም።
10-የነጂብና የኦማር፤ እንዲሁም የመንሱር ሁኔታ ግን ግራ ገብቶኛል። በግሌ ከነጂብም ይሁን ከማናቸውም ሙስሊሞች ጋር ምንም ችግር የለብኝም። ዞሮ ዞሮ ግን ነጂብና ካሊድ የሀይማኖት መሪ ናቸው። ነጂብ የፈርስት ሂጅራ ፋውንዴሽን። ከዚህ ቀደም የሚጋበዙትም ይሁን አሁን እነሱን የሚያጅቡት የኢሳት ሰዎች ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ወክለው ነው የሚመጡት ከሚል ግምት ካልተነሳን፤ ወይንም እነታማኝና ሌሎች “ሜይንስትሪም” የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ኦርቶዶክሱን ይወክላሉ የሚል ያልተጻፈ ግምት ከሌለ በስተቀር፤ ታማኝም ይሁን ሻምበል፤ አበበ ገላውም ይሁኑ አበበ በለው ለኢሳት ዝግጅቶች የሚገኙት በዜግነት እንጂ በሀይማኖት አይደለም። ኦርቶዶክስን ወክለው አይደለም። ስለዚህ የሄኖክና የታማኝ፤ የሻምበልና የሲሳይ መገኘት የሙስሊም ሀይማኖት መሪዎችን መገኘት አያካክሰውም።
11-ወዳጄ ታማኝ፤ ከዚህ ቀደም በስህተት ሙስሊሞቹን የካሰ መስሎት በልጅነቱ የክርስቲያኑ በኣል ሲከበር ስለሙስሊሞች በአል አለመከበር የተናገረው ንግግር በየዋህነት ቢታለፍም፤ በምንም መልኩ ግን ታማኝ እንደ ኢትዮጵያዊ እንጂ የክርስትና እምነት ተከታዮችን ወክሎ የሰነዘረው የይቅርታ ንግግር አይመስለኝም። እኔና ታማኝ ኦርቶዶክሶች ብንሆንም ኦርቶዶክሶችን አንወክልም። እኔ እስከማውቀው ድረስ፤ እነ ነጂብ ትናንትም ዛሬም ከኢሳትም ጋር ያገናኛቸው የሀይማኖት መሪዎች መሆናቸው ነው። የሀይማኖት መሪዎች ከጋበዝን ደግሞ ቢመጡም ባይመጡም የኦርቶዶክሱንም የፕሮቴስታንቱንም፤ የይሁዲውንም፤ የካቶሊኩንም ነው እንጂ፤ በምን መስፈርት ነው የሙስሊሞቹን ብቻ የምንጋብዘው? ይሄ አደገኛና መታረም ያለበት አካሄድ ነው።
12-እንደምረዳው፤ እንደሚመስለኝም፤ ኢሳት የሙስሊሞቹን እንቅስቃሴ ሌት ተቀን የሚዘግበው፤ በሙስሊም ኢትዮጵያዊያን ላይ በመንግስት የሚፈጸመው ኢፍትሀዊነት ሁሉንም ኢትዮጵያዊና የሰው ልጅ ስለሚመለከት ነው እንጂ፤ ብዙዎች የነቁም ያልነቁም የሙስሊሙን እንቅቃሴና አካሄድ በጥርጣሬ የሚመለከቱ ስጋት የገባቸው ኢትዮጵያዊያን የሉም ማለት አይደለም። ያንን እኔ ራሴ ሌላው ቢቀር ኢሳት ውስጥ በምሰራበት ወቅት ከሚደርሱን የስልክና የኢሜል መልእክቶች እረዳለሁ። በዚህ ሁኔታ ውስጥ እንደ ኢሳት ያለ ለሁሉም ኢትጵያዊያን በእኩልነትና ፍትሀዊነት ላገለግል ቆሜያለሁ የሚል ተቋም፤ ዝግጅቶችን ሲያዘጋጅ በክብር እንግድነት ስለሚጋብዛቸው ሰዎች ማንነትና በህዝብ ዘንድ ሰለሚፈጥሩት ስሜት ጥንቃቄ ማድረግ አለበት። ከስድስት ዝግጅቶች በአምስቱ ላይ እነ ነጂብን ሲጋብዝ ሊፈጥር የሚችለውን አንድምታ፤ ሊያሸሽ የሚችለውን ህዝብ ማሰብ አለበት። ኢሳት ደግሞ የሙስሊሞችና የኦርቶዶክሰቶች ብቻ ሳይሆን፤ ለአገር ያላቸው ተቆርቋሪነት ጎዶሎ ቢሆንም እንኳን፤ የጴንጤዎችም ጭምር ነው። ወይም ነው ብለን ነው ማሰብ ያለብን። ዝግቶቹ በተለያየ አጋጣሚ የተዘጋጁ ቢሆኑ አይገርምም። ነገር ግን ሆን ተብሎ ባንድ ላይ ታስቦበት ይሄንን ቅርጽና አንድምታ እንዲይዝ የተዘጋጀ ይመስላል።
13-መቼም በነካ እጄ ለመጨመር ያህል፤ ከላይ እንዳልኩት፤ መንገስት ሴኩላር ይሁን ስንል፤ ይሄንን መንግስት ለመጣል የምፈልግ ሀይሎችም ሴኪውላር መሆን አለብን ማለቴ ነው። እንጂ፤ የምንሰራው ስራ በሀይማኖታዊ አንድምታ እንዲተረጎም አድርገን መሆን የለበትም። በመሰረቱ የሀይማኖት ስራ በሰውና በእግዚአብሄር መካከል ያለውን ግንኙነት የሚመለከት ነው፤ የፖለቲካ ዓላማ ደግሞ በሰውና በሰው መካከል ያለውን ግንኙነት የሚመለከት ነው። የተለያዩ ሀይማኖት ተከታዮች ባሉባት አገር፤ ሀይማኖት የሰውና የሰውን ጉዳይ እንዲዳኝ መጋበዝ የለብንም። ሀይማኖት በሰውና በሰው መካከል ያለውን ግንኙነት የሚዳኘው ፖለቲካ ላይ ተጽእኖ ማሰደር ሲጀምር ነው። ተጽእኖ አሳዳሪውን ሀይማኖት (በኛ አገር፤ እስልምናን ሊሆን ይችላል) የሚገዳደር ወይም የሚያርቅ በሌላ ሀይማኖት ዙሪያ የተደራጀ ሀይል (ምሳሌ ኦርቶዶክስ ወይንም ፕሮቴስታንት) ከሌለ፤ የዚያ ተጽእኖ ፈጣሪ ሀይማኖት (እስልምና) አንድ ወጥ በሀይማኖት ዙሪያ የተሰባሰበ ሀይል ወይም ቡድን ሆኖ መውጣት ለሁላቸንም አደጋ ነው። ኢሳት ያንን አደጋ መከላከል እንጂ ማበረታተት የለበትም።
14-መቼም የሆነ ሆኗል፤ ድስት ተጥዷል፤ ጠላም ተጠምቋል፤ ጠጅም ተጥሏልና፤ የተጋበዙት ሰዎች ይሰረዙ፤ ወይንም አቡነ ፊሊጶስን ፈልጋችሁ ደባልቁ ብለን አንጮህም። ይሁን እንጂ፤ ለወደፊቱ ይሄ እንዳይደገም ጥንቃቄ ያስፈልጋል። ያለበለዚያ የምንቆጣም እንኖራለን።
15-ለነገሩ፤ እሁን እነ ሌንጮ ለታ፤ እነ ዲማ ነጎ፤ ይሄን የመሰለ ፖለቲካዊ ጮማ አዋጅ ይዘው አንድነታችን ደጅ ላይ ቆመው፤ እጣ ፈንታችን የሚወሰነው ከኢትዮጵያዊነት ታዛ ስር ነው እያሉ አዋጅ ሲነግሩ፤ ሲሆን ሲሆን ለቀጣዮቹ ወራት እነሱን ብቻ፤ ካለበለዚያም ከሌሎች ጋር እየቀየጥን የአገራችንን ነገር መምከር ነበር እንጂ፤ ሀይማኖታዊ መሪዎች ላይ ማተኮር አልነበረብንም። ለወደፊቱ ጥንቃቄ ይደረግ። የኢሳት አስተዳደርን ለዛሬ ምረነዋል። ለወደፊቱ ይታረም።
እኛው ነን። ታሰበ፤ ተጻፈም፤ በአገረ-ካናዳ፤ ቶሮንቶ፤ ሚያዚያ፤ 2005/2013