Wednesday, May 15, 2013

ከሙስናው በስተጀርባ (ከኢየሩሳሌም አርአያ)


ሙስናው በስተጀርባ (ከኢየሩሳሌም አርአያ)

ከኢየሩሳሌም አርአያ
በሕወሐት የተፈጠረው የቀውስ ማእበል አድማሱን እየለጠጠ መሔዱን ተከትሎ «ታማኝ» ሆነው በሙስና ሲያገለግሉ የቆዩትን ጭምር እየበላ እንደሚገኝ የቅርብ ምንጮች አስታወቁ። በቀዳሚነት የሚያነሱት በጉምሩክ ቁልፍ ስልጣን የነበረውን የሕወሐት አባል ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ሲሆን እንዴትና በማን ወደስልጣን እንደመጣ እንዲሁም ምን-ምን ተግባራት ይፈፅምና ያስፈፅም እንደነበረ ምንጮቹ ሂደቱን እንደሚከተለው ይገልፁታል።tplf rotten apple
ገ/ዋህድ በ1993ዓ.ም ፓርቲው ለሁለት መሰንጠቁን ተከትሎ ወደ ስልጣን እንዲመጣ ተደረገ። ከጉምሩክ ሃላፊነት በተጨማሪ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተርነት ስልጣን እንዲጨብጥ የተደረገው በአቶ መለስ በተለይ በአዜብ ይሁንታ ጭምር እንደነበረ ምንጮቹ ይጠቁማሉ። ገ/ዋህድ ለዚህ ስልጣን የበቃው ለአቶ መለስ ቡድን በከፈለው መስዋእትነት ሲሆን በክፍፍሉ ማግስት የሙስና ዘመቻ ተከፍቶ እነአባተ ኪሾና ሌሎች እስር ቤት እንዲገቡ ቀጥተኛ ትእዛዝ ከመስጠት አንስቶ ራሱ ክስ አዘጋጅ፣ምስክርና ፈራጅ..በመሆን የላቀ ሚና መጫወቱን ያስታውሳሉ። በዚህ ተግባሩ የበለጠ ታማኝነቱን በማሳየቱ ከአዜብ በሚሰጠው ቀጥታ ትእዛዝ ሙስናውን ማከናወን መቀጠሉን ምንጮቹ አያያዘው ይጠቁማሉ። በ10ሺህ ቶን የሚገመት ቡና ከአዜብ በተቀበለው ትእዛዝ በህገወጥ መንገድ ከአገር ተዘርፎ የተሸጠበትና ጉዳዩም በፓርላማ ተነስቶ በጠ/ሚ/ሩ «የሌቦቹን እጅ እንቆርጣለን» የሚል አስቂኝ ምላሽ መሰጠቱን ያስታውሳሉ። በተጨማሪ በጉምሩክ ለረጅም አመት በመምሪያ ሃላፊነት ሽፋን የተቀመጠውና የቢሮውን የበላይ ሃላፊዎች በጥብቅ ከመቆጣጠር ጀምሮ እያንዳንዱን የሙስና ተግባር ከጀርባ ሆኖ የሚያስፈፅመው የአዜብ የቅርብ ስጋ ዘመድ ፍትሃነገስት ክንደያ እንደሚጠቀስና ግለሰቡ ቀረጥ ያልተከፈለባቸው 500 ሳተላይት ዲሾች እንዲገቡና በአዜብ በበላይነት ይመራ ለነበረው የዘረፋ ቡድን ለሰባት አመታት በየወሩ 20ሚሊዮን ከቴሌ በህገወጥ መንገድ እንዲዘረፍ ያደረገና በኋላም ከነገ/ዋህድ ጋር ሆኖ በርካታ ሙስናዎችን በዋናነት በማስፈፀም እንደሚጠቀስ ያመለክታሉ።
በሌላም በኩል የገ/ዋህድ ባለቤት ኰ/ል ሃይማኖት ስትጠቀስ ከሕወሐት አንጋፋ ሴት ታጋዮች አንዷ ናት፤ ከጡረታ ጋር በተያያዘ ከመከላከያ በመልቀቅ በአዜብ የበላይነት በሚመራው የሴቶች እና ኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ቢሮ መስራት ቀጠለች። ለዚህ ቢሮ ከአሜሪካ መንግስት ብቻ በአመት እስከ 240ሚሊዮን ዶላር ይለገሳል። ገንዘቡ ለሚመለከታቸው ወገኖች ሳይሆን የሚውለው የነአዜብ ኪስ ማደለቢያ ሆኖ እንደሚዘረፍ ያመለከቱት ምንጮች ይህም ጉዳይ በፓርላማ ለቀድሞ ጠ/ሚ/ር ተነስቶ « ከእንግዲህ ቁጥጥር እናደርጋለን» የሚል የተድበሰበሰ ምላሽ እንድተሰጠ ያስታውሳሉ። ባልና ሚስቱን በተለያየ ወጥመድ በማስገባት የሙስና ጋሻ-ጃግሬ አድርገው የቆዩት አዜብ እንዲሁም ሌሎቹ ቱባ ባለስልጣናት መጠነ-ሰፊ ዘረፋና ሙስና ጉዳይ ሳይነካ ግልገሎቹን ብቻ (ያውም በአስፈፃሚነት ራሳቸው የመደቧቸውን) ተጠያቂ ማድረግ ተራ ድራማ ነው ሲሉ ምንጮቹ ያጣጥሉታል። በማስረጃነትም፥ 400 ሚሊዮን ብር ለ«ራዲሰን ሆቴል ግንባታ» በሚል ሽፋን በመፍቀድ 150ሚሊዮን ኪሳቸው ከከተቱትና በርካታ ብድሮችን በመፍቀድ (የስጋ ዘመዶቻቸውን ደላላ በማድረግ…) በሙስና የደለቡት አባይ ፀሃዬ ጨምሮ፣ የበታች ሙሰኞች ላይ <ምስክር> ሆነው የቀረቡትና ከአዜብ ጋር በሙስና የሰከሩት አባዱላ ገመዳ፣ የተለያዩ ድርጅቶች ባለቤት ስብሃት ነጋ፣ የቱጃሩን የቢሊዮን ብድር በግል ከመፍቀድ አንስቶ የታዋቂ ባለሃብቶች <ቀኝ እጅ> የሆኑትና ሚስታቸውን ጭምር በሙስና ያሰማሩት በረከት ስምኦን፣ ሶፍያን አህመድ፣ እንዲሁም ቪላዎችን ከ8 እስከ 10 ሚሊዮን ብር ወጪ በማስገንባትና በማከራየት የአገር ሃብት የሚዘርፉ ሁሉም የገዢው ትላልቅ ባለስልጣናት የሙስና ጉዳይ በዋቢነት ይጠቅሳሉ። ባጠቃላይ የስርአቱ ቁንጮዎች የሚያናቁራቸው የገዛ ጥቅምን ከማስጠበቅና አንዱ ጎራ ከሌላው በልጦ በሙስና የሚከብርበትን መንገድ ለማመቻቸት ብሎም ሌላኛውን በመጨፍለቅ ስልጣኑን ከነታማኝ ተከታዮቹ አስጠብቆ የሚቀጥልበትን ብቻ እንደሚያልም የጠቆሙት ምንጮቹ፣ ስርአቱ የአስተዳደር፣የፖለቲካ፣ የፖሊሲ…ወዘተ ልዩነት እንደሌለበት ያሰምሩበታል።
ሌላው ዘብጥያ የወረዱት ባለሃብት አቶ ነጋ ገ/እግዚያብሄር ናቸው፤ የአቶ ነጋ ባለቤት የቀድሞ የሜጋ ኪነጥበብ ሃላፊ እቁባይ በርሄ እህት ናት። ከጥቂት ወራት በፊት ከሙስና ጋር በተያያዘ አስገራሚ ፍርድ የተሰጠውና ጥፋተኛ ተብሎ የተለቀቀው እቁባይ ያንን አይን ያወጣ «ፍርድ» እንዲያገኝ የተደረገው ከአዜብ በተሰጠ ቀጭን ትእዛዝ ነው ያሉት ምንጮቹ ይህ ሊሆን የቻለው አዜብ ከአቶ ነጋ ጋር ባላቸው የቢዝነስ ትስሥር ጭምር መሆኑን አያይዘው ይገልፃሉ። (ሌላም አሳፋሪ ቁርኝት ቢኖራቸውም ለጊዜው ማለፍ ይመረጣል)…
በሌላም በኩል የስዬ አብርሃ ወንድም ምህረተአብ አብርሃ እንዲሁም አይነስውሩ አስመላሽ ወ/ስላሴ ይጠቀሳሉ፤ ምህረተአብ ከስዬ ጋር ተፈርዶበት የተለቀቀው ከአምስት አመት በፊት ሲሆን አሁን ደግሞ ከነገ/ዋህድ ክስ ጋር በተያያዘ አብሮ እንዲቀላቀል ተደርጎዋል።…. አይነስውሩ አስመላሽ (በቅፅል ስማቸው አባይ ነብሶ) በፓርላማ የሕግ ጉዳይ ቢሮን ሲመሩ የቆዩ ናቸው፤ በሕወሐት ክፍፍል ጊዜ እያለቀሱ ፓርቲው እንዳይፈርስ ሲማፀኑ እንደነበር ያስታወሱት ምንጮቹ በተለይ በአንድ ቀን ተፅፎ እንዲወጣ የተደረገውንና አንድ ሰው ለማጥቃት ሲባል ብቻ አዋጅ ሆኖ እንዲፀድቅ የተደረገውን ዋስትና የሚከለክል ሕግ ካረቀቁት አንዱ እንደሆኑ ይገልፃሉ። የአስመላሽ ባለቤት በጠ/ሚ/ሩ ቢሮ ተመድባ በፀሓፊነት የቆየችና በተለይ «ሚስጥራዊ» የሚባሉ ዶክመንቶችንና የአቶ መለስ ፅሁፎችን (በብእር ስም ይወጡ የነበሩትን ጭምር) በመተየብ በታማኝነት ስታገለግል እንደቆየች አመልክተዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በመከላከያ ጄኔራሎችና የበታች ከፍተኛ መኮንኖች ግምገማ ላይ መሆናቸው ታውቋል። ከጥቂት ወራት በፊት ለመጠቆም እንደተሞከረው የሚባረሩ ጄኔራሎች እንዳሉ መገለፁ ይታወሳል። በዚህ መሰረት ከአዜብ ጋር የከረረ ፀብ ውስጥ የገቡት ጄ/ል ታደሰ ወረደን ጨምሮ ሶስት የሕወሐትና ሁለት የብአዴን ጄ/ሎች በሳሞራ ውሳኔ መባረራቸውን ምንጮች ገልፀዋል። በቅርቡ የተጀመረውና « የመለስን ራዕይ እናስፈፅማለን» በሚል መሪ አጀንዳ የቀጠለው ግምገማ ተጨማሪ የመከላከያ የጦር አዛዦችንና የበታች መኮንኖችን ለማባረር ቅድመ ዝግጅት አድርጎ ማጠናቀቁ ታውቋል። በሳሞራ የተወሰነው ሌላው ጉዳይ ለመከላከያ ከሩሲያ የመጡ የመሳሪያ ባለሙያዎች በተለያዩ ቦታዎች እንዲመደቡ መደረጉ ሲታወቅ ይህም የሆነው « አገሪቱ ውስጥ ችግር ከተፈጠረ ልንቋቋም አንችልም » በማለት ሳሞራ ድምዳሜ ላይ በመድረሳቸውና ከአየር ሃይል አንስቶ ያለው ወታደራዊ ክፍል እምነት ሊጣልበት ባለመቻሉ እንደሆነ ምንጮቹ አስረድተዋል። የጦር ሃይሎች ጠ/አዛዥነቱ ስልጣን የጠ/ሚ/ሩ እንደሆነ ሕገ መንግስቱ ቢደነግግም ነገር ግን ለአቶ ሃ/ማርያም ይህ ስልጣን እንዳልተሰጣቸው፣ ጄ/ሎች ሲባረሩ ከእርሳቸው እውቅና ውጭ እንደሆነ፣ ውሳኔው በሳሞራ እንደሚከናወን ምንጮቹ አስረድተዋል።