Monday, August 19, 2013

ሽብርተኝነት አዋጁ፤ የጠሉትን መምቻ?

ሽብርተኝነት አዋጁ፤ የጠሉትን መምቻ?
ተመስገን ደሳለኝ
ኢህአዴግ ባለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት በስራ ላይ ካዋላቸው አዋጆች መካከል የ‹‹ፀረ-ሽብር ህጉ››ን ያህል
ያጨቃጨቀ የለም ቢባል ከእውነቱ ብዙም አልራቀም፡፡ በርግጥ ከተቃውሞ አቅራቢው አብዛኛው በደፈናው ‹‹ህጉ
አያስፈልግም›› የሚል አልነበረም፡፡ ህጉ ‹‹ሽብርተኝነት››ን የገለፀበት መንገድና አንዳንድ አንቀፆቹ ለትርጉም አሻሚ
በመሆናቸው ከስርዓቱ ባህሪ አኳያ ለፖለቲካ ጥቅም የሚውሉበት ዕድል መኖሩ አይቀሬ ነው የሚል ስጋት ነበር፡፡
የህግ ረቂቁ ለተወሰኑ የምዕራብ ሀገራት ዲፕሎማቶች ይመለከቱት ዘንድ በተሰጣቸው ጊዜም ተመሳሳይ ስጋት
ሲያነሱ፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ደግሞ ‹‹ሽብርተኝነት››ን ከየትኛውም የአለማችን ሀገር እጅግ በሰፋ መልኩ ስለሚተረጉም መሰረታዊ
መብቶችን ሊዳምጥ እንደሚችል ጠቅሶ መጽደቁን ለመቃወም ብዙ ጊዜ አልወሰደበትም፡፡
በጊዜው የግንባሩን ለዘብተኛ አመራሮች ጨምሮ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ አለም አቀፍ የመብት ተሟጋች ተቋማት፣ የምዕራብ ሀገራት
ዲፕሎማቶች፣ ጋዜጠኞች፣ ምሁራኖች… ይህ ህግ ፀድቆ በስራ ላይ ቢውል የፖለቲካ መብቶችን እና የዜጐችን ነፃነት ከመገደብ አልፎ
ስርዓቱ በአይኑ መዓት የሚያያቸውን ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች መምቻ (ማጥቂያ) ሊያደርገው ይችላል በሚል ጥርጣሬ ቢያጣጥሉትም
በነሐሴ 22/2001 ዓ.ም በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከመውጣት ሊያስቆሙት አልቻሉም፡፡
…ህጉ ስራ ላይ ከዋለ ሶስት አመት ሞቶታል፡፡ በዚህ ፅሁፍም ህጉ ከመተግበሩ አስቀድሞ የተነሱ ስጋቶች እውን መሆናቸውን እና በተግባር
ከታየው የህጉ ዓላማ ጋር አሰናስዬ ለማየት እሞክራለሁ፡፡
እንደ መግቢያ
የአፍሪካ ቀንድ ከተፈጥሮአዊው ጂኦ-ፖለቲካ አኳያ እና በአካባቢው ያሉ ሀገራትም የፈራረሰችውን ሶማሊያን ጨምሮ ለጽንፈኛ የእስልምና
እንቅስቃሴ የተጋለጡ መሆናቸው ለሽብርተኝነት የተመቻቸ ሜዳን እንዲፈጥር ማድረጉ አያከራክርም፡፡
በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የአሸባሪዎች ቀጥታ ጥቃት የታየው የቀድሞውን የግብፅ ፕሬዘዳንት ሆስኒ ሙባረክን ዒላማው ያደረገ አንድ
ቡድን በ1986 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የግድያ ሙከራ ባደረገበት ጊዜ ነበር፤ ቀጥሎ ደግሞ በ1991 ዓ.ም. በትራንስፖርትና መገናኛ ሚኒስትሩ
አብዱልመጅድ ሁሴን ላይ የተሞከረው ግድያ የሽብርተኝነት ጅማሮዎች ሆነዋል፡፡ ይህ ከሆነ ጥቂት ዓመታት ዘግይቶ በተመሳሳይ ሰዓት
በግዮን እና በዋቢ ሸበሌ ሆቴሎች የደረሰው የቦንብ ጥቃት፣ መሀል ፒያሳ ይገኝ በነበረው ትግራይ ሆቴልን የመታው ፍንዳታ የሽብር
አደጋው በቅርብ ርቀት ለመኖሩ አመላካች ነበር፡፡ ይህም ሆኖ ስርዓቱ ድርጊቱን ለመከላከል በስራ ላይ ከዋሉት ህጎች ተጨማሪ አዲስ አዋጅ
‹‹ያስፈልገኛል›› የሚል ድምዳሜ ላይ አልደረሰም፤ ወይም የመፈለግ ምልክት አልታየበትም፡፡
በግልባጩ ከምርጫ 97 በኋላ የሽብር ጥቃቱ ዒላማውን ከባለስልጣናት እና ሆቴሎች ወደ ህዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርቶች (ሚኒባስ
ታክሲ እና የከተማ አውቶብስ) ያሸጋገረ መሰለ፡፡ በአንዳንድ አካባቢም የተጠመዱ ፈንጂዎች በደህንነት ሰራተኞች ‹‹ቅድመ ንቃት››
የመምከናቸው ዜና የቴሌቪዥን ርዕሰ ጉዳይ እንደነበረ ይታወሳል (በነገራችን ላይ መንግስት ከጥቂት ዓመት በፊት በአዲስ አበባ ሶስት ሰዎች
የገደለውን የፈንጂ ጥቃት የፈፀሙት የኦነግ አባላት ናቸው ቢልም፣ በወቅቱ በኢትዮጵያ የአሜሪካ ጉዳይ ፈፃሚ የነበሩት ቪክ ሀድልስተን
የኢምባሲ ምንጫቸውን ጠቅሰው ወደስቴት ዲፓርትመንት በላኩት ዘገባ ፈንጆቹን ያጠመደው የኢትዮጵያ መንግስት እንደነበረ ዊክሊክስ
መዘገቡ ይታወሳል) አሳዛኙ ጉዳይ የድርጊቱ ትርፍና ኪሳራ የተወራረደው አጀንዳውን (ጥቃቱን መሰንዘር ያስፈለገበት ምክንያት) በጭራሽ
የማያውቁትን እና የማይመለከታቸው በርካታ ንፁሃንን የህይወት ዋጋ በማስከፈል መሆኑ ነበር፡፡
በየትኛውም ሀገር ህዝብን በማሸበር ዓላማቸውን ለማስፈፀም የሚቋቋሙ ቡድኖች የመጀመሪያ ዒላማ የሚያደርጉት ሰላማዊ ዜጎችን ነው፤
የዚህ ምክንያቱ ፍርሃትን ካላነገሱ በቀር ኃይል ያለው ቡድን ፍላጎታቸውን ሊያሟላ ወይም በትይዩ ተቀምጦ ለመደራደር ፍቃደኛ ሊሆን
ባለመቻሉ ይመስለኛል (በቅርቡ የባራክ ኦባማ አስተዳደር በአፍጋኒስታን ህጋዊ ስልጣን የያዘውን መንግስት አውላላ ሜዳ ላይ አስቀምጦ
ለዓመታት በአስቸጋሪው ቶራ ቦራ ተራራ ሳይቀር ዘመን ባፈራው ቴክኖሎጂ ሲያሳድደው የነበረው ታሊባንን ዕውቅና ከመስጠት አልፎ
ለመደራደር ፍላጎት እንዳለው መግለፁ አንዱ ማሳያ ነው፡፡)
በኢትዮጵያ ከላይ የተጠቀሱት የሽብር ድርጊቶች ቢፈፀሙም በአብዛኛው ህዝብ ዘንድ ‹‹አሸባሪ›› ወይም ‹‹ሽብርተኝነት›› የተባሉ ቃላቶች
የተለመዱ አልነበሩም፤ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራትና ታላቋ አሜሪካንን የሚመለከት ብቻ ተደርጎ የተተወ ነበር-የኢትዮጵያ መከላከያ
ሰራዊት ፊቱን የጦር አበጋዞች በታትነው /ከፋፍለው/ ወደ ሚያስተዳድሯት ሶማሊያ የሚመልስበት ምክንያት እስኪያገኝ ድረስ፡፡የ‹‹መና›› ዘመን
የምርጫ 97ን አለመግባባት ተከትሎ በተለያዩ ቦታዎች የተለኮሱ ‹‹የአብዮት ደመራዎች››ን አገዛዙ በወታደራዊ ኃይል ለማዳፈን
ቢሞክርም ሳይሰምርለት ቀርቶ እንቅልፍ ያጣበት ወቅት ነበር-1998 ዓ.ም፡፡ በተለይም በየጎዳናው በጥይት ተደብድበው ከወደቁት ንፁሀን
በተጨማሪ የምርጫው ዋነኛ ተዋናዮች (የቅንጅት የአመራር አባላት) ጅምላ እስርን በተመለከተ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች በየትምህርት
ቤታቸው ደጃፍ ያሰሙ የነበረው የተቃውሞ ድምፅ፣ ሃይማኖታዊ በዓላትን ምክንያት አድርጎ በአደባባይ የሚሰበሰበው ህዝብ
የ‹‹መሪዎቻችን ይፈቱ›› ጥያቄ፤ ከሀገር ውጪ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ በአገዛዙ ላይ የሚያሰማው ወቀሳ እና ቅሬታ፣ ከአውሮፓ ህብረት
ምርጫው ተጭበርብሯል አቋም ጋር ተደማምሮ ኢህአዴግን ፋታ የነሱ ጉዳዮች ነበሩ፡፡ እነዚህ ኩነቶችም ለግንባሩ መርከብ ከባድ ወጀብ
ሆነው ዕጣ ፈንታው ባለየበት በዛ ቀውጢ ወቅት ነበር በመንግስት አልባዋ ሶማሊያ ራሱን ‹‹የእስልምና ህብረት ፍርድ ቤቶች›› እያለ
የሚጠራው የጦር አበጋዞች ስብስብ እንደተመሰረተ ይፋ የሆነው፡፡
ኢትዮጵያ ከቡድኑ ጋር ትከሻ የምትገፋፋበት አጣዳፊ ምክንያት ባይኖራትም፣ የአለምን የፖለቲካም ሆነ የዲፕሎማሲ ኃይል ሚዛን
የማቻቻሉ አቅም ላላት አሜሪካ የሞቃዲሾው ወሬ በቸልታ የሚታለፍ አልነበረም፡፡ እናም ክስተቱ በጄኔራል መሀመድ ፍራ ሀይድድ ዘመን
ሶማሊያ ‹‹ዳግማዊ ቬትናም›› የሆነችባት አሜሪካንን፣ የአለም አቀፍ ተቃውሞ ወጀብ ሊውጠው ከሚያጣድፈው ኢህአዴግ ጋር ‹‹ሻጭና
ሸማች›› አድርጎ አገናኛቸው (በርግጥ ለነሱ ይህ ሰጥቶ መቀበል ነው) አሜሪካ የኢትዮጵያ ወታደር የሶማሊያን ድንበር ጥሶ በመግባት
‹‹ጥጋበኞቹን›› አደብ እንዲያስገዛቸው፣ በምላሹም ኢህአዴግን እያሰመጠው ከነበረው የውስጥና የውጪ ጫና መላኩ ሚካኤል ሆነው
ሊታደጉት ተስማሙ፡፡
እንግዲህ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም ይህንን እውነታ ነበር ‹‹የሶማሊያ አክራሪዎች በኢትዮጵያ ላይ ጀሀድ አውጀዋል›› ወደሚል ቀይሮ፣
መከላከያ ሰራዊቱን በፍጥነት ወደ ሞቃዲሾ ለመላክ ም/ቤቱ ይወስን ዘንድ የጠየቀው፤ በተለመደው መንገድም ተወሰነለት፡፡ አሜሪካም
ከትልቁ አል-ቃይዳ ጋር ግንኙነት ይኖረዋል ብላ የጠረጠረችው ጠላቷ በጥቂት ቀናት ጦርነት ተበታትኖ ሜዲትራኒያን ሲገባላት፤
‹‹መና››ውም የውስጥ ጉዳዩ የዶግ ዓመድ ሊያደርገው ለተቃረበበት ኢህአዴግ ጊዜያዊ መውጫ አስገኘለት፡፡
አል-ሸባብ
የሶማሊያ ዘመቻ ውጤት እንዲህ ተጠናቀቀ፡- ዋነኛ ዒላማው አሜሪካንን ያደረገው የእስላማዊ ፍርድ ቤቶች ከስሞ፣ የኢህአዴግን ወረራ
እመክታለሁ የሚለው አል-ሸባብ ተተካ፡፡ የአልሸባብ አፈጣጠር በሶማሊያ ግዛት ውስጥ ቢሆንም ከፍርድ ቤቶቹ በጠበቀ ከአል-ቃይዳ ጋር
ግንኙነት ያለው በመሆኑ ሊያደርስ የሚችለው አደጋ በቀላሉ የሚታይ አለመሆኑ ግልፅ ነው፡፡ አል-ሸባብ ከየትኛውም ጠላቱ በፊት
ኢትዮጵያን ደመኛው በማድረጉና የሽብር ድርጊቶች የሚፈፀሙበት ስልት ከዘመኑ ጋር የተራቀቀ በመሆኑ ኢህአዴግ አዲስ ‹‹የፀረ-ሽብር
ህግ›› እንዲያዘጋጅ ገፊ ምክንያት ቢሆነው አያስደንቅም፡፡
ስጋት የከበበው ‹‹ህግ››
የኢትዮጵያ ሰራዊት የአሜሪካንን ተልዕኮ ተቀብሎ ወደ ሶማሊያ ያደረገው ጉዞ ትርፍ የልዕለ ኃያሏን አሜሪካ ስውር ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍና
በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ብቻ አይደለም፣ ድንጋጤ ውስጥ ከቶት የነበረው የምርጫ 97ቱ አይነት ህዝባዊ ንቅናቄ ዳግም እንዳይከሰት
በር የሚዘጋበት ምክንያትም እንጂ፡፡
እናም ከቀደመው የአል-ቃይዳ ታሪክ ንባብ ማጣቀሻዎችን በመሽረፍ እና አል-ሸባብ በሶማሊያ ያደረሰውን የሽብር ጥቃት በማጋነን
በኢትዮጵያም ላይ የምፅዓት ቀን ተቃርቧል በሚል፣ በአል-ሸባብ በኩል ከአል-ቃይዳ ጋር ያላተመችው አሜሪካ ራሷ (በለሰለሰ መልኩ
ቢሆንም) የተቸችውን የፀረ-ሽብር ህግ አርቅቆ በማዘጋጀት በስራ ላይ አዋለው፡፡ ይህ ህግ ያስፈለገበትንም ምክንያት በአዋጁ ላይ እንዲህ
ገልጿል፡-
‹‹ህዝቦች በሰላም፣ በነፃነትና በተረጋጋ ሁኔታ ለመኖር ያላቸው መብት ከሽብርተኝነት አደጋ ሁልጊዜ መጠበቅ ያለበት በመሆኑ፤
ሽብርተኝነት ለሀገራችን ሰላም፣ ደህንነትና እድገት ፀር እንደሆነ፤ ለአካባቢያችንና ለዓለም ሰላም እና ደህንነትም ከፍተኛ ስጋት እንደሆነ
ግንዛቤ የተወሰደ በመሆኑ፤ በስራ ላይ ያሉት የሀገሪቱ ሕጎች በበቂ ሁኔታ ሽብርተኝነትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችሉ
ባለመሆናቸው ጠንካራ የህግ አቅም መፍጠር በማስፈለጉ…››ይሁንና ህጉ ‹‹ሽብርተኝነት››ን አለቅጥ ለጥጦ ማብራራቱ ለትርጉም ክፍተት ዳርጎታል፤ የመረጃ አሰባሰቡም ቢሆን በርካታ ህገ-
መንግስታዊ መብቶችን ከመጨፍለቁ በተጨማሪ በየትኛውም ሀገር ተቀባይነት የሌለውን ‹‹የሰሚ ሰሚ ወይም በተዘዋዋሪ የተገኙ
ማስረጃዎች›› ብሎ በአንቀፅ 23 ቁጥር 2 ላይ መግለፁ ኢህአዴግን ለመሰለ አምባገነን ስርዓት የሚሰጠው ‹‹ህጋዊ ጉልበት›› ከምንም
በላይ አደጋው የበዛ ነው፡፡ በህጉ ክፍል ሁለት ላይ የ‹‹የሽብርተኝነት ድርጊቶች›› ተብሎ የተዘረዘሩት ሰባት አይነት ድርጊቱ መፈፀሙን
የሚገልፁ መስፈርቶችም ቢሆኑ በተራ (በደረቅ) ወንጀል ውስጥ የሚወድቁ እንጂ የሽብር ድርጊት መገለጫ አይደሉም፡፡
የሆነ ሆኖ ረቂቅ ህጉ በተሰራጨበት ወቅት ነፃ ዳኝነት በሌለባት፣ የጠመንጃ አስተዳደር በሰፈነባት፣ የህግ የበላይነት በማይከበርባት…
ኢትዮጵያ ‹‹ሽብርተኝነት››ን አለቅጥ አስፍቶ የሚተረጉም ህግ መውጣቱ ተቃዋሚዎችን የመንቀሳቀሻ ምህዳር ለማሳጣት እና ተቺ
ጋዜጠኞችን ለማፈን እንደሆነ ተደጋግሞ ቢነገርም በኢህአዴግ በኩል ሰሚ አላገኘም፡፡ የዚህ ፅሁፍ ተጠየቅም ህጉ ይሰረዝ ከሚለው
አይመደብም፤ መሻሻል ከሚጋባቸው የተወሰኑ አንቀፆች በቀር ለሀገር ደህንነት አስፈላጊ መሆናቸውን በመቀበል የሚነሳ ነው፤ ሆኖም ይህ
ህግ ኢህአዴግ በስልጣን ላይ እያለ በትክክል ሊተገበር የማይችል መሆኑን ያምናል፤ እናም ጥያቄው ህጉ አያስፈልግምና ይሰረዝ የሚል
አይደለም፤ ህጉ ያስፈልጋልና፤ የማያስፈልገው (ከስልጣኑ መነሳት ያለበት) ህግን ለፖለቲካ መጠቀሚያ የሚያውለው ኢህአዴግ ነው፤
የትግሉ (የዘመቻው) አቅጣጫም ከዚህ አንፃር ነው መቃኘት ያለበት፡፡ ይህ ህግ ሳይኖርም በሺዎች የሚቆጠሩ ንፁሀን ዜጎችን በየእስር ቤቱ
ሲያጉር የቆየ መሆኑ መረሳት የለበትም (የፀረ ሽብር ህጉ ከተሰረዘ ስርዓቱ ለህግ የበላይነት ይገዛል የሚል መተማመኛ መስጠት የሚችለው
ማነው?) ጉዳዩን በቀላሉ ለመረዳት ኦነግን እንደ ምሳሌ ብንወስደው፣ በአዲሱ ህግ ሽብርተኛ ተብሎ ተፈርጇል፤ ነገር ግን ኦነግ ሽብርተኛ
ከመባሉ በፊት ‹‹ደጋፊና አባላት›› በሚል ወንጅላ በተለያዩ እስር ቤቶች የተጣሉ የኦሮሞ ተወላጆች ስንት ናቸው? ሀያ ሺህ ወይስ ሰላሳ
ሺህ? ጥያቄ ይህው ነው፡፡
ከህጉ በኋላ…
የፀረ-ሽብር ህጉ ከመፅደቁ በፊት ሲነገሩ የነበሩ ስጋቶች፣ ህጉ ከፀደቀ በኋላ አይቀሬ መሆናቸውን ከራሱ ከኢህአዴግ ለመረዳት ለወራት
በሚቆጠር እድሜ ብቻ ነበር የዘገየው፡፡ በአቶ መለስ ዜናዊ አዘጋጅነት እንደሚታተም (በህልፈቱ ማግስት) በጓዶቹ የተነገረው የድርጅቱ
የንድፈ ሃሳብ መጽሔት ‹‹አዲስ ራዕይ›› በመጋቢት-ሚያዝያ እትሙ የህጉን አስፈላጊነትና ጠቀሜታ ቀደሞ ከተከራከረበት አል-ቃይዳ፣
አል-ሸባብ፣ ኦነግ፣ ኦብነግ እና ግንቦት ሰባት፣ በሰላማዊ መንገድ ወደሚታገሉ ፓርቲዎች እንዲህ ሲል አሸጋግሮታል፡-
‹‹ፀረ-ሽብር ህጉ ዜጐች ያለስጋት በነፃነት እንዲንቀሳቀሱ በማድረጉ በአገራቸው የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ህይወት ውስጥ ንቁ
ሚና እንዲጫወቱ ለማድረግ ያለመ ነው፡፡ ከ97 ዓ.ም. በኋላ መንግስት ከወሰዳቸውና በተግባርም ካዋላቸው ትምህርቶች መካከል
የፖለቲካ ምህዳሩ ለዜጐች በተለይም ህግ አክብረው ለሚንቀሳቀሱ ዜጐች መስፋት ያለበት የመሆኑን ያህል ለህገ-ወጥ በተለይም ደግሞ
ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በኃይል ለመገርሰስ ለሚደረጉ የተደራጁም ሆኑ የተበተኑ እንቅስቃሴዎች መንቀሳቀሻ አድማሱ እንዲጠብ
የማድረግ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መሰረት አገር ውስጥ ከአመፅና ጎዳና ላይ ነውጥ በስተቀር ሌላ ሰላማዊ መንገድና ስልት ለማይታያቸው
መንቀሳቀሻ ቦታው እንዲጠብ አድርጓል፡፡ ህግ እየጣሱ በኢትዮጵያ ውስጥ በመገንባት ላይ ያለውን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ህግ የማስከበር
ብቃት ሊፈታተኑ የማታ ማታም ህግና ስርዓት ማስከበር አቅቶት እንዲሽመደመድ ለማድርግ የቆረጡ ኃይሎች እነሱን የሚሸከም ትከሻ
እንደማይኖር እንዲያዩ ተደርጓል፡፡›› (ቅፅ 3፣ ገፅ 28-29)
መቼም የኢህአዴግ የጎዳና ላይ ነውጥና ህዝባዊ ንቅናቄ ትርክት ዓለም የተስማማበትን የሽብር ድርጊት ያሰላ አለመሆኑ ግልፅ ነው፤ ‹‹ከ97
ዓ.ም በኋላ መንግስት ከወሰዳቸውና በተግባርም ካዋላቸው…›› የሚለው አገላለፅ አል-ቃይዳን ወይም አል-ሸባብን የሚመለከት አይደለም፤
እነኦነግ እና ኦብነግም ‹‹የምርጫ ፓርቲ›› እንዳልሆኑ ይታወቃል፡፡ ህጉን ያወጣው ገፊ ምክንያት ሰላማዊ ዜጎችን ዒላማ ከሚያደርገው
ድንገቴ የፈንጅ ጥቃት ለመከላከል ሳይሆን፣ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎችን በማዳፈን የአገዛዙን ዕድሜ ለማራዘም ነው፤ በተግባር የታየውም
ይህ ነው፡፡ ተቀናቃኝ ፓርቲዎችን በግላጭ የመምቻ ዱላ ማድረግ (እንዲህ አይነቱ የስርዓቱ ነባር ልማድ የተወረሰው ከማኪያቬሊ
‹‹ፍትሀዊ ምሰል እንጂ ፍትሀዊ አትሁን›› አስተምህሮ ይመስለኛል)
የሆነ ሆኖ ይህ ህግ ተፈፃሚ የሆነባቸውን የህሊና እስረኞች ማንነት ብንፈትሽ በሽብር ተግባር ላይ የሚሰማሩ ሰዎችን በተመለከተ ጥናት
ያደረጉ ባለሞያዎች ካስነበቡን ስብዕናም ሆነ ባህሪ ጋር በፍፁም የሚቀራረብም የሚመሳሰልም አይደለም፡፡ በፍርድ ቤት
ለ‹‹አሸባሪነታቸው›› ማረጋገጫ ተብሎ የተጠቀሰውም በሀገሪቱ የነገሰውን የፍትህ ሂደት የሚያሳይ ነው፤ ለምሳሌ ያህልም የጥቂት
ሰለባዎችን የክስ ማስረጃና ማንነት ጨርፈን እንመልከት፡፡
እስክንድር ነጋ
በሙያው ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ ሲሆን ባለትዳርና የአንድ ልጅ አባት ነው፤ ትምህርቱንም ከሁለተኛ ደረጃ ጀምሮ እስከ ሁለተኛ
ዲግሪው ድረስ በአሜሪካን ሀገር ነው የተከታተለው፤ በ1983 ዓ.ም የመጣውን የስርዓት ለውጥ ተከትሎ ወደ ሀገሩ በመመለስ ከስድስትያላነሱ ጋዜጦች መስርቶ በኃላፊነት መርቷል፤ አገሩን ከልብ ከመውደዱ በቀር የሀይማኖትም ሆነ የብሄር ጥላቻን የማያራምድ፣ ለፖለቲካ
ልዩነትም አክብሮት ያለው ነው፤ ለህግ ተገዢ ቢሆንም በፖለቲካ አመለካከቱ ከኢህአዴግ የተለየ ነው (ጥፋቱም ይህ ይመስለኛል)::
እስክንድር ነጋ አዲሱን የፀረ-ሽብር ህግ ተላልፈሀል በሚል 18 ዓመት ተፈርዶበት በዝነኛው ማጎሪያ ‹‹ቃሊቲ ወህኒ ቤት›› ይገኛል፤
ለ‹‹አሸባሪነቱ›› ማረጋገጫ ተብለው በፍርድ ቤቱ የተሰሙት የሚከተሉት ሶስት ነገሮች ነበሩ፡- የአመፅ ተግባርን ለመፈፀም ከሚንቀሳቀሱ
የሀገር ውስጥ ፓርቲ አመራሮች ጋር ስለጉዳዩ ተደጋጋሚ ስብሰባ ማድረግ፣ ለኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን የተለያዩ መረጃዎችን መስጠት
(አቦይ ስብሀት ነጋን ጨምሮ በስራ ላይ ያሉ ጄነራሎችም ለጣቢያው መረጃ መስጠታቸው ‹‹የሽብር ድርጊት ነው›› በሚል አለመከሰሳቸው
ልብ ይሏል) እና ሁከትን መፃፍና ማሰራጨት፤ አለቀ፡፡
ርዕዮት አለሙ
ጋዜጠኛና መምህርት ናት፤ በሁለት የተለያዩ የትምህርት ዘርፎችም ሁለት የመጀመሪያ ዲግሪዎች አግኝታለች፤ ለቤተሰቦቿ የበኩር ልጅ
በመሆኗም የአስተዳዳሪነትን ኃላፊነት የመሸከም ሞራልም ብቃትም እንደነበራት በተግባር አስመስክራለች፤ ሀገሯ የተሻለች እና ለዜጓቿ
የምትመች እንድትሆን የምታልም፣ ሰላም ወዳድ እንስት ናት፤ ከሀይማኖትም ሆነ ከብሄር ጥላቻ የራቀች፣ ትህትናን የተላበሰች ጎበዝ
ጋዜጠኛ፡፡
‹‹አሸባሪ›› ተብላ ሲፈረድባት በችሎቱ የተነበበው ማረጋገጫ፡-
‹‹ከ1ኛ ተከሳሽ (‹የኢትዮጵያን ሪቪው ድህረ-ገፅ› ባለቤት ኤልያስ ክፍሌ) ጋር የስራ ግንኙነት በመፍጠር ለአመፅ ቀስቃሽ ስራዎች
በመተባበር ፎቶ ግራፍ ስትልክለት ነበር፡፡››፤ በቃ!
ውብሸት ታዬ
በዩኒቲ ዩንቨርስቲ በጋዜጠኝነት ትምህርት ሰልጥኗል፤ ባለትዳርና የአንድ ልጅ አባት ነው፤ በሙያው ሀገሩንና ወገኑን ከማገልገል ባለፈ
ጥላቻና የጭካኔ ባህሪ የሌለው ጎበዝ ጋዜጠኛ፡፡
ለ14 ዓመት ፍርድ የተዳረገውም ‹‹ሽብርተኛ›› ተብሎ ቢሆንም የቀረበበት ክስ እንዲህ የሚል ነበር፡-
‹‹የኤሌትሪክ መስመሮች እና የፋይበር ኦፕቲክስ መቆራረጣቸውን ለ1ኛ ተከሳሽ (ኤሊያስ ክፍሌ) ሲነግረው ነበር፡፡ አንደኛ ተከሳሽ ደግሞ
የደረሰውን ውድመት በድረ-ገፁ ሲያስተጋባ ነበር፡፡ ይህም የሽብር ድርጊት ለመፈፀም ሲያሴር እንደነበረ ያስረዳል፡፡››፤ በቃ!
አንዱአለም አራጌ
በታሪክ ትምህርት ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የመጀመሪያ ዲግሪ አግኝቷል፤ ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ነው፤ አንዱአለም ከ1993 ዓ.ም
ጀምሮ ‹‹የኢህአዴግ አስተዳደር ለሀገሬ አይጠቅማትም›› ብሎ በሠላማዊ መንገድ የተደራጁ ፓርቲዎችን (ኢዴፓ-ቅንጅት-አንድነት)
ተቀላቀሎ በይፋ የሚታገል ትንታግ ፖለቲከኛ ነው (የእርሱም ጥፋት ይህ ይመስለኛል)
‹‹አሸባሪ›› ተብሎ ለእድሜ ልክ ፍርድ የተዳረገው፡- ‹‹ኤርትራ ከሚኖረው ኮሎኔል አለበል አማረ ጋር በኢ-ሜል ‹እንኳን አደረሰህ›
ተባብለሀል››፣ ‹‹ህገወጥ ፅሁፎችንና ወረቀቶችን በየአደባባዩ በማስለጠፍ የማነሳሳት ስራ መስራትና ማሰራት›› እና ‹‹የአረብ ሀገር አመፅ
በኢትዮጵያ መከሰቱ አይቀሬ ነው ብለሀል፡፡››፤ በቃ!
ሂሩት ክፍሌ
ትምህርቷን እስከ አስረኛ ክፍል ተምራለች፤ ባለትዳርና የሶስት ልጆች እናት ናት፤ የመዐህድ መስራች አባል የነበረችና ለዓመታት በሠላማዊ
መንገድ ለውጥ ይመጣ ዘንድ የአቅሟን ያህል አስተዋፆ ያደረገች ብትሆንም ህዝብን ዳኛ የሚያደርገው ታሪክ የዘነጋት ባለውለተኛ
ትመስለኛለች፡፡
19 ዓመት ‹‹አሸባሪ›› ብሎ ያስፈረደባትን ክስ ዳኛው እንዲህ ሲል ማንበቡን አስታውሳለሁ፡-
‹‹1ኛ ተከሳሽ (ኤሊያስ ክፍሌ) በሚልክላት ገንዘብ የሽብር ድርጊት ለመፈፀም ሰዎችን ታደራጅ ነበር፡፡››፤ በቃ! (በነገራችን ላይ ‹ኤሊያስ
ክፍሌ› የሚባል ጋዜጠኛ እንጂ በፓርላማ ‹ሽብርተኛ› ተብሎ የተፈረጀ ድርጅት መኖሩን ሰምቼ አላውቅም)
የሆነ ሆኖ የኢህአዴግን ኢ-ፍትሀዊነት የሚያሳየው የውብሸት ታዬ እና የሂሩት ክፍሌ ጉዳይ ነው፤ ሁለቱም ከፍተኛው ፍርድ ቤት
የተጠቀሰውን ቅጣት ከወሰነባቸው በኋላ እንደ ሌሎቹ ተከሳሾች ‹‹ይግባኝ›› አልጠየቁም፤ ምክንያቱም የሀገሪቱ ህግ ለማንኛውም ተከሳሽ
የሚሰጠውን ‹‹የይቅርታ መብት›› ለመጠቀም ስለመረጡ፤ እናም በደንቡ መሰረት ‹‹ለይቅርታ ቦርዱ›› ማመልከቻ አስገቡ፤ ምላሽ
ሳያገኙም ይግባኝ መጠየቂያው ጊዜ አለፈ፤ በዚህ መሀል ከእነርሱ በኋላ በተመሳሳይ አንቀፅ ተከሰው የተፈረደባቸው ስውዲናዊያን
ጋዜጠኞች (ማርቲን ሹብዬ እና ጆዋን ዋሹን) የይቅርታ መብታቸው ተከብሮ በምህረት ተፈተው ወደ ሀገራቸው ሲገቡ ውብሸትና ሂሩት
ነገን ተስፋ አድርገው እየጠበቁ ነበር፤ ግና ምን ዋጋ አለው! ለሂሩት ክፍሌ በ24/11/05 ዓ.ም ‹‹የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ
ሪፖብሊክ የፍትህ ሚኒስቴር›› እንደሚከተለው የሚነበብ ደብዳቤ እስር ክፍሏ ድረስ ላከላት፡-
‹‹ለህግ ታራሚ ሂሩት ክፍሌ ወልደየስአ/አበባ ማረሚያ ቤት
ጉዳዩ፡- የይቅርታ ጥያቄዎ ውድቅ መደረጉን ስለማሳወቅ፣
ለክቡር የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፕሬዘዳንት የይቅርታ ጥያቄዎ ቀርቦ ከተመለከቱት በኋላ ውድቅ የተደረገ መሆኑን እንገልፃለን፡፡
ከሠላምታ ጋር
ፋንታዬ ነጋሽ
ስለይቅርታ ቦርድ ጽ/ቤት ኃላፊ
(የማይነበብ ፊርማና ማህተም)
ይህ ነው የኢህአዴግ እውነተኛ ባህሪ፤ ከፖለቲካ ትርፉ በቀር ለህግም ለባህልም የማይጨነቅ ደንታቢስ፤ ከቶስ! ኢትዮጵያ ሀገራችንን ከእኛ
ዜጎቿ በላይ ማን ያውቃታል?
ሃዋ ዋቆ
ሃዋ፣ በእነበቀለ ገርባ (የኦፌዴን ም/ሊቀ-መንበር) እና ኦልባና ሌሊሳ (የኦህኮ ዋና ፀሀፊ) የክስ መዝገብ ‹‹የኦነግ አባል›› ተብላ ነው
የታሰረችው፤ የሃዋ ትውልድና ዕድገት ኬኒያ ሲሆን፣ ከኦነግ ጋር ለተወሰነ ጊዜ አብራ ከታገለች በኋላ ከድርጅቱ ሙሉ በሙሉ በመውጣት፣
መንግስት ምህረት አድርጎላት ሀገሯ ገብታ መኖር ከጀመረች አመታት አልፈዋል፡፡
ሃዋ ዋቆ ‹‹አሸባሪ›› ተብላ ለቀረበባት ክስ ‹‹ሀሰት ነው፤ በግል ጉዳይ ያልተግባባዋቸው ሰዎች የፈጠሩት ወንጀል ነው›› ብላ ከመከራከሯም
በተጨማሪ ይህንን ጉዳይ ይመሰክሩልኛል ያለቻቸውን ሶስት ሰዎች በችሎቱ አቅርባ እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡
የመጀመሪያው ምስክር መሀመድ በሉ ይባላል፤ ቃለ-መሀላ ከፈፀመ በኋላ እንዲህ ሲል መስክሯል፡-
‹‹አንድ ሰው (በስም ጠቅሷል) ‹ላግባሽ› ሲላት ‹አባቴ ትሆናለህ አላገባህም፤ ደግሞም እኔ ጓደኛ አለኝ› ስትለው አሳስርሻለሁ ባላት መሰረት
አሳስሯታል፡፡››
ሁለተኛው ምስክርም ቀጠለ፤ አዲስ በከሬ ይባላል፤ የሃዋ የፍቅር ጓደኛ መሆኑን ከገለፀ በኋላ ምስክርነቱን ሰጥቷል፡-
‹‹ከሃዋ በፊት ፍቅረኛዬ የነበረችውን ቀበሌ በርካሳን ትቼ ከሃዋ ጋር ለመጋባት ቃል ተገባብተን ነበር፡፡ የቀድሞ ፍቅረኛዬ ግን በዚህ
ተበሳጭታ ‹ላግባሽ› ሲላት ‹እምቢ› ካለችው ሰው ጋር በመሆን ሃዋን በተሳሳተ ምስክርነት አሳሰሯት፡፡›› (ሶስተኛው ምስክርም ተመሳሳይ
ቃል ነው የሰጠው)
…ፀረ-ሽብር ህጉ ገና መረቀቁ እንደታወቀም የብዙዎች ስጋት ይህ ነበር፡፡ ስርዓቱ ተቀናቃኞቹን የሚያጠቃበት ‹ህጋዊ መሳሪያ› አገኘ፡፡
ኢህአዴግም የሚፈልገው ይህንኑ ነው፡፡ ነፃ ባልሆነው ምርጫ ቦርድ አማካኝነት የሚደረገውን ምርጫ አጭበርብሮ ሲያበቃ እንዲህ ይልና
ይቀልዳል፡-
‹‹ፓርቲዎቹ ህገ-መንግስቱንና ህግን አምነው ተቀብለው የሚወዳደሩበት፣ ምርጫ በመጣ ቁጥር ህዝቡ የቀውስና የብጥብጥ ስጋት
ሳያውከው፣ የምርጫ ውጤቶች በሁሉም ተዋናያን ተቀባይነት አግኝተው ተግባራዊ የሚሆኑበት ስርዓት መሠረቱ ዲሞክራሲያዊ ህገ-
መንግስት ነው›› (አዲስ ራዕይ ቅፅ 3፣ ቁጥር 3፣ ገፅ 21)
…በኢህአዴግ መዝገበ ቃላት ‹‹ሠላማዊ፣ ህጋዊ ምርጫና የህዝብ ድምፅን በፀጋ መቀበል›› ምን ማለት ይሆን? ማን የሚያረጋግጠውን
የምርጫ ውጤት ነው ‹አምናችሁ ተቀበሉ› የሚለው? ‹ድምፄ ተጭበርብሯል› ማለትስ ‹ሽብርተኝነት› የሚሆነው እንዴት ሆኖ ነው?
የአንድነት መንገድ
አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ‹‹የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት›› በሚል መፈክር የፀረ ሽብር ህጉ እንዲሰረዝ የሚጠይቅ የሶስት ወር
ሀገር አቀፍ ዘመቻ ጀምሮ እየተንቀሳቀሰ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ፓርቲው ዘመቻውን እያካሄደ ያለው በህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ዳንኤል
ተፈራ የሚመራ አስተባባሪ ኮሚቴ በማቋቋም ነው፡፡
ከአስተባባሪው ለመረዳት እንደቻልኩት ዘመቻው የሚካሄደው በሶስት መንገድ ነው፤ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ሠላማዊ ሠልፍ
በማካሄድ፣ የአዳራሽ ስብስባዎችን በመጥራት እና በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ያሉ ኢትዮጵያውያኖችን ‹ፒቲሽን› (ፊርማ) በማሰባሰብ፡፡
በዕቅዱ መሰረትም ጎንደር፣ ደሴ፣ ጅንካ፣ አርባ ምንጭ፣ እና ባህርዳር ሰልፎቹ ሲደረጉ፣ የመቀሌው ‹‹ህወሓት አላንቀሳቅስ አለን›› በሚል
ምክንያት ተሰርዟል፤ ወሊሶ፣ ናዝሬት፣ ፍቼ፣ ባሌ፣ ቤንሻንጉል እና አዲስ አበባ ደግሞ በአንድ ወር ውስጥ ሊካሄድባቸው የታሰቡ ከተሞች
ናቸው፡፡በወላይታና በአዲስ አበባ የአዳራሽ ስብሰባዎች የተደረጉ ሲሆን፤ ድሬደዋ፣ ጋምቤላ፣ አምቦ፣ አዋሳ እና ደብረ ማርቆስ በቀጣዩ መርሀ ግብር
ውስጥ የተካተቱ ሲሆን፣ ፒቲሽኑን በተመለከተ ይህ ፅሁፍ እስከተጠናከረበት 6/12/05 ዓ.ም ድረስ የተሳተፉትን ኢትዮጵያውያን ቁጥር
ገና ለይተው እንዳላወቁት አስተባባሪው ገልጿል፡፡
ኢህአዴግ የአንድነትን ዘመቻ ተከትሎ በ4/12/05 ዓ.ም ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር በፀረ-ሽብር ህጉ ላይ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ራዲዮን
ድርጅት በኩል ውይይት ለማድረግ ቀጠሮ ይዞ የነበረ ቢሆንም፣ አንድ ቀን ሲቀረው ላልተወሰነ ጊዜ መተላለፉን አሳውቋል፤ ይሁንና ህጉ
ከፀደቀ ሶስት ዓመት አልፎት፣ በርካታ ንፁሀኖችን ሰለባ ካደረገ በኋላ ለውይይት መቀመጥ የተፈለገበት ምክንያት አልተገለፀም (ምናልባት
ዘመቻውን ለማደብዘዝ ሆነ ብሎ ያደረገው ይመስለኛል፤ ምክንያቱም ድርጅቱ ህጉ ከመፅደቁ በፊት ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር የመወያየት
ፍላጎት እንዳልነበረው አስታውሳለሁና)
የሆነ ሆኖ አገዛዙ ህጉ ላይ የሚቀርበውን ተቃውሞ ወደአልተነሳበት ጠርዝ እየገፋው ነው፡፡ በተለይም የአንድነትን የይሰረዝ ዘመቻ
‹‹ሽብርተኝነት ያሰጋናል ወይስ አያሰጋንም?›› ወደሚል አይነት ጥያቄ ሰቅሎ እያቀረበው ነው፡፡ በአናቱም በኢትዮጵያ ህግ የሚሻሻለው
ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀርቦ እንጂ በፊርማና በአደባባይ በመጮኽ አይደለም ሲል ለማደናገር እየሞከረ ነው፤ በርግጥ ይህ መሟገቻ
እውነት ቢሆንም፣ ‹ተረት ተረት› ያደረገው ሀገሩ-ኢትዮጵያ፣ ሥልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ መሆኑ ብቻ ነው፡፡
ሌላው አሰቂኙ ጉዳይ ግምባሩ ‹ህጉ ለምን ያስፈራችኋል?› ሲል ተቺዎቹን መልሶ መጠየቁ ነው፤ ምክንያቱም ህጉ የተፈራው ኢህአዴግ
በሚመራው መንግስት የሚተገበር መሆኑን ጠንቅቆ ያውቀዋልና፡፡
…በአዋጁ ይሰረዝ ስም የተጀመሩት እንቅስቃሴዎች ፖለቲካዊ መነቃቃትን ለመፍጠር አጋዥ ሙከራዎች እንደሆኑ ቢታወቅም ይህ ፊርማ
የማሰባሰብ ዕቅድ ሰነዱ በመጨረሻ ለስርዓቱ ቀርቦ አዋጁ የሚሻሻልበት እድል ባይኖር ምን ይደረጋል የሚለው መታሰብ አለበት፡፡ ከዚህ
ሁሉ በላይ አዋጁ ቢኖርም ሆነ ቢሻሻል ስርዓቱ እስካለ አንዳች በጉ ነገር ስለማይኖር ኢህአዴግ ከስልጣን የሚወርድበትን መንገድ ማሰብ
ብቸኛው አመራጭ ነው፡፡