Saturday, September 7, 2013

ሰላማዊ ትግላችን ይቀጥላል!!!

ሰላማዊ ትግላችን ይቀጥላል!!!
(ከሰማያዊ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ)
ሰማያዊ ፓርቲ ለነሐሴ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ጠርቶት የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ በመንግስት ታጣቂ ኋይሎች ሕገ-አራዊት እርምጃ ከተደናቀፈ በኋላ ፓርቲያችን ነሐሴ 30 ቀን 2005 ዓ.ም በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ጳጉሜ 2 ቀን 2005ዓ.ም ሠልፉ በድጋሚ እንደሚካሔድ አስታውቋል፡፡ ሠልፉ የተሳካና ሰላማዊ እንዲሆን በፓርቲ በኩል ልዩ ልዩ ተግባራት ከመከናወናቸው ጎን ለጎን አስፈላጊው የጸጥታ ጥበቃና የአስተዳደር ድጋፍ እንዲሰጠን በህጉ መሰረትም ሠልፉ እውቅና እንዲያገኝ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሰወቂያ ክፍል ነሐሴ 27 ቀን 2005ዓ.ም ደብዳቤ ለማስገባት በአካል ተገኝተን ጠይቀናል፡፡ ሆኖም ግን ይህ ክፍል ደብዳቢያችንን ለመቀበል ፍቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል፡፡
በፓርቲው በኩል በሁኔታው ተስፋ ባለመቁረጥ በኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት በኩል የማሳወቂያ ደብዳቤውን ከላይ በተጠቀሰው ቀን የላክን ሲሆን ውጤቱ ግን አሁንም በፖስታ ቤት በኩል የተላከውን ደብዳቤ በእንቢተኝነት አለመቀበል ሆኗል፡፡
ይህን ጉዳይ አስመልክቶ በዛሬው ዕለት የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች በአስተዳደሩ ፅ/ቤት በመገኘት ከተለያዩ ኃላፊዎች ጋር ለመነጋገር እረጅም ሰዓት የወሰደ ከቢሮ ቢሮ መንከራተት የተሞላበት ደጅ ጥናት ካደረጉ በኋላ በመጨረሻም በከንጺባ ጽ/ቤት የካቢኔ ጉዳዮች ም/ኃላፊ ጋር ለመነጋገር ተችሏል፡፡
በዚህም ውይይት የጳጉሜ አምስቱ ቀናት በከተማው አስተዳደር ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ለጥቃቅንና አነስተኛ ድርጅቶች የገበያ እድል ለመፍጠርና እራሳቸውን እንዲያስተዋውቁ በየዓመቱ አስቀድሞ በከተማው ማዕዘናት ያሉ ቦታዎች ለዚህ አገልግሎት ስለሚያዙ በነዚህ ቀናት የሰላማዊ ሰልፍ ጥያቄዎችን ለማስተናገድ የማይችሉ መሆኑን አበክረው ገልጸውልናል፡፡ ፓርቲው በከንቲባ ጽ/ቤቱ የቀረበውን ምክንያት ከመረመረ በኋላ የበዓሉ ዋዜማና የዘመን መለወጫ በዓል ካካፋ በኋላ ባሉት ቀናት ሰልፉን ለማድረግ በመወሰን ለጳጉሜ 2 ቀን 2005 ዓም ጠርቶት የነበረውን የተቃውሞ ሰልፍ ወደ መስከረም 12 ቀን 2006 ዓ.ም እንዲተላለፍ ወስኗል፡፡ የዚህን ሰልፍ እውቅና ጥያቄ ወዲያውኑ ለሚመለከተው ክፍል በማቅረብ የሰልፉ ማሳወቂያ ደብዳቤ ቀሪ ላይ በማስፈረም ገቢ አድርጓል፡፡
በመሆኑም ከለይ በተጠቀሰው ምክንያት ሠልፉ ወደ መስከረም 12 ቀን 2006ዓ.ም መተላለፉን እየገለጽን ከዚህ በፊት የጠራናቸው የተቃውሞ ሰልፎች የተሳኩ እንዲሆኑ የመገናኛ ብዙኃን፣ የሲቪክ ማሕበራትና በአጠቃላይ ኢትዮጵያውያን ላደረጋችሁት ድጋፍ ፓርቲያችን ምስጋናውን እያቀረበ፤ አሁንም ቀጣዩ ሠልፍ በታሰበለት ዓላማ መሠረት የተሳካ እንዲሆን የተለመደ ድጋፋችሁን እንድታደርጉ ፓርቲያችን ጥሪውን ያቀርባል፡፡
ምንግዜም የተባበረ የሕዝብ ትግል ያሸንፋል!!!
ነሐሴ 30 ቀን 2005ዓ.ም
አዲስ አበባ