Tuesday, November 5, 2013

እንዴት ነሽ ኢትዮጵያ፡ ስላም ነው?

የሃያ ዓመት ደብዳቤNovember 5, 2013
ከፈቃደ ሸዋቀና

እንዴት ነሽ ኢትዮጵያ፡ ስላም ነው?

እንደዘበት ትቼሽ ወጥቼ ከቀረሁ ያለፈው መስከረም ገብርኤል ሃያ ዓመት ሆነኝ። ከጠቅላላ ዕድሜዬ ከሲሶው በላይ መሆኑ ነው። ጊዜው እንዴት ይሮጣል? ያኔ ትቼሽ ስወጣ ወደኋላ እንዳላይ ብዬ ድንጋይ ወርውሬ መውጣቴን ስለምታውቂ ምነው ይህን ያህል ዘመን ጠፋህ የምትዪኝ አይመስለኝም። ምን ላድርግ። አይንሽ እያየ አይገፉ መገፋት አስገፋሽኝ። ዘር አስቆጠርሽብኝ። መገፋቴን ለምን እንደማለት በመገፋቴ ከንፈር የሚመጡ ሰዎች አብዝተሽ አሳየሽኝ። አንዱ ቅድመ አያቴ ዓድዋ አንዱ አያቴ ማይጨው ወድቀው የቀሩት የልጅልጃቸው አጎንብሼ እንድኖርብሽ ፈልገው አለመሆኑን አፍ አውጥቶ መናገር አቃተሽ። ያስገፋሽኝ ምናልባት ከስንበሌጥ ክምር አንድ ሰበዝ ቢመዘዝ ምን ይጎዳል በሚል ሂሳብ ይሆናል። ተመዝዤ የወጣሁት እኔ ብቻ ብሆን ኖሮ እውነትሽ ነበር። አንድ ባንድ እየተመዘዘ ከዚህ ከኔ ስደት አገር ብቻ የንጀራ አገሩን የሚያቀናውን ልጅሽን ብዛት ብታዪ ጨርቅሽን ጥለሽ ታብጂ ነበር።
ተከፍቼ ስለነበር ወዳጅ ዘመድ እንኳን በወጉ ሳልሰናበት ነው የወጣሁት። ዘጋዋለሁኝ ደጄን እንዳመሉ፥ የት ሄደ ቢሏችሁ ከፍቶት ሄደ በሉ” እያለ ያንጉጎራጎረው ዘፋኝ ራሴ መስሎኝ ነበር ያን ሰሞን። ጨክንሽ አስጨከንሽኝ። እንደ መከፋቴ ይህንንም ደብዳቤ የምጽፍልሽም እኔ ሆኜ ነው። ያውም ሰሞኑን የስደት ሀገሬ ፖለቲከኞች ተጣልተው መንግሥት ሲዘጉ የኔንም ስለዘጉት ያልታሰበ ዕረፍት አግኝቼ ነው የጻፍኩልሽ። ፖለቲከኞች ተጣልተው ስልሽ ደሞ አንቺ ጋ ያለው አይነት የፖለቲካ ጠብ መስሎሽ እንዳታስቢ። አንቺ ጋ እንደሚሆነው መትረየስና ቦምብ የታጠቀ ወታደርና ታንክ ከተማ መሀል አይርመሰመስም። ዱላና ርግጫ፥ በጥይት መደባደብ ፥ ወሕኒ ቤት እየጎተቱ ማጎር፥ የገዥዎች አይን እያየ የሚፈርድ ዳኛ ፊት ማቆም የሚባል ነገር የለም። አንቺ ጋ እንደሚሆነው ቢሆንማ ኖሮ መንግሥት ያዘጉትን የሪፐብሊካን ፓርቲ አባላት የመራውና በዚህም ምክንያት አገሩን ሀያ አራት ቢሊዮን ዶላር ያከሰረው ሴናተር ቴድ ክሩዝ በሽብርተኝነት ተከሶ ቤቱ ከስክንድር ነጋ ጋር ነበር የሚሆነው። ማን ያውቃል ወይም አንድ ጊዜ አንቺ ጋ ሆነ ተብሎ ተጽፎ እንዳነበብኩት ፈንጂ ሊያፈነዳ ሲዘጋጅ ራሱ ላይ ፈንድቶ ሞተ ተብሎ ይነገርና እስተወዲያኛው ይሸኝ ነበር። ዓለምን በደቂቃዎች ውስጥ ለፈጣሪዋ ማስረከብ የሚችል መሳሪያ ግምጃ ቤት ቁልፍ የያዘው አቶ ኦባማ አንጀቱ ሲቃጠል ይውላታል እንጂ የተቃዋሚዎቹን ዝንብ እንኳን እሽ ማለት አይችልም። ለነገሩ እዚህ አገር ሰው ፊት ላይ የሚፈነጭ ዝንብ የለም። ከስንት ጊዜ ብኋላ እሰው ፊት ላይ የሚያናጥር ዝምብ ያየሁት አንቺው ቴሌቪዥን ላይ ኢንተርቪው የሚስጠው ሰውዬና ጠያቂው ጋዜጠኛ አፍንጫ ላይ ነው። ኦኦ! ሰላምታዬን ትቼ ወደጎን ወሬ ሄድኩ መሰለኝ።
ለመሆኑ ሁሉም ነገር ደህና ነው። ሳሩ፥ ቅጠሉ፥ ወንዙ፥ እነዚያ ሰማይ የጓጎጡ ተራሮችሽና ከስማይ ሲያዩዋቸው ዘንዶ ይሚመሳስሉት ወንዞችሽ ሁሉ ደህና ናቸው? ዋልያው፥ ቀይ ቀበሮው ሁሉም ሰላም ነው? ስለደን ያልጠየኩሽ ከሞላ ጎደል አልቋል፥ የተረፈውንም የህንድና የዓረብ የሩዝ ገበሬዎች ይጠርጉት ይዘዋል የሚል ወሬ ሰምቼ ነው። እንደሽፍታ ገደላ ገደል ውስጥ አምልጠው የመሸጉትን ደኖች ሁሉ ባለ መጥረቢያና ሰደድ እሳት ካላሳብ ለዘር እንዳይተርፉ  እየመደመዳቸው ነው የሚል ወሬም እሰማለሁ። ጥሩ ነው። የተረፈውም የዱር አውሬ ሁላ እንደኔው መኖሪያ ሲያጣ ይሰደድልሻል። መጥረቢያና ጠመንጃ ተሸክሞ የሚዞር ሰው ምን እንደሚያስወድድሽ ፈጽሞ አይገባኝም። ገበሬዎችሽም ቀጥ ብሎ የቆመ ዳገት ማረሱን በርትተውበታል ይባላል። አፈር ስለረከሰብሽ ጭንጫ መሬት ሲቀርሽ የሚሆነውን እናያለን። በዚህ ላይ የኔን የስደት እድሜ በሚያክል ጊዜ ወስጥ ብቻ ያመረትሽው አፍ ብዛት በጥፍ አካባቢ መጨመሩን እሰማለሁ።  እግዜር የከፈተውን ጉረሮ ሳይዘጋው አያድርም የሚባለው ተረት ለድሮ መሆኑን ረስተሽዋል መሰለኝ። ሀይቆቹም ወደመሀል እየሸሹ ቀስ በቀስ ወደ በቆሎ ማሳነት እየተቀየሩ መሆኑን አንዳንዶቹም እንደቻይና ወንዞች በፋብሪካ ቆሻሻ መመረዝ መጀመራቸው ይወራል። ካህያ ጋር ሲውሉ ይመጣል የሚባለው ነገር መሆኑ ነው። ካላጡት ዓርዓያ ሹሞችሽ አንዴ ካልጠፋ የአውሮፓ አገር መርጠው ጉስቁሊቱን ኣልባንያን፥ ሌላ ጊዜ ደግሞ ምርት እስከተገኘ ድረስ ወንዙም ቢጠነባ ሰራተኛውም መርዝ ጠጥቶ ቢሞት ደንታ የሌለውን የቻይናን አራዊታዊ ካፒታሊዝም በሞዴልነት ይመርጡልሻል። ስንት ሰው አስተምረሽ ከራስሽ ተፈጥሮና ከውስጥሽ መድህኒት የሚፈልግልሽ ጠፋ። አንቺም በጎ የሚያስብልሽን ሰው አላስቀምጥ አልሽ። ኢትዮጵያኛ የሆነ ችግር መፍቻ ዘዴ የለም ማለት ውርደት የሚመስለው ሰው ጠፋ። መማር ማለት ፈረንጅ መጥቀስ ሆነ። አሁን ደሞ ድንጋይ ለመፍለጥ ሆኗል ሲባል እሰማለሁ። ሊቅነት የሚገኘው ከመማር ሳይሆን ከስልጣን የሚምስላቸው ሰዎች በገፍ አፈራሽ። አፍ አውጥቶ መናገር ወይ መጮህ አቃተሸ። ባለቤት ካልጮኸ ጎረቤት አይደርስም የሚል ተረት ለኔ አስተምረሽ አንቺ ዝም።
ለመሆኑ እነዚያ ልጆችሽ  ደህና ናቸው። እነ “የባስ አታምጣ”፥ አነ “ይህንስ ማን አየበት” እነ “ላይችል አይሰጠው” ደህና ናቸው? በህይወት መኖራቸውን አሰማለሁ። አንዴውም አምሮባቸዋል ይሉኛል አንቺ ጋ ደርሰው የተመለሱ ሰዎች። “የባሰ አታምጣን”ና “ይህንስ ማን አየበት”ን በቀደም ቴሌቢቪዥንሽ ላይ ያየኋቸው መሰለኝ። ልጆችሽ አፍሪካ ዋንጫ ተወዳድረው ተሽንፈውና መጨረሻ ወጥተው ሲመጡ በተገኘው ውጤት ሕዝቡ እንዲደሰት እዚህ መድረሳችን ታምር ነው እያሉ ሲኩራሩና ህዝቡን ሲሰብኩ ያ የኋቸው መሰለኝ። ከሀምሳ ዓመት በፊት የዚያ ዋንጫ ባለቤት የነበርን መሆኑን፥ ዛሬ የሚያሽንፉን ሁሉ ያኔ ፈረንጅ በባርነት ፈንግሎ ይገዛቸው የነበሩ ሰዎች መሆናቸውን እያወቀ ትንሽ የቁጭት መልክ የማይታይበትን “ይኸንስ ማናየበት” ባየሁት ቁጥር ይገርመኛል። አንዳንዴ ሳስበው ከነዚህ ቁልቁል በወረዱ ቁጥር ቁጭት ከማይሰማቸው ልጆችሽ ይልቅ ገና ለገና ድንጋይ ተወረወረብኝ ብሎ ሰው ጉረሮ ላይ ካልተሰካሁ ብሎ ለገላጋይ የሚያስቸግረው ያ ያብዬ ሻረው ውሻ ለራሱ ያለው ክብር የሚበልጥ ይመስለኛል።
እኔ ደህና ነኝ። ላንቺ ይብላኝ እንጂ ሰደቱን ለምጄዋልሁ። ከመልመዴ የተነሳ ስደተኛ መሆኔንም ረስቸዋለሁ። ዱሮ ሰው በላ እያልን የምንጠራው የዛሬው የስደት ሀገሬ መሆኑ ትዝ ባለኝ ቁጥር ሳቄ ይመጣል። ያንቺ ልጆች አንዳንድ ጊዜ የሰው ስም ስናጠፋ ዓይናችንን አናሽም። ይኸው ሐያ ዓመት ስኖር አበላኝ እንጂ በላኝ ወይም ሊበላኝ ነበር የሚል ሰው አጋጥሞኝ አያውቅም። እንደመጣሁ ጥገኝነት የሰጠኝ ሀላፊ ፊት ቀርቤ ተጠየቅ ስባል ስራ የሚለው ቦታ ላይ “ስራ አጥ” አስብለሽ ያጻፍሽበትን ፓስፖርቴንና ማመልከቻዬን እያገላበጠ “አገርህ እንዴት ትምህርት ረክሷል ባክህ፤ ሁለት ዲግሪ ይዘህ ነው ሰራ አጥ የሆንከው? በል ለኛ ጥሩ ሲሳይ ትሆናለህ ማለት ነው” እያለ ሲቀልድ ይኸ ሰውዬ እንበላሀለን ነው እንዴ የሚለኝ ብዬ አሳብ ይዞኝ ነበር። ያሾፈው በኔ ሳይሆን ባንቺ መሆኑ የገባኝ ቆይቶ ነው።
ለምጃለሁ እናትዬ። ስመጣ ንክች አላረገውም ያልኩትን ምግብ ሁሉ ካላሳብ እበላለሁ። ድሮ ኳኳታ ብቻ ይመስለኝ የነበረው የጃዝ ሙዚቃ የነፍሴ ምግብ ሆኗል። መጀመሪያ ሳየው የበጎች ውጊያ ይመስለኝ የነበረውን የዚህ አገር ፉትቦል በፍቅር መውደድ ከጀመርኩ ሰነበትኩ። ቡድኔን ጊዮርጊስን ረስቼው ዛሬ የዋሽንግተን ሬድ ስኪንስ ቲፎዞ ሆኛለሁ። ኒውዮርክ ታይምስን ሳላነብ ካደርኩ ያመኛል። ያ “አዲስ ነገር” የሚባል ጋዜጣ ቆይቶ ኒውዮርክ ታይምስን ይሆንልሻል ብዬ ተመኝቼልሽ ነበር። ጋዜጣውንም አዘጋጆቹን በላሻቸው አሉ።
ያንቺን ፍቅር ቢተካልኝም ባይተካልኝም ይህንን የስደት ሀገሬን ወድጄዋለሁ። ከልቤ እንደምወደው ያወኩት ጥላሁን ገሰሰ ስምሽን እየጠራ ባንጎራጎረ ቁጥር ጸጉሬ የሚቆመውን ያህል ሬይ ቻርለስ “አሜሪካ ዘ ቢዩቲፉልን” ሲዘፍን ስሰማ ጸጉሬ ሲቆም ሲሰማኝ ነው። የስደት ሀገሬን የምወደው ሆዴን ስለሞላልኝ መስሎሽ ያን ሆዳም የሚባለውን ክፉ ስድብሽን እንዳታሰድቢኝ። ብዙ ያንቺ አገር ሰው ሁሉንም ነገር ፍቅርንም ከሆድ ጋር ማያያዝ ይወዳል። ስድቡ ሁሉ ሆዳም ነው። በልቶና ጠግቦ ማደር የብዙ ሰው የህይወት ግብ በሆነበት አገር ሰው ለምን ሆዳም ተብሎ እንደሚሰደብ አንዳንድ ጊዜ አይገባኝም። እዚህ የኔ ስደት ሀገር በልቶና ጠግቦ ማደር ትልቅ ነገር አይደለም። ምግብ የተትረፈረፈ ከመሆኑ የተነሳ አንዳንድ ጊዜ ተርፎን የምንደፋው ከምንበላው ይበልጣል። በቀደም አንድ ባለሞያ በሂሳብ አስልቶ እዚህ ባንድ ሳምንት ተርፎ የምንደፋው ምግብ አንቺን የሚያክል ሁለት አገር ዓመት ይቀልባል አለኝ።  ለማንኛውም የስደት ሀግሬን ለሆዴ ብዬ የምወደው ከመሰለሽ ተሳስተሻል።
ይህን የስደት አ ገሬን የምወድበት ምክንያት ነገሩ ወዲህ ነው።  አንደኛ ነገር ሰውና የሰው ነፍስ ክቡር የሆነበት አገር ነው። የሰው የመጀመሪያ መለያ ሰው መሆን ነው። እንዳንቺ ብሄር ብሄረሰቡ አይደለም የሰው ልጅ ዋና መለዮ። ከሰው በላይ ሕግ እንጂ ሰው የለም። ሕግ ማለት ደግሞ ለይስሙላ ወረቀት ላይ የሚጻፍ ሲፋጅ በማንኪያ ሲበርድ በጣት የሚዝቁት ገንፎ አይደለም። ሕግና ሕገመንግሥት ዜጋን ከጥጋበኛ መንግሥት መከላከያ እንጂ መንግሥትን መጠበቂያ አይደለም። እዚህ አገር የገዥ ፓርቲና የመንግሥት ገንዘብ ለየቅል ነው። አይነካካም። አቶ ኦባማ የቢሮውን ስልክ አንኳን ተጠቅሞ የፓርቲውን ስራ ሲሰራ ቢገኝ ጉዱ ነው የሚፈላው። አንቺ ጋ የታክስ ከፋዩ ህዝብና የፓርቲው ገንዘብ ተደባልቆ እንደሚሰራበት ሰምቻለሁ። ጋዜጠኛ አንቺ ጋ ነጋ ጠባ ይጠበሳል። በኔ ስደት ሀገር ደግሞ ጋዜጠኛ ከህግ የወጡና ሀላፊነታቸውን ያጓደሉ የመንግሥት ባለስልጣናትን እያገላበጠ ይጠብሳል። በየቀኑ መንገድሽ ላይ እየቆመ አላሳልፍ የሚል መንግሥት የለም። አርፎ ስራውን የሚሰራ ሰው ባመት አንድ ወይም ሁለት ቀን ወይ የታክስ ዕለት ወይም መንጃ ፈቃዱን ለማሳደስ ሲሄድ ነው ከመንግሥት ጋር ፊት ለፊት የሚገናኘው።  ባጭሩ እዚህ ህዝብ የሚነዳው መንግሥት እንጂ ህዝብ እንደ እንስሳ መንጋ የሚነዳ መንግሥት የለም።  እኔ ልጅሽ በሀያ አመት ውስጥ ከፖሊስ ጋር የተገናኘሁት አንድ ቀን ብቻ ነው፥ ያውም በገዛ ጥጋቤ። 65 ማይል በሰዓት የተፈቀደ አውራ መንገድ ላይ በ85 ስነዳ አነዳዴን አይቶ ይከታተለኝ የነበር ፖሊስ ከኋላዬ መጥቶ አስቆመኝ። ብዙ አላስቸገረኝም። የመቀጫ ትኬቴን ስጥቶ አደጋ ላይ እንዳልወድቅ መክሮ ሰላምታ ሰጥቶ ባምስት ደቂቃ ውስጥ አሰናብተኝ። በቃ ይኸው ነው።
የዚህ አገር መንግስት ቴሌቪዥንም ሬዲዮም ስለሌለው ማታ ቤቴ ስገባ እደነቁራለሁ ብሎ ስጋት የለም። ስልጣንና እውቀትን አደባልቆ የሚያይ ባለስልጣን ሺ ጊዜ አብልጬ በማውቀው ጉዳይ ላይ ሊያስመልሰኝ እስቲተናነቀኝ ዉሸት ሊግተኝ ይንጠራራብኛል ብሎ ስጋት የለም። ታጋይ፣ ካድሬ፣ ቀበሌ ብሎ ነገርማ ባገሩ የለም።  የመንግሥት የድጋፍ ሰልፍ፥ የተሀድሶ፥ የግምገማና የንቃት ስብሰባ የሚባል የስራ ፈት ስራ የለም። ድሀ የሚበላው እንጂ የሚከፍለው አያጣም በሚል ፍልስፍና ነጋ ጠባ መዋጮ የሚጠይቅ መንግሥት የለም። እዚህ እንደ ጉራፈርዳና ቤኒሻንጉል ከክልሌ ውጡ ብሎ የሚያስቸግር መንግሥት የለም። ከየትም ሄዶ የትም ርስት ገዝቶ መኖር ይቻላል። በገዛሁት ርስት ላይ ደግሞ ነዳጅ ባወጣበት ወይም ማዕድን ባገኝ አምጣ ወይም ጥለህ ሂድ የሚለኝ የለም። ያለሁበት ሀገር ሀብታም የሆነው በምትሐት እንዳይመስልሽ። እዚህ አገር ክልል ማለት ሀብታም ገበሬዎች ከብት የሚያረቡበት ሰፋፊ በረት ነው። አንቺ ጋ የመንግሥት ሹም ኤክስፐርትና ምሁራንን ሰብስቤ ካላሰለጠንኩ ይላል። የዚህ አገር ሹማምንት ምንም የተማሩ ቢሆኑም እንኳን ከባለሞያ ከፍለው ምክር ይገዛሉ። እዚህ አገር ያሉ ፖለቲካኞች አብዛኛውን ጊዚያቸውን የሚያጠፉት ስለነገ በመጨነቅ እንጂ ባለፈና ባጨቃጫቂ ታሪክ ላይ በመነታረክ አይደለም። ታሪክ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እንጂ በየሜዳውና በየቀበሌ ስብሰባ ላይ የማንም ጥራዝ ነጠቅና ረኸጥ ወሬኛ እንዳሻው ሲያቦካው የሚውል ሊጥ አይደለም። እና ታዲያ ይህን የመሰለ አገር ለምን አልወደውም?
ደሞ እኩያዬ ካልሆነ አገር ጋር ለምን ታወዳድረኛለህ ትይኝ ይሆናል ያንቺ ነገር። አንቺ እኮ በድሜ ከሁለት ሺ አምስት መቶ ዓመት በላይ ስለምትበልጭው አገር ነው የማወራው። ባለራዕዮቹ መሪዎቻቸው ምንም ባሪያ ፈንጋይ ቢሆኑና ቢደላቸውም ከሁለት መቶ ዓመት በፊት ራሳቸውን ከበታቹ ሆነው ሊታዘዙት ወስነው ባወጡት ሕገ መንግሥት ነው ዛሬ ድረስ የሚተዳደሩት። እስቲ አስቢው እነሱ ከሁለት መቶ አመት በፊት ያወጡትን ዘዴ ማውጣት አንቺ ዛሬና አሁን እንዴት ያቅትሻል? ደሞ አብሬ ኖሬ ሳያቸው ከቆዳ ቀለም በቀር ካንቺ ልጆች የተለየ የተፈጥሮ ባህርይ ምንም የላቸውም። እንደኛው ስዎች ናቸው። አንዳንዶቹን ዛሬ የምናስተምራቸው እኮ እኛው ያንቺው ልጆች ነን።
ይህንን አንዳንዴ በዕዝነ ልቦናዬ እየመጣሽ አንተ ከሃዲ በሌላ ለወጥክኝ አይደል፣በችግር አሳድጌ አስተምሬህ ዛሬ ሲመችህ ከዳኸኝ አይደል? እያልሽ የምትጨቀጭቂኝን ስለመድሀኒዓለም ብለሽ ተይኝ። እንዴ! ምን አርግ ነው የምትዪኝ? ፈረንጅ አገር እኮ ስማር ከርሜ ወዳንች ከተመለስኩ ዓመት እንኳን አልሞላኝም ነበር ሹሞችሽ ያቅሜን ያውም በድህነት ላገለግልሽ ከምሰራልሽ ሥራ ሲያባርሩኝ ዝም ብለሽ ያየሽኝ። መካር ተው አትሂድ ሲለኝ ነው እኮ ዘልዬ ወዳንች የመጣሁት። አዲሶቹ ገዢዎችሽ ሲመጡ ከምር በጎ ነገር ያመጡ ይሆናል ብዬ ልረዳቸው ተነስቼ ነበር። ጥላቻ አሽነፋቸው መስለኝ ጠሉኝ። ያገኘሁትን ሰርቼ እንኳን እንዳልኖር የሚያደርጉኝን ነገር አይተሻል። ጎዳና ተዳዳሪነት ተመኙልኝ። ጥላቻቸው እንዳይጋባብኝ ክፉኛ ፈርቼ ነበር። ጥላቻ ጠይውን ይበልጥ እንደሚጎዳ ስለማውቅ መጥላት አልወድም። በድርጊታቸው እንድጠላቸው ሳይሆን እንድንቃቸው ስላደረጉኝ አመሰግናቸዋለሁ። በዚህ ላይ ያንን አስራ ስባት ዓመት የልጅነት እድሜዬን እንዴት እንዳሳለፍኩት ታውቂያለሽ። ነፍሴ የተረፈችው የሎተሪ ያህል ዕድል አግኝታ እንጂ ጓደኞቼማ የት ወድቀው እንደቀሩ የምታውቂው አንቺው ነሽ። እናት አባቴ ለኔ ብለው ከጠላት ተዋድቀው ባቆዮት ሀገር እንዴት ነው ዘላለም አጎንብሼና ፈርቼ እንድኖር የምትፈርጅብኝ? ለውለታቸው ክፍያ አልጠየቁ። ሌላ ቢቀር ለፍተው ያስተማሩት ልጃቸው ቀና ብሎ መሄድ ሲከለከል ምን ይሰማሻል? ይህን የቁም ሞት እየኖርኩ ካንቺ ጋር ብኮራመት ምን እጠቅምሻለሁ? ተይ እንጂ። እንዴት ነው ባንቺ ብሶ የምትውቅሽኝ። ለመሆኑ መንዝ ጌራና ላሎ መጋጠሚያ ቆላ ውስጥ ያለውን አመጠኜ ዋሻን አንቺም እንደሰው ረሳሽው? አመጠኜን ትልቁን ያርበኞች ምሽግ ዋሻ ነው የምልሽ ረስተሽው እንደሆን። ከዚያ እየወጡ ነበር ጣሊያንና የባንዳ ሰራዊቱን እብድና እውር ያደርጉት የነበረው የኔ ዘመዶች። ጣሊያን ምሽጉን መስበር ሲያቅተው ያገኘው ሰይጣናዊ ዘዴ የመርዝ ጋዝ የያዘ በርሜል ካፋፍ ዋሻው በር ላይ አንጠልጥሎ ማፈንዳት ነበር።  በመቶዎች የሚቆጠሩ አንበሶች እዚያው በመርዝ ጭስ ፈጃቸው። አንድ ዘመዴ ነበር በልጅነቴ አጽማቸውን እያሳየ እያለቀስ ያስጎበኘኝ። እንደ ውለታና ታሪክ አክባሪ አገሮች ብትሆኚ ኖሮ የኔን የዘመዳቸውን ቀና ብሎ መሄድ ማስከበር በቻ ሳይሆን ለጀግኖቹ አመጠኜዎች በቦታው ሀውልት አሰርተሽ የቱሪስት ማዕከል ታደርጊው ነበር። አንቺ ደስ የሚልሽ የገዛ ወንድሙን የገደለ የርስበርስ ጦረኛ ጀግና እያሉ ማሞገስና ሀውልት መስራት ሆነ። ቁርጡን ልንገርሽ። ዉለታ በላ ሀገር ባለውለታ ትውልድ አያፈራም። ችግርሽም ይህ ይመስለኛል። ያገለገሉሽን ማስከበር አቅቶሻል። ካንቺ አልለይም ብሎ ሙጥኝ ብሎ የሚኖረውን እኔን፣አስተማሪዎቼንና ያስተማሪዎቼን አስተማሪዎች ያስተማረ የሶስት ትውልድ መምህር ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያምን ምን እንደምታስደርጊው የማላውቅ መሰለሽ?  የሚወርድበትን የመደዴ ስድብ ሀይ ማለት ያቅትሽ፤ እንዴት ወህኒ ቤት በሰማኒያ አመቱ ታሳጉሪዋለሽ? ኑ ሞግቱኝ ስላለና ስለተከራከረ? ሃሳቡ ተቀባይነት የለውም ቢባል እንኳን ይህ ሁሉ ይገባዋል? ትንንሾቹ  ልጆችሽ ትልልቆቹ ባለክብረ ህሊናዎች ሲዋረዱ እያየን እንዴት ላንቺም ለራሳችንም ክብር እንዲኖረን ትጠብቂያለሽ።
ደሞ ለምን እዚሁ ሆነህ እንደ አገሩ ልማድ ጠምንጃ አንስተህ ሸፍተህ አልሞከርከውም እንዳትዪኝ።  ይህን ርስ በርስ እየተጋደሉ ጀግና እየተባባሉ የመኮፈስ ወግሽን አልወደውም። በዚህ ላይ ጠመንጃና መጥረቢያ አልወድም ብዬሻለሁ። ከፈለግሽ ፈሪ ልትዪኝ ትችያለሽ። መብትሽ ነው። ጠመንጃ የጠላሁት ገና ትንሽ ልጅ ሆኜ ነው። ጥምቀት ለማክበር ይመስለኛል በዚያውም ዘመድ ለመጠየቅ ባላገር ዘመዶቼ ጋ ሄጄ ነበር። አንድ እንደብርቅ የሚወደኝ አጎቴ ተኩስ ላስተምርህ ብሎ አረህ ይዞኝ ወረደ። ጭር ካለው ቆላ ውስጥ ከፊቴ ኢላማ እያሳየ ሲያስተኩሰኝ ያሳየኝን ኢላማ ሁሉ አልመታሁትም። መጨረሻ ላይ በይ አሁን ግዳይ ትጥያለሽ አለና ከበላያችን አለው ተረተር ላይ መሬት የሚጭሩ ዝንጀሮዎች መሀል አስተኮሰኝ። (ሞት ሲመጣ ተሳሳትኩ ብሎ እንዲመለስ ነው አሉ የኔ ዘመዶች ወንዱን አንቺ ሴቱን አንተ እያሉ የሚጠሩት)። ዝንጀሮዎቹ ደንብረው ከሸሹ በኋላ ቦታው ደርሰን ስናይ አንዲት ግልገል ዝንጀሮ አይኗን እያንከራተተች ስታጣጥር አገኘናት። አጎቴ ደስ የሚለኝ መስሎት “የኔ አምበሳ ደረቷን ነው ያገኘሽው” እያለ ሊያኩራራኝ ሲሞክር እኔ በሀዘን ተጨማድጄ መፈጠሬን ነበር የጠላሁት። ለጨዋታ እየዘለልሁ የወጣሁት ልጅ በሀዘን አጎንብሼ ነው የተመለስኩት። ያን ሰሞን ህልሜ ሁሉ ቅዠት ሆኖብኝ ከረመ። ከዚያን ቀን በኋላ ጠመንጃ ያስጠላኛል። እኔ ዝንጀሮ ስለገደልኩ ያን ያህል ሌት ተቀን ያባነነኝን ቅዠት አስታውስና ሰውን ያህል ፍጡር አነጣጥረው ገለው በሰላም እንቅልፍ ይዟቸው የሚያድር ሰዎች እንዴት ከራሳቸው ጋር እንደሚኖሩ መገመት ይከብደኛል። እናም እናቴ እንደፍጥርጥርሽ ሁኚ እንጂ እኔ ሰው ላይ አልተኩስም። በዚህ የሚገኘው ጀግንነትም ባፍንጫዬ ይውጣ።
እምዬ ብዙ ክፉ አናገርሽኝ። ጠልቼሽ ግን እንዳይመስልሽ ይህን ሁሉ የምወርድብሽ። እጆችሽን ዘርግተሽ ለተሻለ ዘመን እንደምትጸልዪም አውቃለሁ። እጅሽ ዝሎ ከመሰብሰቡ በፊት ግን አምላክሽን ወይ ውረድ ወይ ፍረድ ብለሽ ወጥረሽ ብትይዢው ይሻላል። የመከራሽን ጊዜ ያሳጥርልሽ ይሆናል። አትፍረጂብኝ እናት አለም። እሁን ብመጣም የማረግልሽ ነገር የለም። ሰርቶ ያልጠገበ፣ ምን ልፍጠር ያለ ጎረምሳ ሽኝተሽ እሁን በስተርጅና ብመጣ ምንም አላደርግልሽም። ልጅ ሆኜ ሳረጅ የበግ ርባታ ገበሬ እሆናለሁ የሚል ምኞት ነበረኝ። ያን ጊዜ “ርስት በሺ ዓመቱ ለባለቤቱ” ይባል ስለነበር ትውልዴን ቆጥሬ በግ ማገጃ የሚሆን መሬት የማጣ አይመስለኝም ነበር። ዛሬ ባለርስቱ መንግስት ስለሆነ ድፍን ኢትዮጵያ የመንግሥት ጭስኛ ሆኗል።  ኩርማን መሬት በየከተማው በቶኪዮ ዋጋ በመጋዞ እንደሚሽጥም ሰምቻለሁ። አባቶቻችን “የልጅ ደንጋዛ ያባቱን መሬት ይጋዛ” ይሉ ነበር ርስቱን በጉልበተኛ ተነጥቆ መልሶ የራሱን ርስት ተጋዝቶ የሚያርስ ገበሬ ሲያዩ። ዛሬ አብዛኛው ልጅሽ ደንግዞ ያባቱን መሬት መጋዛትም እንዳቃተው እሰማለሁ።
አንድ ነገር ደሞ ልንገርሽ። ይህንን ሬናይሰንስ (ህዳሴ) ላይ ነሽ የሚሉሽን ሰዎች ተዉ በያቸው። መንገድና ግንብ መስራት መጥፎ አይደለም። ህዳሴ ግን ትርጉሙ ይህ አይደለም በያቸው እነዚህን ስልጣንና ዕውቀት የተምታታባቸውን ሰዎች። ህዳሴ የሚጀምረው ጭንቅላት ውስጥ መሆኑን ንገሪ። አብርሆተ ህሊናን፣ ሕግን፣ ሥነ ጥበብን፣ የህሊና ነጻነትን፣ የምርምር ፍንዳታንና በራስ መተማመንን ሌላም ብዙ ነገርና ሁለንተናዊ ትንሳኤን የሚያካትት ነገር ነው በያቸው። አትሸንገይ። እኔ ነገሩ የቀፈፈኝ ያባይን ድልድይ ጃፓኖች ሙሉ በሙሉ በራሳቸው ገንዘብ ሰርተው ካስረከቡን በኋላ “ህዳሴ ድልድይ” ተብሎ በጠቅላይ ሚንስትሩ ተሰየመ የተባለ ጊዜ ነው። ልመና ብዙ ገብዘብ ሊያስገኝ ይችላል። ህዳሴ ግን አያመጣም። ጽድቁ ቀርቶ በወጉ በኮነነሽ። በባዶ ቤት ወግ መጠረቅ ራት አይሆንም።
ሟቹ ገዠሽ አቶ መለስ አፈሩ ይቅለለውና ከሰራቸው ስራዎች ሁሉ አባይን ለመገደብ መነሳቱን እንደትልቅ ቁም ነገር አይቼለት ነበር። ሀሳቡ ካንድ የጎሳ ብሄርተኛ ይመጣል ብዬ አላሰብኩም ነበር። ውጥኑን ስሰማ ደብዳቤ ጽፌ አመሰግነዋለሁ ብዬ ነበር። ሕዳሴ የሚለውን ስያሜ ከፈለገ ግን ሌሎች ማድረግ ስላለበት ነገር ሳልነግረው ስለሞተ ይቆጨኛል። ምናልባት እሱ ከነገረን ነገር ውጭ ውልፍት ካልን እንኮነናለን ብለው ለሚፈሩ ደቀ መዛሙርቱ ነግሮልን ይሄድ ነበር። ይህን የሚያክል ፕሮጀክት በባዶ ኪስ ጀምሮ አብሮት የሚሄድ የፖለቲካ ጥበብና ፈቃደኝነት ከጎኑ ሳያስቀምጥ መቅረቱ ያለውን ችግር ልነግረው ፈልጌ ነበር። ልጆችሽ ምንም ብንወድሽ እንደ እንስሳ እየተነዳን፣ እንጨት እንጨት የሚል ፕሮፓጋንዳ እየጠጣንና እየተሰደብን የምንሰራው ነገር አለመሆኑን ምንም የዋህ ብትሆኚ የምታጭው አይመስለኝም። የድሆችሽን መቀነት በማስፈታት የምትሰበስቢው መዋጮ ቆሞ እዚህ የኔ ስደት ሀገር ያለነው ልጆችሽ ብቻ ያለን ቢያልቅብን በክሬዲት ካርድ ተበድረን እንሰራው ነበር ግድቡን።  የምንሰራው ግን ለሰማይ ቤት ጽድቅ ብለን ሳይሆን ከነሙሉ ያንቺ ልጅነት ክብራችንና ነጻነታችን ጋር ይህም የሚፈጥረውን የባለቤትነት ስሜትና ርካታ ተላብሰን መሆን ይኖርበታል። አንድ ቀን ለዚሁ ተብሎ መንግስት እዚህ አገር ድረስ መጥቶ በጠራው ስብሰባ ያለኝን ልረዳ ሄጄ ነበር። ያዳራሹን በር የከበቡት አድር ባዮች ገና ለገና የሚነገረውን አርፎ አይሰማም ወይ ጥያቄ ይጠይቅ ይሆናል ብለው ከበር ላይ መለሱኝ። ገንዘቤን እንጂ ነጻነቴን አልፈለጉም። አቤት አድር ባይ ለመፈልፈል ያለሽ ችሎታ! ያላማራቸውን ሰው ሁሉ ከበር ሲመልሱ ግድቡን ጨርሰው የሚሰሩት እነሱ ይመስሉ ነበር። ያወጡትን ገንዘብ ያህል ብዙ እጥፍ መልሰው የሚመነትፉ ጀግኖች ናቸው ይህን የሚሰሩት።
ለማንኛውም ልማት ጥሩ ነገር ቢሆንም ልማት ሁሉ ህዳሴ አለመሆኑን ከሰሙሽ ንገሪ። የጥሩ ነገር ስም ማበላሽት ሳያስፈልግ ሊሰራ የሚቻለውን መስራት ይቻላል ብለሽ በያቸው። አንቺ ኮ ገና እምቦቀቅላ ልጆቿን ከባርነት ላልተናነስ ግርድና አረብ ሀገር ልካ የምታስቃይ አገር ነሽ፤ ወጣት የተባለ ሁሉ ስደትን መንግሥተ ሰማያት አርጎ ይሚመለከትባት ሀገር ነሽ፤ ያስተማረቻቸውን ሊቃውንት ሁሉ ለባዕድ ሲሳይ በገፍ የምትገብር ሀገር ነሽ፤ የዘመኑ የሳይንሰና ቲክኒዎሎጅ ምንጭ የሆነውን የኢንተርኔት መረብ በማዳረስ ካፍሪካ ግርጌ የቆምሽ አገር ነሽ፤ ሰው በተናገረውና በጻፈው ነገር አሸባሪ እያሰኘሽ የምታሳስሪ አገር ነሽ። አሁን ዶሮን በሬ ነሽ ብለው በመጫኛ ቢጥሏት ምን ይጠቅሟታል? የባዕድ ጽንሰ ሀሳብና በፈረንጅ ቋንቋ መጠቀም ካለሽበት ይሚያንፏቅቅሽ አይመስለኝም። ከበርቴዎችሽና ባለስልጣኖችሽ  ሚስታቸው ስታረግዝ እዚህ አገር እያመጡ እንደሚያስወልዱ ታውቂያለሽ። ልጃቸውን ያን ሁሉ ንብረታቸውን አውርሰው የተንቀባረረ አገልጋይ ዜጋሽ እንደማድረግ ገና ሳይወለድ ሲያስቀሙሽ አየሻቸው? እነሱ ለልጃቸው ያልተመኙትን ሀገር ታዲያ ማን ይመኝ እምዬ? ለመሆኑ ምን ሆነው ነው ይህን የሚያደርጉት? መቼም በደህናቸው አይደለም። በቀደም ለት አንድ በዚህ አገርና ባውሮፓም እንደራሴሽ (አምባሳደርሽ) የነበረ የተከበረ ሰው እዚሁ የኔ ስደት አገር አንድ የመንግስት በጎ አድራጎት ድርጅት ቢሮ ውስጥ ከሚስቱ ጋር ተሰልፎ አየነው ብለው ሰዎች ነገሩኝ። ክብርሽ እዚህ ድረስ ወርዶልሻል። ቀደም ብሎ ሚስቱንና ልጆቹን በጎን ጥገኝነት አስጠይቆ ከመንግስት ፈቃድ ጠይቆ በሰላም ነው አሉ የመጣው። እዚህ በኛ ላይ በውሽት ሳይቀር ሲያሳብቅ የከረመ ሰው እንደነበር ካዝረከረከው ዶሴ ላይ አንድ ጊዜ አይቼ ነበር። ምን ምን አይነቱን ሰው ነው እየመረጥሽ የምታግበሰብሽው? አሁን ይኸ ማ ይሙት ህዳሴ ላይ ያለች አገር ባህሪ ነው?
ሌላም እንድ ነገር ልንገርሽ። ይህን ከመንግሥት ጋር ጣጣ ያለውን ሁሉ አሸባሪ ማለትን ተዉት በይ። ዘላለም ተከባብረው የኖሩ ሙስሊምና ክርስቲያን ልጆችሽን ለማጣላት የሚደረገውን የሰይጣን ስራ አቁሙ በይ። በነገሩ ውስጥ እኔ ምንም የሽብር ነገር አላየሁም። ይህ የኔ የስደት ሀገር ያሸባሪ ችግር የገጠመው ነገሩ ወዲህ ነው። ክንፉ ረጂም ስለሆነ ዓለምን ከአጽናፍ አጽናፍ ይነካል። ጡንቻውም አንዳንዴ የሚያርፍበት ቦታ ነገር ያመጣል። አውሮፓዎቹም እንደዚያው ነው። አንቺ የለት ጉርስ ማሟላት ያቃተሽ ድህነት ያሸበረሽ አገር ነሽ። ግዥዎችሽ አርፈው ከተቀመጡ አንቺን ለማሸበር እንቅልፍ አጥቶ የሚያድር ባዕድ ያለ አይመሰለኝም። የውስጥ አምባጓሮኛ ሁሉ ደሞ አሸባሪ አይደለም። ከታሪክሽ ታውቂዋለሽ። መፍትሔው የከፋቸውን ሁሉ ሰብስቦ መነጋገርና መፍትሔ ማበጀት እንጂ አሽባሪ ማለት አጉል ፈልፈላ መጥራት ነው። ጦም ውሎ ማደርንና እንደነገሩ ኖሮ መሞትን ያህል ሽብር ያለብሽ ሀገር የገዛ ልጆችሽ ምን ሁኝ ብለው ያሸብሩሻል። ይህን ነገር ብዙ መዘዝ ሳያመጣ  አስቁሚ። ነገሩ የሚፈታው ሰው በማሰርና በመግደል ሳይሆን በመወያየት ነው። አየሽ መወያየት ሰው አይገልም። በመጋደልና በስቃይ መንገድ ያለውን ሁሉ ሞክረሽዋል። የውይይቱን መንገድ ደግሞ ለለውጥ ያህል እንዲሞከር ምከሪ።
በይ እናት አለም ስለጮኩብሽ ይቅርታ። ዉቢቱ ለምለሚቱ እያሉ የሚፎግሩሽ ብዙ ስለሆኑ ነው እኔ የምር የምሩን የነገርኩሽ። ክፉሽን እንዳልሰማ እዚሁ ሆኜ እጸልይልሻለሁ። ካላንቺ የማይሞላ ተልቅ ጉድጓድ አሁንም በሆዴ ውስጥ አለ። ከርቀት ተለቅሶ የማይወጣ እምባ አጠራቅሜበታለሁ። ከወለደችኝ ጀምሮ ነጋ ጠባ ተንበርክካ፣ አምላኩዋን አስቸግራ በህይወት የምንሳፈፍበት ክንፍ ከእግዚአብሄር ያሰጠችኝን የናቶች ሁሉ እናት፥ ቀዥቃዣው አንድ ልጇ ዘላለም አደጋ ውስጥ በተማገድኩ ቁጥር በክንፋቸው ከልለው የሚያወጡኝ መላዕክት ልመና ከቤተ ክርስቲያን በር ላይ የምትገኘውን እናቴን፥ የደግነትና የፍቅር መምህርቴን፣ የርሀብ መድሃኒቴን እማዬን ቀብሯ ላይ ተንበርክኬ ሳላለቅስላት ስለቀረሁ ፈስሶ ያላለቅ እምባ በሆዴ ጉድጓድ አለ። እንኳን ሀዝንና ለቅሶ ደስታም በስደት አያምርም አይደል።
ሰላምና ፍቅር አብዝቶ ያስፍንብሽ። አልረሳሽም እናትዬ፥ ብረሳሽ ቀኝ እጄ የምትሰራውን ትርሳ።
Fekadeshewakena@yahoo.com