Monday, December 23, 2013

የኢህአዴግ አዲሱ አሰላለፍ ፪ (ተመስገን ደሳለኝ)


   በድህረ-መለስ ኢትዮጵያ የፖለቲካው ሥልጣን በስርዓቱ ልሂቃን መካከል ከሚደረገው የኃይል መተናነቅ አንጻር፣ ዛሬም ከመፈራረቅ ጣጣው የተላቀቀ የማይመስልባቸው ምልክቶች መታየታቸው እንደቀጠለ ነው፡፡ ከአራት ወር በፊት በዚህ መፅሄት ላይ ‹‹አዲሱ የኢህአዴግ አሰላለፍ›› በሚል ባቀረብኩት ፅሁፍ በገዥው ፓርቲ ውስጥ ተፈጥሮ ከነበረው ክፍፍል የትኛው ቡድን የበለጠ ጉልበት አግኝቶ በአሸናፊነት መውጣት እንደቻለ ከገለፅኩ በኋላ ፅሁፉን የቋጨሁት እንዲህ በማለት ነበር፡- ‹‹የፓርቲው የታሪክ ድርሳን እንደሚነግረን ‹ይሆናሉ› የተባሉት ተቀልብሰው፣ ባልተጠበቁ ሁነቶች (የኃይል መገለባበጥ ተከስቶ) ፖለቲካው የሚመራበት አጋጣሚ
ሊፈጠር የሚችልበት ዕድል ሊኖር እንደሚችልም መዘንጋት አያስፈልግም፡፡›› 
  እነሆ በዚህ ፅሁፍ ደግሞ በቅርቡ በተጨባጭ የታዩትን አዳዲስ ኩነቶች እና ይህንኑ ተከትለው ሊመጡ ይችላሉ ብዬ የምገምታቸውን ‹የቢሆን ዕድሎች› (Scenarios) ለማየት እሞክራለሁ፡፡ 
         ሰላም የራቀው - ኢህአዴግ
    በግንባሩ አባል ድርጅቶች መካከል ዛሬም ድረስ ሙሉ በሙሉ የተረጋጋ ፖለቲካ አልሰፈነም፤ የዚህ ዋነኛ ምክንያቱ ደግሞ፣ ቁልፍ የሥልጣን ቦታዎችን ጠቅልሎ ይዞ በነበረው በቀድሞ ሊቀ-መንበሩ ህልፈት ሳቢያ የተፈጠረው የአመራር ክፍተት እና እርሱን ሊተካ የሚችል መሪ ማግኘት ባለመቻሉ ይመስለኛል፡፡ እንዲህ አይነት አጋጣሚዎችም በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባለ ከሕግ ይልቅ የጠመንጃ ኃይልና የግለሰብ አምባገነናዊነት በገነነበት ሀገር ‹የማይገመቱ ክስተቶች› (Unpredictable Event) ማምጣታቸው የሚጠበቅ ነው፡፡ 
  የሆነው ሆኖ በዚህ አጀንዳ ለመመልከት የምሞክረው ጉዳይ፣ በአሁኑ ጊዜ ሀገር እየመራ ያለው ኃይል ለሁለት የተከፈለ ቢሆንም፣ በአንፃራዊነት በጥምር የሚሰራ መሆኑን በማስረገጥ ነው፡፡ የእነዚህ ሁለት ቡድኖች የጉልበት ምንጭም የታጠቀውን ኃይል በመቆጣጠር እና የፖለቲካውን ሥልጣን በመያዝ ላይ የተመሰረተ ነው፤ ይኸውም ሠራዊቱ እና የደህንነት መስሪያ ቤቱ ሙሉ በሙሉ በህወሓት ሰዎች ሲንቀሳቀሱ፣ ፖለቲካውን ደግሞ የብአዴን መሪዎች፣ ከተወሰኑ የኦህዴድና ደህአዴን የአመራር አባላት ጋር ተባብረው መያዛቸውን የሚያሳዩ ምልክቶች መኖራቸው ነው፡፡                                                የህወሓት ኃይል 
   ህወሓት የቀድሞው ፍፁማዊ የበላይነቱን ለመመለስ ዋና ችግር የሆነበት በውስጡ ለተፈጠረው መከፋፈል እስካሁን መፍትሄው ተለይቶ አለመታወቁ ነው፤ ከዚህ ቀደም በዚሁ መፅሄት፣ አንዱ ኃይል የተሻለ ጉልበት በማግኘቱ ሌላኛውን (እነአዜብ መስፍንን ጨምሮ አባይ ወልዱና ቴዎድሮስ ሀጎስን የመሳሰሉ ከፍተኛ ካድሬዎች የተሰባሰቡበትን) በመብለጥ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን እንቅስቃሴያቸውን መገደቡ ተሳክቶለት እንደነበረ ማስነበቤ ይታወሳል፡፡ ይህ ክፍፍል ምንም እንኳ እንደ 1993ቱ ከፓርቲ እስከ ማስወጣት የሚደርስ አለመሆኑ ቢታወቅም፣ ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል እና ጌታቸው አሰፋ የተሰለፉበት ቡድን ተፅእኖ ፈጣሪ ሆኖ መውጣት ችሏል፤ ይህም ሆኖ ውስጥ ውስጡን የሚገመደው ተንኮልም ሆነ ሽኩቻ ገና መቋጫ አለማግኘቱ ግልፅ ነው፡፡    
   በዚህ ፅሁፍ ጠመንጃ የታጠቀውን ክፍል ‹የህወሓት ኃይል› እያልኩ የምገልፀበት ዓብይ ምክንያት፣ በጄነራል ሳሞራ የኑስ ኤታ ማዦር ሹምነት የሚመራው የመከላከያ ሠራዊት እና በማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ጌታቸው አሰፋ ስር ያለው የደህንነት ኃይል ለሚደግፉት ቡድን መጠናከር እያበረከቱት ያለውን አስተዋፅኦ ከግምት በመክተት ነው፡፡ ሁለቱም ሰዎች ለመለስ ፍፁም ታማኝ የነበሩ ቢሆንም፣ ከህልፈቱ በኋላ እንደእርሱ ተጭኖ ሊቆጣጠራቸው የሚችል ጉልበታም ህወሓትን ጨምሮ በሁሉም የግንባሩ አባል ፓርቲ ውስጥ አለመኖሩ፣ በፖለቲካው ‹ቼዝ› የ‹ዘመነ መሳፍንቱ›ን ሚካኤል ስሁል አይነት ሚና እንዲጫወቱ አስችሏቸዋል፤ ሁለቱም ከስራቸው የነበሩትንና ‹ስልጣን ሊጋፉ ይችላሉ› ብለው የጠረጠሯቸውን ባልደረቦቻቸውን አስቀድሞ ገለል ማድረጉ ከሞላ ጎደል የተሳካላቸው ይመስለኛል፡፡ በተለይም ጌታቸው አሰፋ ከራሱ ወንበር አልፎ ከእነአዜብ መስፍንና አባይ ወልዱ ጋር በመተባበር አንድ ቀን በጠቅላላው የመንግስት የሥልጣን እርከን ላይ ‹ናቡቴ ሊሆን ይችላል› የሚል ስጋት ያሳደረበትን እና ‹መለስ ዜናዊ ሞት ባይቀድመው በእርሱ ቦታ ሊተካው ነበር› እየተባለ የሚነገርለትን የመረጃ ኃላፊ ወልደስላሴ ወልደሚካኤል በሙስና የሚወነጀልበትን መንገድ አመቻችቶ ለእስር ባይዳርገው ኖሮ ‹‹ለቁርስ ያሰቡንን…›› አይነት ታሪክ ራሱን መድገሙ አይቀሬ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡  
   ጄነራል ሳሞራ የኑስ በበኩሉ ተቀናቃኙ አድርጎ ይመለከታቸው የነበረው ሶስቱ ከፍተኛ መኮንኖች እንደ ወልደስላሴ ‹ፍንቀላ መሳይ ነገር ሊሞክሩ ይችላሉ› ተብለው አይደለም፡፡ የእነርሱ የመጀመሪያው ችግር ከወታደራዊ ዲሲፕሊን በማፈንገጥ አለቃቸውን አለማክበራቸው
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ሳሞራ ‹በየትኛውም ምክንያት ከኃላፊነቴ ብነሳ የቆየ ፋይል አገላብጠው አደጋ ላይ ሊጥሉኝ ይችላሉ› በሚል ስለሚጠረጥራቸው ነው፡፡ እነዚህ መኮንኖች የሰሜን ዕዝ አዛዥ ሌፍተናንት ጄነራል ሰዓረ መኮንን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ መልካም ግንኙነታቸው እንደቀድሞው እንዳልሆነ የሚነገረው የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌፍተናንት ጄነራል አበባው ታደሰ እና የአየር ኃይሉ አዛዥ ሜጀር ጄነራል ሞላ ኃይለማርያም ናቸው፡፡ እናም ሰዓረ እና አበባው በቀጥታ ሠራዊት ከሚያዙበት ቦታ ተነስተው በመከላከያ ሚኒስትር ውስጥ በቢሮ ስራ ላይ ሲመደቡ፣ ሞላም ከነበረበት ኃላፊነት አኳያ ብዙም ይመጥነዋል የማይባል የቢሮ ስራ ተሰጥቶታል፤ በእርሱም ቦታ ሜጀር ጄነራል አደም መሀመድ ተተክቷል፡፡ የሳሞራ እና የሞላ ልዩነት በመለስ ዘመንም በአደባባይ የሚታወቅ እንደነበረ ሰምቻለሁ፡፡  
ለጉዳዩ ቅርብ ከሆነ የመረጃ ምንጬ እንዳረጋገጥኩት የአስተዳደር ዘይቤውን በማኪያቬሊያዊ አስተሳሰብ (ከፋፍለህ ግዛ) የሚያሳልጠው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፣ ለሞላ ትዕዛዝ የሚሰጠውም ሆነ ማንኛውንም ጉዳይ በተመለከተ የሚያነጋግረው የዕዝ ተዋረዱን ጠብቆ በኤታ ማዦሩ በኩል ሳይሆን፣ በቀጥታ በመገናኘት መሆኑ፣ አየር ኃይሉን ከመከላከያ ሚኒስቴር የተገነጠለ አስመስሎት ነበር፤ ይህ ሁኔታም በሁለቱ መኮንኖች መካከል ያለው ግንኙነት የሥልጣን ተዋረድን የጠበቀ እንዳይሆን በማሰናከሉ በጄነራሉ ላይ ደፍሮ የማይናገረው ቅሬታ ሊያሳድርበት ችሏል፤ ከመለስ ህልፈት በኋላም ሳሞራ ሂደቱን ለማስተካከል መሞከሩ፣ በየግምገማው ላይ እስከ መዘላለፍ አድርሷቸው ነበር (በነገራችን ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ እንደ ጦር ኃይሎች አዛዥነቱ፣ ከጄነራሎቹ ጋር መደበኛ /Official/ በሆነ መንገድ ትውውቅ አላደረገም፤ እነዚህ ሶስት ጄነራሎችም ለዚህ አይነቱ የአሰራር መፋለስ ጥፋተኛ የሚያደርጉት አለቃቸውን ሳሞራ የኑስን ነው፤ ከምንጮቼ እንደሰማሁት ከሆነም ከወራት በፊት ኃይለማርያም ደሳለኝ በተገኘበት ‹ጎልፍ ክለብ› በሚባለው የጄነራሎቹ መዝናኛ በተዘጋጀ ፕሮግራም ማጠናቀቂያ ላይ ሳሞራ አንድ ጠረጴዛ ከበው ወደ ተቀመጡት እነዚህ ጄነራሎች ጋ ሄዶ ‹ኑ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ላስተዋውቃችሁ› ማለቱን እና እነርሱም በጥያቄው ተበሳጭተው ቢሮ ያላቸው መሆኑን እና ክብራቸውን በሚመጥን መልኩ መተዋወቅ እንደነበረባቸው በኃይለ ቃል መመለሳቸውን ነው)       የሳሞራ የኑስ እና ሰዓረ መኮንን መነቋቆር ከትግሉ ዘመን ጀምሮ የመጣ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ሳሞራ ከማንም በላይ የሚፎካከረውም ሆነ መበለጥ የማይፈልገው በሟቹ ጄነራል ኃየሎም አርአያ እንደ ነበር የቀድሞ ጓዶቻቸው ያስታውሳሉ፤ ይህ ሁኔታ ዛሬም ድረስ በስራ ላይ ያሉ መኮንኖችን ‹የሳሞራ› ወይም ‹የኃየሎም ተከታይ› በማለት መከፋፈሉ በጓዶቻቸው እና በፓርቲው መሪዎች አካባቢ የሚታወቅ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ለማዕረግ እድገት የተለየ የድጋፍ አስተያየት የሚያገኙት በዛን ዘመን ‹የሳሞራ ተከታይ› የሚባሉት እየተመረጡ እንደነበረ በወሬ ደረጃ ይናፈሳል (በነገራችን ላይ ጄነራል ሳሞራ ከጤንነት ጋር በተያያዘ በአጭር ጊዜ ውስጥ በጡረታ ይሰናበታል በተባለበት ጉዳይ ላይ እያንገራገረ እንደሆነ ከመከላከያ አካባቢ የሚወጡ መረጃዎች ያመላክታሉ፤ እንደ ምክንያት የሚጠቀሰው ደግሞ ‹ለእኔ በጎ አመለካከት የላቸውም› በሚል የሚጠራጠራቸው ጄነራሎች በሥራ ላይ እያሉ የእሱ ጡረታ መውጣት ከመስሪያ ቤቱ ጋር ተያይዘው የሚነሱ ያደሩ የሙስና ካርዶች የሚመዘዙበትን ዕድል ያሰፋዋል የሚል ነው፤ በተለይም በግዙፍ የቢዝነስ ሥራዎች ላይ በታላቅ ተፎካካሪነት እየተሳተፈ የሚገኘው ‹መቴክ› ምንም እንኳ ማረጋገጫዎች ባይቀርቡበትም በመከላከያ ሥር ከነበረበት ዘመን እስከ 2002 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ ከግዥዎች ጋር ተያይዘው የሚነሱ በርካታ የሙስና ሁኔታዎች በመኖራቸው ነው፡፡ መቴክ ካለፉት አራት ዓመታት ጀምሮ በአዋጅ የልማት ድርጅት እንዲሆን ቢደረግም፣ ዛሬም ዳይሬክተሩ የሠራዊቱ አባል ብርጋዴር ጄነራል ክንፈ ሲሆን፣ መከላከያ ደሞዝ የሚከፍላቸው ጥቂት የማይባሉ ሠራተኞችንም እንዳቀፈ ይታወቃል፡፡ እናም ሳሞራ ሃሳቡ ከተሳካለት ለጥቂት ተጨማሪ ዓመታት በሥልጣኑ ላይ ሲቀጥል፣ አሊያም ‹የወንድ በር› ለማግኘት በትግሉ ዘመን የእርሱ ሰልጣኝ እንደነበረ የሚነገርለትን እና በቅርቡ ብቸኛው ከሜጀር ወደ ሌፍተናት ጄነራል ማዕረግ ያደገው ዮሀንስ ገ/መስቀል እንዲተካው መንገድ ጠረጋውን ማመቻቸቱ ትኩረት ሰጥቶ የሚሰራበት ጉዳይ ይመስለኛል)  
  ይህም ሆኖ የተኮረኮርን ያህል የምንስቀው ጄነራል ሳሞራ የኑስ በቅርቡ ለታተመው ‹‹ህብረ ብሔር›› መፅሄት ሙስና ለሠራዊቱ አደገኛ መሆኑን እንዲህ በማለት መግለፁን ስናነብ ነው፡- ‹‹ ሙስና ሠራዊቱን ሊያበላሸው ይችላል፡፡ ሙስና ፀረ - ልማት ነው፤ ሠራዊቱን ሊበትነው እና ሕዝባዊ ባህሪውን እንዲያጠፋ ሊያደርገው ይችላል፤ አንድ ሠ ራዊት ሠራዊት ነው የሚባለው እንደ ወታደር እንደ አንድ አካል ሲያስብ እንጂ ለግሉ ሲያስብ አይደለም፡፡ … በአጠቃላይ ( ሠራዊቱ ) በዚህ ነው የሚፈርሰው፡፡ ›› 
    መቼም ጄነራሉ ይህንን የተናገረው እራሱን ጨምሮ በርካታ ከፍተኛ መኮንኖች እንደ እንግሊዝ ንጉሳውያን ቤተሰቦች በተንጣለለ ቪላ ቤት ውስጥ፣ የተቀማጠለ ኑሮ መኖራቸውን ረስቶት አይመስለኝም፤ ‹ይህ የተንዛዛ ወጪያቸውም የሚሸፈነው ከደሞዛቸው በሚያገኙት ገቢ ነው› ብሎ ቧልት መሳይ ክርክር ሊያመጣ አይችልም፡፡ ይሁንና እታች ያለው ጭቁን የኢትዮጵያ ሠራዊት ምንም እንኳ በአለቆቹ ‹ቴክሳስ›ነት ላይ ለመቆጣት ባይደፍርም፣ እንደማንኛውም ዜጋ ለኑሮ ውድነትና አስከፊ ድህነት የተጋለጠ መሆኑን መካድ አይቻልም፡፡            የሆነው ሆኖ ተሰሚነታቸው እየተቀዛቀዘ የመጣው አቦይ ስብሃት ነጋ ከወራት በፊት ለ‹‹ውራይና›› መፅሔት ‹‹ህወሓት ትንሳኤ ያስፈልገዋል›› በማለት የሰጡትን ምክር ተከትሎ፣ ጄነራል ሳሞራ እና አቶ ጌታቸው አሰፋ፣ ከድርጅቱ ምክትል ሊቀ-መንበር ዶ/ር ደብረፅዮን ጋር በመተባበር ህወሓትን ለማጠናከር እና በፖለቲካ ውስጥ የነበረውን የአንበሳውን ድርሻ ለማስከበር (ጉዳዩን ከለጠጥነው ደግሞ ‹ለማስመለስ›) እየሰሩ እንደሆነ ይነገራል (በነገራችን ላይ የሳሞራና ጌታቸው ተፅእኖ መጨመሩን ለመረዳት፣ መከላከያ ‹አገራዊ
ጥቅምንና ደህንነትን ለመከላከል› በሚል ‹እጅግ ጥብቅ ሚስጢር ብሎ የሰየማቸውን የሰው ኃይል ፕሮፋይል፣ የሒሳብ መዝገቦችና ሰነዶች እና የክፍያ ማስረጃዎች ለማንም አካል እንዳይገለፅ› የሚያስችለውን ስልጣን፣ ደህንነቱ ደግሞ በስራ ላይ የሚፈፅማቸው ማንኛውም ጉዳዮች ወደፊት በህግ እንዳይጠይቅ እስከ መከላከል የሚደርሰውን አዲስ የተዘጋጁትን አዋጆች ማንበቡ በቂ ነው፡፡ በርግጥ እነዚህ ባለሥልጣናት እንዲህ ባለ ተመሳሳይ መንገድ እንዲጓዙ ያስተሳሰራቸው አንዱ ጉዳይ ‹ህወሓት ተዳከመ፣ ተሸነፈ፣ አበቃለት…› የሚለው የካድሬውና ደጋፊው ቁጭት እንጂ ወትሮም መልካም ግንኙነት ኖሯቸው አይመስለኝም) 
   ለማንኛውም በጥቅሉ ሲታይ የህወሓት ትልቁ ችግር ተብሎ በአመራር አባላቱ የሚጠቀሰው ‹በዚህ ወቅት ወደፊት መምጣት የሚችሉ ጠንካራ ቴክኖክራቶችን አለማፍራቱ፣ ሁለንተናዊ ድጋፍ የሚያደርግለትን የታጠቀውን ኃይል ተጠቅሞ የፖለቲካ ልዩነቱን ጨፍልቆ በአሸናፊነት ይዞት መውጣት የሚችል መሪ እንዳይኖረው አደረገ› የሚል ነው፡፡ በርካታ የላይኛ እና የታችኛው ካድሬዎችም ‹ለእንዲህ አይነቱ ክፉ ጊዜ ድርጅቱ የሚያስፈልገው፣ በትግሉ ዘመን ልምድ ያካበተ ታጋይ ብቻ ነው› የሚል አቋም እንዳላቸው ይነገራል፡፡ ስርዓቱ ከሚያራምደው ርዕዮተ-ዓለም ጋር ጠንካራ ትውውቅ ያሌለውን እና የትግሉን ዘመን በአሜሪካን ሀገር በማሳለፉ ‹የምዕራባውያን ድጋፍ አለው› ለሚባለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የሚሰጡት ዝቅተኛ አመለካከት መግፍኤም ይኸው ይመስለኛል፡፡ ለነገሩ እርሱም ቢሆን በጠንካራ ድርጅታዊ ዲሲፕሊን ካለመታነፁ እና መሰል ጉዳዮች ጋር በሚያያዙ ምክንያቶች ለትንፋሽ ጊዜ የማይሰጠውን የድርጅት ሊቀ-መንበርነትንም ሆነ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ የሚወራውን ያህል ይፈልገዋል ብሎ መደምደሙ አስቸጋሪ ነው ብዬ አስባለሁ፤ ከዚህ ይልቅ በተፈጥሮ ከታደለው የተግባቢነት ባህሪው አኳያ እንደ ሕዝብ ግንኙነት የመሳሰለ ብዙም የማያጨናንቅ ሥራን ይመርጣል፡፡ ለዚህም ይመስለኛል ከሰለጠነበት ሙያ ጋር የቀጥታ ተያያዥነት ያለውን የጤና ጥበቃ ሚኒስትር በሚመራበት ዘመን፣ ከውጭ ሀገር በርካታ የተቋረጡ ፈንዶችን እንደገና ለማስለቀቅ መቻሉ እንደ ታላቅ ስኬት የሚወራለት፤ አልፎ ተርፎም ‹ወባን ከኢትዮጵያ ምድር ለማጥፋት ብርቱ ትግል አደረገ› ተብሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሳይቀር እስከ መሸለም የደረሰው እዚህ መስሪያ ቤት እያለ እንደሆነም ይታወቃል፡፡ 
  በሌላ በኩል ደግሞ በፓርቲውም ሆነ በመንግስት አስተዳደር ከህወሓት ሰዎች ትልቁን ስልጣን የያዘው ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል ከምዕራባውያን ጋር የቆየ ቀረቤታ እንዳለው ሰምቻለሁ፤ እንደሚታወሰው ደብረፅዮን ከክፍፍሉ በፊት (የደህንነት መስሪያ ቤቱ እንዲህ እንደ ዛሬው እጅግ ዘመናዊ በሆነው የቻይና ቴክኖሎጂ ሳይጥለቀለቅ) ከነበረው ከፍተኛ የሥልጣን ቦታ ላይ ተነስቶ፣ ቁልቁል ወርዶ በሁመራ በአንድ ዞን እንዲሰራ የተመደበው (ሁላችንም ስንገምት እንደነበረው) የአንጃው አባል ወይም ደጋፊ ሆኖ አይደለም፤ ይልቁንም የእነስዬ-ተወልደ ቡድን በመባል የሚታወቀው (‹አፈንጋጩ› ኃይል) ደብረፅዮንን በሲ.አይ.ኤ እና ሞሳድ ወኪልነት የመክሰሱ ጉዳይ የድርጅቱን በርካታ አባላት ቀልብ በመሳቡ፣ መለስ ይህንን ተከትሎ ከሚመጣበት አደጋ ራሱን ለመከላከል የወሰደው እርምጃ በመሆኑ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት እስከ 1998 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በሁመራና ራያ አካባቢዎች በዞን ደረጃ ለማገልገል ተገዷል፡፡ እናም እርሱን የምዕራቡ ዓለም ፊት-አውራሪ አሜሪካና ሸሪኮቿ ወዳጅ ነው የሚያስብለው በቀድሞ መስሪያ ቤቱ በኩል በነበረው ግንኙነት ይመስለኛል።             የፖለቲካውን መዘውር የጨበጠው ኃይል 
   የዚህ ቡድን አምበል እንደ ድርጅት ብአዴን ቢሆንም፣ በቋሚ ተሰላፊነት ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ አባዱላ ገመዳ፣ ሙክታር ከድር እና ሬድዋን ሁሴን እንደሚገኙበት ይነገራል፤ ለብአዴን ‹በተሻለ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ለመገኘቱ መደላድል ፈጥሮለታል› የሚለውን ሙግት ምክንያታዊ የሚያደርገው ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፖሊሲና ጥናት ምርምር አማካሪ በረከት ስምዖን፣ የኢህአዴግን የካድሬ ማሰልጠኛ ማዕከል በዳይሬክተርነት የሚመራው አዲሱ ለገሰ፣ ደርቦ ይዞት የነበረውን የትምህርት ሚኒስትርነት ለሽፈራው ደሳለኝ በመልቀቅ፣ በአሁኑ ወቅት ሙሉ የስራ ጊዜውን በግንባሩ ፅ/ቤት የሚያውለው ም/ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን እና የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈ-ጉባኤው ካሳ ተክለብርሃን የያዙት ሥልጣን ያለውን የፖለቲካ አቅም መመዘኑ ይመስለኛል፡፡ በመከላከያ ሠራዊቱ ውስጥም ከሳሞራ አንድ እርከን ዝቅ ባለ ሥልጣን ከሌሎች ሁለት ጄነራሎች ጋር የሚገኘው አበባው ታደሰ እንደ ቀድሞው በዕዝ አዛዥነቱ (በቀጥታ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ወታደሮችን ማንቀሳቀስ የሚችልበት) ላይ ቢሆን ኖሮ ጥንካሬውን የተሟላ ማድረጉ አይቀሬ እንደነበረ መገመት ይቻላል፡፡ 
 ከዚህ ሌላ ለእነበረከት ቡድን ተጨማሪ የፖለቲካ ጉልበት እየሆናቸው ያለው የኃይለማርያም ደሳለኝ ቢሮ እና በአባዱላ ገመዳ አፈ- ጉባኤነት የሚመራው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው፡፡ አባዱላ፣ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ሪፖርት ለማቅረብም ሆነ ለመታዘዝ ፍቃደኛ ያልሆኑ አንዳንድ ባለስልጣናት፣ በውስጥ መስመር በሚተላለፍለት ‹ጥቅሻ› በምክር ቤቱ በኩል የሚመለከተው የቋሚ ኮሚቴ አባላት አስጠርቶ የተሰጠውን ኃላፊነት የሚገመግምበት ስልት እየተገበረ ነው፡፡ በአናቱም ምን ጊዜም የሳምንቱን የሥራ መጨረሻ ቀን አርብን ጠብቆ የሚሰበሰበው የሚኒስትሮች ም/ቤትን ከሞላ ጎደል ይህ ቡድን እየጠቀመበት ይመስለኛል፡፡ በርግጥ ሚኒስትሮቹ በሚገናኙበት አብዛኛውን ሰዓት ሳይግባቡ (በጭቅጭቅ) ማሳለፋቸው ይነገራል፤ የዚህ ምክንያቱ ደግሞ በአቶ መለስ ዘመን ም/ቤቱ የሚሰበሰበው የተለያዩ አጀንዳዎችን ለማቅረብ እና በቀረበው አጀንዳ ላይ ለመከራከር (ለመመካከር) ሳይሆን፣ መለስ ወስኖ የመጣበትን የሥራ ድርሻ ተቀብሎ ለመበተንና ሪፖርት ለመስማት የነበረው አሰራር፣ ዛሬ ተቀይሮ በርካታ የተነቃቁ ሚኒስትሮች የየራሳቸው ሃሳብ ተቀባይነት እንዲያገኝ (ለማንፀባረቅ) የሚታገሉበት መድረክ ወደ መሆን በመሸጋገሩ ነው፡፡ ይህም ሁናቴ ዋናውን የመንግስት ሥራ የመገምገም እና
የማስፈፀም አቅምን ሳይቀር ከሚኒስትሮች ም/ቤት ወደ ኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ አሻግሮታል የሚያስብሉ ማሳያዎች አሉ፡፡ ይሁንና በዚህ ስብሰባ ላይም ቢሆን ደፈር ብሎ ከበረከት ስምዖን እና አባይ ፀሀዬ የተሻለ አዳዲስ ሃሳብ የሚያቀርብ ባለሥልጣን እንደሌለ ሰምቻለሁ (በነገራችን ላይ ምክንያቱን ባላውቅም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹የፖሊሲና ጥናት ምርምር አማካሪ› ተደርገው የተሾሙት በረከት ስምዖን፣ አባይ ፀሀዬ፣ ኩማ ደመቅሳ እና ዶ/ር ካሱ ኢላላ የሥራ ቦታቸው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ፅ/ቤት ሳይሆን መገናኛ አካባቢ በሚገኝ አንድ ህንፃ ላይ ነው፡፡ የተሰጣቸው ኃላፊነት ኃይለማርያምን በቅርብ እንዲያገኙ ከማስገደዱ እና በግልፅ ከሚታወቀው የአማካሪ አስፈላጊነት አኳያ ካየነው ግን ግራ የሚያጋባ ይመስለኛል)  
          ጠቅላይ ሚኒስትሩ … 
      ኃይለማርያም ደሳለኝ ይህንን ቦታ ከያዘ በኋላ፣ ብዙዎች በስልጣኑ የማዘዝ አቅሙ ላይ አመኔታ እንደሌላቸው (አንጋፋ ታጋዮች እንደ ‹አሻንጉሊት› ሊጠቀሙበት እንደሚችሉ) ደጋግመው መግለፃቸው ይታወሳል፡፡ በግልባጩ ‹አፈንግጦ ለመውጣት መሞከሩ አይቀሬ ነው› የሚሉ ግምቶች ነበሩ፡፡ በርግጥ እነዚህ መላ-ምቶች ዛሬም ድረስ እልባት ባያገኙም፣ እዚህ ጋ ያልጠቀስኳቸው አንዳንድ ጉዳዮች ላይ ያሳያቸው ወጣ ያሉ አቋሞቹን ሳስተውል ግን፣ አሁን ያለው አሰላለፍ (የአነበረከት እና አባዱላ ፖለቲካዊ መጠናከር) ለእርሱም የተረፈው ይመስለኛል፡፡ እንዲሁም ከቤንች ማጂ የተባረሩ አማርኛ ተናጋሪዎችን አስመልክቶ በድርጅቱ ውስጥ ባልተለመደ መልኩ ‹አጥፊዎቹ ላይ እርምጃ እወስዳለሁ› ከማለት አንስቶ (በነገራችን ላይ በአማካሪ ብዛት እንዲከበብ ካደረገው ምክንያት አንዱ ጓዶቹ በዚህ ንግግሩ መበሳጨታቸው ነው) በቅርቡ ህወሓትን ለመሸምገል በተዘጋጀ መድረክ ላይ ‹ሁኔታዎች እንዲህ እየተካረሩ ከሄዱ ወደ ማሰሩ መግባታችን አይቀርም› በማለት ማስፈራራቱ እና በቴዎድሮስ አድህኖም የሶሻል ሚዲያ አጠቃቀም ላይ የመቆጣቱ ጉዳይ ድረስ የሚካተቱ እውነታዎች ሰውየው የራሱን መንገድ ለመከተል እየሞከረ መሆኑን ያሳያሉ ብዬ አስባለሁ፡፡ 
    የሆነው ሆኖ እነዚህ ሁናቴዎች የፖለቲካውን ጉልበት ሙሉ በሙሉ በብአዴንና በተባባሪነት በጠቀስኳቸው የኦህዴድና ደህአዴን የአመራር አባላት አካባቢ ቢያከማቻቸውም፣ በማንኛውም ሰዓት ያሻውን ማድረግ የሚችለው የታጠቀው ኃይል ደግሞ ከህወሓት ጎን እንደተሰለፈ ይገኛል፡፡ መጪውን ጊዜም አዲስ ክስተት እንድንጠብቅ ገፊ ምክንያት ይህ አይነቱ የኃይል አሰላለፍ ይመስለኛል፡፡ 
            ምን እንጠብቅ ? 
   ከረጅሙ የፓርቲ ፖለቲካና መንግስታዊ መንገራገጮች በኋላ፣ የሁለቱንም የኃይል መሰረቶች ጠቅልሎ በመዳፉ ሥር የከተተው መለስ ዜናዊ በሞተ ማግስት ‹የኃይል መገዳደሮች ሊከሰቱ ይችላሉ› የሚለው የብዙዎቹ ግምት ነበር፤ ከወራት በፊት አስነብቤ በነበረው ከላይ በተጠቀሰው ፅሁፍም ግምቶቹ እውን መሆን እንደ ጀመሩ ማሳያዎች ማቅረቤ ይታወሳል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ ራሳቸውን ያቧደኑት ኃይሎች ዋነኛ ግብ ከሥልጣን የሚነሱ ጥቅሞችና አነስተኛ የየራሳቸው ፓርቲ ፍላጎቶች የፈጠሩት በመሆኑ፣ እንደ ሟቹ ደመ-ቀዝቃዛ አምባገነን አይነት በጠንካራ መዳፍ ሥር የሚያሰባስባቸው ባለመገኘቱ በየጊዜው የኃይል መሸጋሸጎች ሊከሰቱ እንዲችሉ አድርጓቸዋል፤ አሁንም እየተስተዋለ ያለው ይኸው እውነታ ነው፡፡ በዚህ አውድ ላይ ቆመን ሊፈጠሩ የሚችሉ የቢሆን ሃሳቦችን ስናስቀምጥም በጠረጴዛው ላይ የምናገኘው ሁለት ዕድሎችን ይመስለኛል፡፡  
  የመጀመሪያ ሲናሪዮ የሚሆነው ከላይ የጠቀስኩት ቡድንተኝነት እንዳለ ሊቀጥል ይችላል የሚል ነው፤ ይህም የሚሆንበት ምክንያት ባለኝ መረጃዎች መሰረት የፖለቲካውን መስመር የያዘው ቡድን መሪ አባላት፣ አሁን ያላቸውን መንግስታዊ ሥልጣን ጠብቀው መቆየትን መሰረታዊ መሰባሰቢያ አጀንዳ ማድረጋቸው ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የሳሞራና ጌታቸው ጥምረት ህወሓትን ወደ ቀደመው ዘመኑ ለመመለስ ቢሻም፣ ሊሄድበት የሚችልበት መንገድ አደገኛ መሆኑ (ወታደራዊ ላዕላይ መዋቅሩንና የደህንነት ኃይሉን ከመያዙ አኳያ) ሁኔታዎችን ባሉበት ይዞ መቀጠልን በትርፍ-ኪሳራ ስሌት የተሻለ አማራጭ አድርጎ ይወስደዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ 
   ሁለተኛው የቢሆን ዕድል፣ ዳግመኛ የኃይል መሸጋሸግ ሊፈጠር መቻሉ ነው፤ ሰዎቹ ጥቅመኛ በመሆናቸው የቋንቋ ተናጋሪነት ልዩነቶቻቸውንና የኋላ የመቆራቆስ ታሪኮቻቸውን ተሻግረው፣ አንዳቸው ከአንዳቸው ጋር ሌላ መልክ ያለው ስብስብ ሊፈጥሩ ይችሉ ይሆናል፤ ይህ አይነቱ አዲስ የኃይል አሰላለፍም፣ ከቀጣዩ ሀገራዊ ምርጫ በፊት በማይታወቀው ተሰዊና ሰዊ ሊጠናቀቅም ይችላል፡፡ 
    በመጨረሻም ምንም ይፈጠር ምን፤ እኛን ሊያግባባን የሚገባው ጭብጥ፣ የትኛውም ቡድን በግንባሩ ውስጥ ቢነሳ፣ የማዕከላዊ መንግስቱን ህልውና ወደሚበታትን ሂደት መግባቱ ሊሰካለት አለመቻሉ ነው፤ ምክንያቱም በዚህ መልኩ ሄዶ የሚጣሉበትን ጠረጴዛ መስበሩ ምን እንደሚያስከትል ያውቁታልና ወደዚህ ምዕራፍ እንደማይሻገሩ አምናለሁ፡፡ ይሁንና ከፓርቲው ዝግነት እና ከፖለቲከኞቹ አቋም የለሽነት አንፃር አሁንም ሆነ በቀጣይ ጊዜያት ከማንም ግምት ውጪ ያሉ ክስተቶች እንደ ደራሽ ውሃ ድንገት ሳይታሰብ ግንባሩን ሊያተራምሱት ይችላሉ ብሎ መገመቱ አግባብ ይመስለኛል፡፡