Saturday, December 28, 2013

ጃዋርና ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ (ክፍል 3)


ከዓለማየሁ መሀመድ (ክፍል 3)
አቧራው ጬሷል። ግለቱ ጨምሯል። ሙቀቱ አይሏል። የሳይበሩ ጦርነት ተጋግሏል። በሁሉም ወገኖች ትርፍና ኪሳራው ገና አልተሰላም። ከመነሻው ትርፋማ መሆኑ የተረጋገጠለት ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ዘና ፡ ከወንበሩ ለጠጥ ብሎ በትዝብት ፈገግታ ሁለቱን ወገኖች ይመለከታል። ቢቻለው ካራ አቀብሎ የፌስ ቡኩ ጦርነት ደም ወደ ሚያፋስስ ዕልቂት ቢቀየርለት ምንኛ በመረጠ?!Jawar Mohamed Muslim fundamentalist
በእርግጥ እያሰበበት ነው። የመረጃ ምንጮቼ ሹክ እንዳሉኝ ከሆነ የህወሀት ስሌት እስከ እልቂቱ የሚሻገር ነው። ሰሞንኛዋ ግርግርም አራት ኪሎ ቤተመንግስ ተቀምራ፡ ዋሽንግተን ዲሲ በህወሀት ኤምባሲ ተከሽና በእነ ጃዋር መሀመድ ታውጃ፡ ሺዎች በደመነፍስና በስሜታዊነት የተቀላቀሉት ስለመሆኑ ከበቂም በላይ መረጃው አለኝ።
ለዛሬ መረጃዎቹን ላካፍላችሁ። ማስረጃዎቹን እየጠበኩኝ ነው። የድምጽና የፎቶግራፍ ማስረጃዎቹ ከእጄ እንደገቡ ጀባ እንደምላችሁ ከወዲሁ ቃል እገባለሁ። በእርግጥ አንድ ላይ ላወጣቸው ነበር እቅዴ። ሆኖም የጬሰው አቧራን እየቃሙ ላሉት ወገኖች በተወሰነ ደረጃ ሰከን እንዲሉ፡ ሰማይ ምድሩን የበጠበጠው ንትርክ የኦሮሞ ህዝብን ብሶት ለመግለጽ ታስቦ  ሳይሆን በህወሀት መንደር ተዘጋጅቶ የቀረበ መርዛማ አጀንዳ መሆኑን በቶሎ እንዲያውቁት በሚል መረጃዎቹን ብቻ ላፈነዳቸው ፈለኩ። ሁለት ናቸው
መረጃ አንድ
ፋይሳል አልዬ ዓመታት የዘለቀ የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ኦህዴድ አባል ነው። እሳት የላሰ ካድሬ ይሉታል። ለህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ሰዎች ምቾት የሚሰጣቸው፡ በኦሮሚያ ክልል  ወጣቱ ለህወሀት ቀጥ ለጥ ብሎ  እንዲገዛ የቤት ስራቸውን በሚገባ የሚሰራላቸው በመሆኑ ፋይሳል በህወሀት መንደር ስሙ ወፍራም ነው። ወጣት ነው። ምላሱ ጤፍ ይቆላል የሚባልለት ዓይነት ነገር።
ጃዋርን ለመመልመል ጊዜ አልወሰደበትም። ጎረምሳው ጃዋር ከአከባቢው የነቃ፡ ነገር በቶሎ የሚገባው ስለነበረ የፋይሳል ቀልብ ውስጥ የገባው በጠዋቱ ነው። በእድሜም እኩያሞች የሚባሉ ናቸው። እናም ጎረምሳው ጃዋር፡ ሰተት ብሎ ኦህዴድን ተቀላቀለ። ኦህዴድ የበኩር ልጆቿን መልምላ ከጨረሰች በኋላ ለተለያዩ ተልዕኮዎች ማሰማራት ጀመረች። ጃዋር በአዲስ አበባ ቆይታው ውሎው ዶሮ ማነቂያ አከባቢ ካሉ ጫት ቤቶች ነበር። ጃዋርና ምልምል የኦህዴድ ካድሬዎች ብዙውን ጊዜ የስለላ ስራዎችን የሚያከናውኑት በዶሮ ማነቂያ አከባቢ በተሰገሰጉ ጫት ቤቶች ነበር። ጫቱን እያመነዥጉ ወሬ ሲለቃቅሙ መዋል የእነ ጃዋር መደበኛ ስራቸው ነበር።
በዚህን ጊዜ ወጣቱ ፋይሰል ወደ ዋሽንግተን ዲሲ የህወሀት ኤምባሲ ይዛወራል። ምሳዩን፡ እኩያውን፡ በግብርም በምግባርም የሚመስለውን ወዳጁን ጃዋርን ተስፋ ሰጥቶት ወደ ዲሲ ይበራል። ጃዋር እዚያው ጨፌ ኦሮሚያ ውስጥ ድርጅታዊ ተልዕኮዎችን እየተወጣ እያለ በመሃል ከወዳጁ ፋይሳል ጥሪ ይደርሰዋል። በትምህርት እድል ሰበብ ጃዋር ወደ አሜሪካ የሚመጣበት አጋጣሚ ይፈጠርለታል።
ለጃዋር የምስራች የነበረው ዜና እንደመጣች በኦህዴድ አማካኝነት ህወሀት ተልዕኮ ማዘጋጀት ጀመረ። የዲያስፖራውን ፖለቲካ ለመበጥበጥ፡ ጊዜ እየጠበቀ እንዲያተራምሰው የሚያስችል የቤት ስራ ተዘጋጀና በዋሽንግተኑ ፋይሳል መሪነት እንዲከናወን ህወሀት አዘዘ። ጃዋርን ይሄን ተልእኮ ሰንቆ ዋሽንግተን ዲስ ከተፍ አለ።
የህወሀት ኤምባሲ የጃዋር መሸሸጊያ ሆነ። ጠዋት ነግቶ ኤምባሲ ይገባል። ከፋይሳል ጋር ሲሰራ ይውልና ማታ ጸሀይ ስትጠልቅ ኤምባሲው አከባቢ ወደተከራዩለት መኖሪያው ይሄዳል። ለአንድ ዓመት ያህል በዚህ ሁኔታ ዘለቀ። አሁን ከወያኔ መንደር የተሰናበተው ብርሃኑ ዳምጤ አባመላ የቅርብ ግንኙነት ነበረው። ሻይ ቡና የሚባባሉት እነዚሁ የኤምባሲው ሰራተኞችና ባለልዩ ተልእኮ አስፈጻሚዎች ነበሩ።
ሁኔታዎች በዚሁ እየቀጠሉ እያለ ጃዋር ከሚኒሶታ የኦሮሞ አንድ ማህበር ጥሪ ይደረግለታል። ወንበር እያሞቁ መዋልና ማደር የሰለቸው ጃዋር ለሚኒሶታው ጥሪ ምላሽ ለመስጠት አልዘገየም። ጓዙን ጠቅልሎ ሚኒሶታ ገባ። ጽንፈኛ የኦሮሞ ብሄርተኞች ተቀባበሉት። ህወሀት ያዘጋጀው፡ ኦህዴድ ያስጠናው ተልኦኮ ለጊዜው አደጋ ገጠመው። የኦነግን የ40 ዓመት ሙዚቃ በቅርበት ለመኮምኮም ዕድል ያገኘው ጃዋር በሚኒሶታ ውርስ ነበር የጠበቀው። ያረጀውን፡ የሻገተውን የኦነግን ፍልስፍና አፈሩን አራግፎ ለማንሳት ቃል የገባው ጃዋር በዋና ጊዜው ትምህርት እየተከታተለ፡ በትርፉ ደግሞ የኦነግን ዜማ እያቀነቀነ የሚኒሶታውን ህይወት ጀመረው።
እነፋይሳል የጃዋር መክዳት ብዙም ያሳሰባቸው አይመስሉም። የተሸከመውን አደራ ሳይወጣ፡ ኮትኩታ ያሳደገችውን፡ ለወግ ማዕረግ ያበቃችውን ኦህዴድን(ህወሀት) ለጊዜው ተለይቷታል።
ፋይሳል በመሃሉ ወደ አዲስ አበባ ይመለሳል። በውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ትልቅ የሃላፊነት ቦታ ተሰጥቶት መስራት ይጀምራል። ጃዋር ደግሞ በዲያስፖራው ውስጥ እንዴት መሰስ ብሎ  መግባት እንዳለበት ሂሳብ ማስላት ጀመረ። በልቡ ውስጥ የኦነግን ነፍስ ተሸክሞ ወደ ተቀሩት ኢትዮጵያውያን መጠጋት ያዘ። እንደ ቪኦኤ፡ ዶቸቬሌ፡ ኢሳት የመሳሰሉ ሚዲያዎች ላይ ቀርቦ ሲናገር በእርግጥ እኔን ጨምሮ ጥቂት የማይባሉ የኢትዮጵያ ብሄርተኞች ጃዋር አልጎረበጣቸውም ነበር።
ጃዋር እዚህም እዚያም ይናገራል። ይጽፋል። ህወሀትን ያወግዛል። ኦህዴድን ይረግማል። በቃ! እውነተኛ ተቃዋሚ የሚል ታርጋ ተለጠፈለት። ወጣቱ የፖለቲካ ምሁር እየተባለ ይጠራም ጀመር።
ነገሮች ጃዋር ባሰባቸው መልኩ እየሄዱ ናቸው። እናት ድርጅቱን ኦህዴድን ለጊዜው ከድቷል። በልቡ የቀበረው የኦነግ ፍልስፍናም እዚያው ተዳፍኖ ይቀመጣል። ቀን ሲመጣ ሁለቱ ተስማምተው ይወጣሉ። የጃዋር ህልም እናት ድርጅቱን ኦህዴድንና የነፍሱ ማረፊያ የሆነውን ኦነግን ማጋባት ነው። ለዚህ ደግሞ ስሙን በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ መተከል አለበት። እያደረገው ዘለቀ።
እነፋይሳል ጸጥ ብለዋል። ጃዋር መጨረሻው ከየት እንደሆነ ያውቁታል። አስረዝመው አሰሩት እንጂ ፈተው አለቀቁትም። ጃዋርም ይህቺን ልቅም አድርጎ ያውቃታል። አንድ ቀን ወደ እናት ድርጅቱ እንደሚመለስ ያም ቀን እየቀረበ እንደመጣ ተረድቷል።
ፋይሳል በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ ሌላ ከፍተኛ ሃላፊነት ተሰጠው። የዲያስፖራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር። ጃዋር አልጀዚራ ላይ ቀርቦ ኦሮሞ ፈርስት ብሎ አውጇል። ከዚያም በፊት በሚኒሶታ አንድ መድረክ ላይ የሜንጫ አብዮት ቀስቅሷል። ከኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ተለይቶ ወደ ጽንፈኛው የኦሮሞ ጎራ ጠቅልሎ ገብቷል። አቧራው መጬስ ጀምሯል።
ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ፈተና ውስጥ ገብቷል። ከሀገር ቤትና ከባህር ማዶ የለውጥ ነፋስ እየነፈሰ ነው። ዲያስፖራው ወያኔን በየመድረኩ ማሳፈር፡ ማባረር ጀምሯል። የህወሀት ወንበር እየተነቃነቀ ነው። ዲያስፖራው የማይገፋ ተራራ ሆኗል። እነፋይሳል አሁን መነቃነቅ አለባቸው። ጃዋር የሚባል በዲያስፖራው ላይ የዘመተ ሃይል ተነስቷል። ፋይሳል ስልኩ አነሳ። ኢሜይሉን ከፈተ:: ….ጃዋር;;
መረጃ ሁለት
በኒውዮርክ የሚገኘው በመንግስታቱ ድርጅት የኢትዮጵያ ተልእኮ ጽህፈት ቤት ብዙ ሰራተኛ የለውም። አምባሳደሩ ዶክተር ተቀዳ ዓለሙ ለይስሙላ ይቀመጡ እንጂ እውነተኛ ስልጣኑ ያለው በሁለት ሰዎች እጅ ነው። ኮነሬል ገብሬ ገብረጻዲቅ የወታደራዊ አታሼውና የጽህፈት ቤቱ አንደኛ ጸሀፊ አቶ ኪዳነማርያም ግደይ የህወሀት ልዩ ተልእኮ አስፈጻሚ ናቸው። ዶክተር ተቀዳ ፕሮቶኮል ጠብቀው በየስብሰባው ይገኛሉ። እነኮነሬል ገብሬና ኪዳነማርያም ዋሽንግተን ዲሲ ካለው ኤምባሲ ጋር በመሆን የስለላና ሌሎች ድርጅታዊ ስራዎችን ያከናውናሉ።
ተቃዋሚዎችን በመሰለል፡ በገንዘብ እየሸነገሉ በማስከዳት፡ የተለያዩ ተለጣፊ ድርጅቶችን በማቋቋም የዲያስፖራውን እንቅስቃሴ የማዳከም ሃላፊነቱ እነዚህ ሁለቱ የህወሀት ሰዎች ላይ ወድቋል።
ጊዜው ለህወሀት ከባድ ሆኗል። ተቃውሞው በየቦታ ጠንከር ብሎ ተነስቷል። ህወሀት አደጋ ውስጥ ነው። እነኮነሬል ገብሬ የቤት ስራ ተሰጥቷቸዋል። ዲያስፖራው መበጠበጥ አለበት። ዘረኝነት ክፉ ነው። የኦሮሞ ዲያስፖራ ማህበረሰብ ራሱን ተጠቂ አድርጎ  የሚኖር በተለይ በአማራው ላይ ቂም ቋጥሮ የተቀመጠ ነው የሚል ድምዳሜ ህወሀት ዘንድ አለ። እናም ይሄን መቀስቀስ አንዱ ህወሀት እፎይታ የሚያገኝበት መንገድ ነው። ለዚህ ደግሞ ትክክለኛው ሰው ጃዋር ነው። ኮነሬል ገብሬ ስልካቸውን አነሱ። ጃዋር የሚኖረው እዚያው እሳቸው ካሉበት ከተማ ነው ኒውዮርክ።
ፋይሰል ከአዲስ አበባ ይደውላል። ኮነሬል ገብሬ ከኒውዮርክ ስልኩን እየመቱ ናቸው። ሁለቱም ከአንድ ቦታ ነው የሚደውሉት። ጃዋር ዘንድ።
ጃዋር አሁን ስራውን ጀመረ። የእናት ድርጅቱን ውለታ ለመመለስ ተዘጋጀ። አቧራውን አጬሰው። እንደተፈለገው እንደታቀደው የኦሮሞ ማህበረሰብ ብድግ አለ። ጽንፈኛው ሆ ብሎ ተነሳ። ህወሀት ለጊዜው እፎይ ያለ መስሏል።
በመረጃ ደረጃ ያገኘሁት እንደሚያመለክተው ጃዋርን ጨምሮ የተወሰኑ የኦነግ መሪዎች አዲስ አበባ ይገባሉ። ለዚህም አባዱላ ገመዳ እና ግርማ ብሩ ስራውን እየሰሩት ነው። ምናልባትም በቅርቡ ጃዋርና የኦነግ መሪዎቹ ኦህዴድን ይዘው ብቅ ሊሉ እንደሚችሉ ይጠበቃል።
እንግዲህ ይህ መረጃ በማስረጃ ተደግፎ ይመጣል። እነጃዋር ከህወሀት ጋር የፈጸሙት ጋብቻ ኢትዮጵያን በመበጥበጥ ላይ ያተኮረ ነው። ጊዜውን ልብ በሉ። ህወሀት ተዳክሟል። እያጣጣረ ያለውን ስርዓት ወደ መቃብሩ ሸኝቶ በእኩልነት ላይ የተመሰረተች ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ ነው እነጃዋር የዘረኝነት ካርድ አንስተው ህወሀትን ለማዳን ወገባቸውን ታጥቀው በማህበራዊ መድረኮች ላይ የዘመቱት።
ዘረኝነት ልብንም አይንንም ያውራል። የሰከነ ውይይት ለማድረግ የሚፈቅድ ትዕግስት አይሰጥም። በእርግጥ የተነሳው አቧራ ይጠፋል። ሰማዩም ይጠራል። እነጃዋር ለህወሀት ከቆሙለት ዓላማ ጋር በታሪክ ጥቁር ስም ታቅፈው ይኖሩዋታል። መልካም ንትርክ!!
 

እኔ አላውቅም ፈራሁ ጁሃር (ከሄኖክ የሺጥላ)

እኔ አላውቅም ፈራሁ ጁሃር (ከሄኖክ የሺጥላ)
ሄኖክ የሺጥላ
Poet Henok Yeshitela  የበደሌ ቢራ ፋብሪካ ከአዲስ አበባ 483 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ኢሉ-ኣባ-ቦራ ( Eloo The father of Holstein Friesian) ኢልባቡር ከተማ በሁለት መቶ ሃምሳ ሺ ስኩዌር ሜትር ይዞታ ላይ ስራውን እንደ ኣውሮጳውያን ኣቆጣጠር በ1993 ማከናወን የጀመረ ትልቅ የቢራ ማምረቻ ድርጅት ነው።
ኢሊባቡር መልካ-ምድራዊ ኣቀማመጡም ሆነ ምድራዊ ልምላሜው፥ እንደ በቆሎ ፤ ገብስ፤ ጤፍ፤ የቅባት እሎች፤ ማር፤ ከነ ቦራ ደሞ ወተት፤ ቅቤ እና ወዘተ የሚዘራባት፤ የሚታጨድባት፤ የሚቆረጥባት፤ የሚታለብባት ሃገር እንድትሆን ኣድርጉዋታል።
ኢሊባቡርን የጽሁፌ መንደርደሪያ አደረኩ እንጂ ዋናው ነጥቤ እሱ አይደለም። ዛሬ መናገር ወይም መጻፍ የፈለኩት ቴዲ አፍሮ በቅርቡ በመላው ኢትዮጵያ የሙዚቃ ዝግጅቱን እንዲያሳይ ወኪል የሆነውን የበደሌ ቢራን ያለመጠጣት አድማ ( boycotting) በመላው ኢትዮጵያ ይደረግ ዘንድ አንዳንድ ግለሰቦች የጀመሩትን ነገር ሰምቼ፤ ለምን በደሌን፤ ለምን ቴድን የሚል ጥያቄ ለሚጠይቁ፤ መልስ የሚመስለኝን ለመተየብ፤ ከተቻለም ለማሳየት መሞከር በመሻቴ ነው ።
ቴዲ አፍሮ በቅርቡ በጋዜጣ ላይ ስለ አድዋ ድል በሰጠው አስተያየት የተቆጡ፤ የተቀየሙ ግለሰቦች፤ ቴዲ አፍሮ “ጥቁር ሰው” ብሎ ንጉስ ሚኒሊክን፤ ከዛም በላይ አድዋ ድልን በመዘከሩ የተበሳጩ የህብረተሰብ አካሎች፤ ቴዲ አፍሮ ከዚህ ቀደም “ጃ-ያስተሰርያል” ብሎ በመዝፈኑ ቂም የቁዋጠሩ ሰዎች፤ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በሊግ ኦፍ ኔሽን በ 1936 የኢጣልያንን የተለከለ የኬሚካል መሳሪያ መጠቀምን በመቃወማቸው፤ ኢትዮጵያን የዩናትድ ኔሽን ኣባል በማድረጋቸው፤ ቅራኔዎችን አብርደው ያፍሪካን ህብረት በመመስረታቸው፤ ለነዚህ ጉልህ አስተዋጾዎቻቸው በመዝፈኑ፤ ለነዚህ ለተጠቀሱት መልካም ስራቸው መታሰቢያ የጭንቅላቱ ውጤት የሆነውን ሙዚቃ በማበርከቱ፤ ቴዲ አፍሮ ፤ አቀንቃኝና አዝማሪ ፤ ገጣሚና ስዓሊ፤ ሃያሲና ደራሲ፤ ጸሃፊ ተውኔቱና ብላታው፤ አፉን በለጎመበት ዘመን፤ በብእሩ የታሪክ ጋሻ፤ በግጥሙ ለቆሰለ ታሪክ ማገገሚያ፤ በዘፈኖቹ ( ከማሊ ሱፊዎች ባልተናነሰ መልኩ) የነብስን ክር እየተጫነ ያላስለቀሰው፤ ያላስተከዘው፤ ሰው እንደሌለ የገባቸው ሰዎች፤ በይበልጥም የአድዋ ድል፤ የጥቁር አንበሳዎች ድል መሆኑን ያሳየበት በመሆኑ እና ይህም የሚያማቸው ሰዎች፤ ዛሬ በደሌ ቢራ ቴዲ አፍሮን ስፖንሰር ስላደረገ፤ በደሌ ቢራን ያለመጠጣት አድማ ጠርተዋል። አሁን ቴዲ አፍሮን አብዶ በረንዳ (የጫት ማከፋፈያ በረንዳ ነው) ቢሆን ስፖንሰር ያረገው ምን ሊሉ ነበር።። ባረገው እና የተከታዮቻቸውን መልስ ባየን። አንድ ጊዜ ቆይ ጠብቁኝ ሳቄ መጣብኝ ያለው ተናጋሪ ማን ነበር።
አዲሱ የቴዲ አፍሮ አልበም (ጥቁር ሰው) የብዙዎቹን ኢትዮጵያዊያኖች ድምጽ ያስገኘለትን ያህል፤ ንጉስ ሚኒሊክ በድሎናል፤ ጡታችንን ቆርጦዋል፤ ወዘተ ወዘተርፈ ለሚሉት ደሞ፤ ከሚኒሊክ መፈጠር፤ ከታሪክ አንቅጽነቱና አኩሪ ገድሉ ጋር የጀመሩትን እጹብ ጸብ ውሃ የሚደፋበት በመሆኑ፤ ጠላት ሊያፈራበት እንደሚችል መገመት ብዙም አይዳግትም። እናም እነዚህ ሰዎች ቀደም ብዬ እንደ ጠቀስኩት፤ በደሌ ቢራን ያለመጠጣት አድማ እናድርግ እያሉ ነው። ልክ ናቸው፤ ህዝብ በጥላቻም በቢራም ሰክሮ እንዴት ይሆናል፤ ባንዱ ብቻ ይበቃልና።
በነገራችን ላይ ይህንን አድማ ለማስመታት ከሚራወጡት እና ከሚሯሯጡት ሰዎች መሃከል አንዱ ጁሃር መሀመድ መሆኑን ሰምቼ አፍሬ ጥፍሬ ውስጥ ልገባ ነበር። ባንድ ወቅት ይሄ ወጣት ፖለቲከኛ ስለ ራሱ ሲናገር “እኔ እናቴ መንዜና የኦርቶዶክስ ክርስቲያን ነች አባቴ ደሞ ኦሮሞና ሙስሊም ነው ፤ ታዲያ ከኔ በላይ ኢትዮጵያዊነትን የሚወክል ምንነት ኣለ ወይ” ብሎ ነበር። መልሱ ሊሆን ይሚችለው ጁሃርዬ በውነትም የለም፤ እንዳንተው አቶ መለስም እኮ የተላቀቀ ነገርን ማጣበቅ የሚችል (ኡሁ የሆነ) (UHU…glue) ደም ነበራቸው፤ ግን ደሙ ሳይሆን የደሙ ባህሪ ነው ወሳኙ ነገር። የተሸከምነው ደም ሳይሆን በውስጣችን ያፋፋነው ስብዕና ነው ማንነት ፤ ማንነት ስራ ነው እንጂ አንተ እንዳልከው የ-ኢ-ተጎራባች ዘር ደም ውህደት (ኬሚስትሪ ውጤት አይደለም)፤ ክርስቶስ (ኤሳው… ኣለይሁ ሰላም) በ-በረት ተወለደ ብለን እናምናለን፤ ግን እንደ ሰብኣዊ ፍጡር በ-በረት መወለዱ ሳይሆን ሰው ሆኖ ሲኖር ያደረገውን ነገር ነው የምናስበው፤ ስለ ነብዩ ሙሃመድ (ሰ.አ.ወ) ኣንድ ሙስሊም ሲያስብ ስለ ዘራቸው ሳይሆን ስለ ስራቸው ነው የሚያስበው ብዬ አስባለሁ ።
ባንድ ወቅት ይሄው ሰው፤ ፹ ከ ፻ የሚሆነው የሃገሬ እስላም ኦሮሞ ነው፤ እናም የኦሮሞ ህዝብን ኢምፓወር ማድረግ፤ እስልምናን ኢምፓወር እንደማረግ ነው አለን፤ ለመስማት አይደል የተፈጠርነው እናም ሰማነው፤ “በሜጫ” አለን ዝም ብለን ሰማነው፤ ቀጥሎም “ኢትዮጵያ አውቶ ኦፍ ኦሮሚያ” አለን እሱንም ሰማነው። በነገራችን ላይ ኢትዮጵያ ኣውት ኣፍ ኦሮሚያን ወደ ፈርንጅኛ ስቀዳው ( the child give birth of her mother) ኣይመስላችሁም ? ለመተርጎም የተገደድኩት የመጀመሪያው ራሱ እንግሊዘኛ መሆኑን ስለተጠራጠርኩ ነው። ለነገሩ ስታንፈርድና ኮሎምቢያ ዩንቨርስቲ እኮ መፈክር አያስተምሩም።
እና ዛሬ በደሌ መጣ እና ወንድሜ ጁሃር ሰማኒያ ከመቶ ካለው ሃሳብ ጋ ግንባር ለግንባር ተጋጨ ( head on collusion) እናም ሁለት የሚጋጩ ነገሮችን እንግዲህ እናስተውላልን።
፩) መቼም ፹ ከመቶው እስላም ኦሮሞ ነው ብለኽን፤ አንተም በዘር ብቻ ሳይሆን በእምነትም ጭምር ጠበኽ፤ ኣልገባኝም ታዲያ እንዴት ነው፤ እነማን ቦይ ኮት እንዲያረጉልኽ ነው ጥሪውን ያቀረብከው፤ ፳ ፐርሰንቱ እስላም ያልሆነው ኦሮሞ ? ደሞ ከ ፹ ከመቶ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ውስጥም ቢሆን አዲስ የበደሌ አድመኛ ማግኘት ይቸግራል ብዬ አስባለሁ፤ ምክኒያቱም እነሱ ላንተ ሲሉ ሳይሆኑ ለዲናቸው ሲሉ ድሮም እንዲህ አይነቱን ነገር ይነኩት ነበር ብዬ አላስብም፤ በፍጽም አያደርጉትም፤ ታዲያ የማይጠጡ ሰዎችን ነው አድማ የጠራነው፤ ወይስ ሙሉ የኢትዮጵያዊነት ማሳያ ምሳሌ እንድትሆን ያደረገችህ የመንዜዋ እናትህን ዘመዶች፤ እኔ ኣላውቅም ፈራሁ ሄኖክ ነው ያለኝ የልጅነት ጉዋደኛዬ፤ ባንድ ትልቅ የውሃ ጉድጉዋድ ውስጥ እንሹለክ ስለው። እኔ አላውቅም ፈራሁ ጁሃር።
ዛሬ ጀርመን ያላትን ቅርጽ እንድትጠብቅ ወይም እንዲኖራት ያደረገው ኦቶ ቮን ቢስ ማርክ፤ የደም ትግል ውጤት ነው። ታዲያ ጀርመኖች በቢስ ማርክ ተናደው ፒሊሲነርን (የጀርመን ታዋቂ ቢራ ነው) ቦይ ኮት እናርግ አላሉሉም። በፈረንሳይ እንዲህ የሚባል ታሪክ አለ፤ በአሜሪካም፤ ኣረ ሆመር በጥንታዊያኖቹ የግሪክ ዘመን ስለነበረው ጦርነትም ጽፎዋል፤ ስለ ስርኣቱ፤ ስለ አገማምኖን እና የወንድሙ መንግስት፤ ስለ ሄለናዊው ስርዓት፤ ከዚያም በሁዋላ እነ ዳንቴ ስለ ጻፉት ስለ ዲቫይን ኮሜዲ፤ ፍሬድሪክ ዊልሃልም ኒቺ ስለተራቀቀበት የማህበረሰብ ስነ ልቦና፤ እነ አልበርት ካሙ ስለጻፉለት የፈረንሳይ ማህበረስብ እና በየስራቶቹ ውስጥ ስለ ነበርው ፍዳ፤ እነ ልዮ ቶሎስቶይ በሰላ ብእራቸው ስለዘገቡት የሩሲያ የጭቆና ቦለቲካ፤ እነ ፓብሎ ፒካሶ ጉሬንሽያ ብለው ስለገለጹት የስፔን ከተማ ስለ ስንቱ ለዚህ ለወጣቱ ፖለቲከኛ እንንገረው እስኪ ባክህ ጁሃርዬ ገረፍ ገረፍ አርጋቸው (በቃ እንደውም ለዚህ ክረምት ለፐርሰናል ዲቨሎፕመንት…ትመለከታቸው ዘንድ እጠይቅሃለሁ (ማሳሰቢያ በኣብዛኛው በአማራ ጻሀፊ አይደልም የተጻፉት ቢሆኑም ደሞ ኣነተ ሃምሳ ፐርሰንት አማራ አይደለህ እንዴ፤ የምሬን እኮ ነው)
በታሪክ ላይ ጥላሸት መቀባት በፍጹም ለማንም አይሳካም፤ ወደድንም ጠላንም፤ ጠቅልለን የምንጎርሰውን እንጀራ የፈጠሩት አባቶቻችን ናቸው፤ ለሆዳችን ያለን ቅርበት ለታሪካችንም ይኑረን። ቴዲ እንዳለው ክፉውን በክፉ ለመመለስ ማሰብ ሌላ ክፉነት ነው። ሁለቱ ደሞች እንደ ደም ይሰሩ፤ ያስቡ ዘንድ ሰው እንሁን።