Monday, January 27, 2014

ጀግናን ማወደስ! (የተከበሩ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ስለ ተመስገን ደሳለኝ)

በአገራችን ውስጥ ታላቅ ተብለው (አተረጓጎሙ እንደ ሀገሩ እና ህብረተሰቡ ባህልና ልማድ የተለያየ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ) ለማህበራዊ አክብሮት የበቁ ደራሲያን፣ ጋዜጠኞች፣ ወንጌላውያን፣ ፈላስፎች ወዘተ መኖራቸው አከራካሪ አይመስለኝም፤ በሌሎችም አገራት እንዲሁ፡፡ በጠቅላላው በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ በአካዳሚያዊ እውቀትም ሆነ በልዩ ሙያዊ ክህሎት ተመርጠው የሚበቁ ሁሉም አይነት ታላላቆች መፈጠራቸው የሚጠበቅ ነው፡፡ ይሁንና በየአገሩ እንዲህ አይነቱን ፀጋ የሚታደሉ ሰዎች ብዙ ሊሆኑ አለመቻላቸውም እውነት ነው፤ ተፈጥሮአዊ ህግ ነውና፡፡  
ይህንን ጉዳይ ያነሳሁበት ምክንያት ስለ አንድ ወጣት ጋዜጠኛ አንዳንድ ሀሳቦችን ጠቅሼ ስለእርሱ የማውቀውን ያህል ምስክርነት ለመስጠት ነው፡፡ ይህ ወጣት ጋዜጠኛ፣ ልቡ በሀገሩ (በኢትዮጵያ) ፍቅር የነደደ ነው፡፡ ከሕዝባዊ ተጋድሎ ለሚያሰናክለው ለፍርሃት ቦታ ሰጥቶ አያውቅም (በአንድ ቃል ቅንጣት ታህል ፍርሃት ውስጡ የለም) እንዲያውም ከሌሎች ወጣቶች የሚለይበት ትልቁ ፀጋው ፍርሃት የለሽነት ተፈጥሮው ነው፤ ብሩህና ታላቅ አእምሮ የታደለ ነው፡፡ በዚያ ላይ ሰው አክባሪ ሲሆን፣ ንግግሩም ምጥን ነው፤ ስሜታዊነት አያጠቃውም፤ ወገንተኛነት አያናውጠውም፡፡ ትግሉ ሁልጊዜ ከሀሳብ ጋር ነው እንጂ ከግለሰቦች ወይም ከቡድኖች ጋር አይደለም፡፡  
 የተለይ ሃሳብ የማስተናገድ አቅም ከሌለው የኢህአዴግ መንግስት ሊደርሱበት የሚችሉት የህይወት መስዋዕትነት፣ የአካል ጉዳት፣ እስራት… አሳስቦት፣ ሃሳቦቹን ከማንፀባረቅ ወደኋላ ብሎ አያውቅም፡፡ ይህ ወጣት ኢህአዴግ ማስራብ፣ ማሰቃየት፣ መግደል… እንደሚችል እያወቀ ከአላማው ፍንክች አይልም፡፡ አንድም ቀን እንዲህ አይነት አደጋዎችን ሲሸሽም አይተነው አናውቅም፡፡ ይህ የሆነው ግን ሞኝ ስለሆነ አይደለም፤ ላነገበው ሀገራዊ ዓላማና ለሚያነሳቸው እውነታዎች ታማኝ ስለሆነ ብቻ ይመስለኛል፡፡ በተቀረ የሚያደርገውን የሚያውቅ ብልህ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡  
ሁልጊዜ ስለሚያጠና እና ስለሚተነትን አስቀድሞ ኢህአዴግ ምን ለመስራት እንዳሰበ መቶ በመቶ ባይሆንም አብዛኛውን ያውቀዋል ማለት ይቻላል፡፡ ያወቀውንም በድፍረት ለሕዝብ ያሳውቃል፡፡ ሲናገርም ህዝቡን በሚያሸብር አፃፃፍ አይደለም፡፡ ለምሳሌ አሁን ኢህአዴግ በዴሞክራሲ ላይ ያለውን ንቀት እና አምባገነናዊ አመለካከት ቀደም ብሎ በአደባባይ ተችቷል፡፡ ኢህአዴጎች ፊታቸውን ወደ ደቡብ እስያ አዙረው ‹‹ልማታዊ ፓርቲ›› የሚባለውን የፖለቲካ ፍልስፍና ከታይዋን፣ ከቻይና እና ከሲንጋፖር ገልብጠው አዲስ ራሳቸው የቀመሩት ፍልስፍና አስመስለው በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ በግድ ለመጫን ታጥቆ ተነስቷል ብሎ አስቀድሞ በተደጋጋሚ ለህዝቡ አሳውቆ ነበር፡፡ አሁን እየሆነ ያለውም ይኸው ነው፡፡ 
ይህ ወጣት ኦክስፎርድ፣ ሃርቨርድ፣ ሶርቦንን ወይም በሌሎቹ የዓለማችን ታላላቅ ዩንቨርስቲዎች ገብቶ ፖለቲካል ሳይንስ፣ ታሪክ፣ ሶስዮሎጂ፣ ሳይኮሎጂን… የመሳሰሉ ከማህበረሰብ ጋር በቀጥታ የሚገናኙ የትምህርት ዘርፎችን አልተማረም፡፡ ነገር ግን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያ ዲግሪ አግኝቷል፡፡ በሰፊው እንዳነበበ እና ከባለሙያዎች ጋር እንደተከራከረ ንግግሮቹ እና ፅሁፎቹ በግልፅ ያስታውቃሉ፡፡ አሁን በህዝባችን ዘንድ በሰፊው የሚታወቅ ስመ-ገናና እየሆነ ነው፡፡ 
ይህ ሰው ማን ነው? …የፋክት መጽሔት አማካሪ እና አምደኛ የሆነው እጅግ በጣም ተስፋ የሚጣልበት ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ነው፡፡ የዚህን ልጅ ብሔር እስከ ዛሬ ድረስ አላውቅም፡፡ እኔም ጠይቄው፣ እርሱም ነግሮኝ አያውቅም፡፡ በእርግጥ ብዙ ሰዎች ስለኦሮሞ ጉዳይ ብቻ የምቆረቆር ይመስላቸዋል፡፡ ደጋግሜ እንደ ተናገርኩት ስለኦሮሞ ጉዳይ የምናገረውና የምፅፈው፣ በደንብ የማውቀው ይህንኑ ስለሆነ፣ እንዲሁም ለባህልና ወጉ ቅርብ ስለሆንኩ ብቻ ነው፡፡ በተቀረ የእኔ መቆርቆርና ትግል ከአምላክ ዕርዳታ ጋር ከተሳካ ሁሉንም ኢትዮጵያውያን ወገኖቼን ከዚህ ግፍና የመከራ ስርዓት ነፃ እንዲወጡ የሚያልም ነው፡፡  
መቼም እንደኢትዮጰያ ባለ የአምባ-ገነን ስርዓት በነገሰባት አገር ህይወቴ የሚሉትን ነገር በሙሉ በመዘንጋት ትግሉን ህይወታቸው ያደረጉ ጥቂት ሰዎችን ለማየት ታድለናል፡፡ ዕጣ-ፈንታቸው ሞትና እስራት እንደሆነ ቀድመው ተረድተው ዕጣው እስኪደርስባቸው ድረስ ያላቸውን ሁሉ ለሚወዷት አገራቸው ሰጥተዋል፤ እየሰጡም ነው፡፡ እንግዲህ ተመስገንም ከነዚህ ጥቂቶች መካከል የሚመደብ መሆኑን ስናገር በሙሉ ልቤ ነው፡፡ እርሱንም ለማወደስ ስነሳ ፍርሃትን ሰብረው ከኋላ የሚከተሉትን የእርሱን ፍሬዎች መብዛት እያስተዋልኩ ነው፡፡ የኢህአዴግ መንግስት ህዝቡን በጠመንጃ ኃይል አስገዝቼዋለሁ ብሎ ሲፎክር እውቀትን ብቻ በተንተራሱ ትችቶቹ ብቅ ያለው ተመስገን ነበር፡፡ ይኸው ዛሬ በእርሱ ብዕር የተነቃቁ ጎበዞችን አፍርቷል፡፡ ከዚህ በላይ ድልም ያለ አይመስለኝም፡፡ ልጁ ሊወደስ ይገባዋል የምለውም ይህን ምክንያት እንደ አንድ መነሻ በማድረግ ነው፡፡ 
ተመስገን ሙያውን ከልቡ መውደዱን የምናየው ከኢትዮጵያ ውጪ አገር እንደሌለውና ለመሰደድ እንደማይዘጋጅ ደጋግሞ ሲናገር ነው፡፡ ሙያው የሚጠይቀው ይህን ነበርና አደረገው፡፡ በስርዓቱ አስከፊ ጫና ምክንያት የተሰደዱ ጓደኞች እንዳሉት አውቃለሁ፡፡ በማገኘውና በማዋራው ጊዜም ለእነርሱ እውቅና በመስጠት ሲያወድሳቸው አደምጠዋለሁ፡፡ የጀግና ባህሪያት መገለጫ ከሆኑት መካከል ይህ አንዱ ነውና እኔም እርሱን ጀግና ለማለት ወድጃለሁ፡፡  በመጨረሻም ለፋክት መፅሄት አንባቢያንም ሆነ ለመላው ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ የማስተላልፈው አንድ መልዕክት አለ፤ ይኸውም እንደ ተመስገን ደሳለኝ ያሉ ጀግኖቻችንን ማወደሱ ወደ ምንፈልገውንና ምናስበው ለወጥ ሊያደርሱን የሚችሉ እልፍ አእላፍ ጀግኖችን ማፍራት የሚያስችለን መሆኑን አፅንኦት በመስጠት ነው፡፡  
እግዚአብሔር ኢትዮጵን ይባርክ!