Monday, May 13, 2013

17 ሰዎችን የገደለው የፌደራል ፖሊስ ማንነት በውል አልታወቀም


17 ሰዎችን የገደለው የፌደራል ፖሊስ ማንነት በውል አልታወቀም

ግንቦት ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-እሁድ ግንቦት4፣ 2005 ዓም ከምሽቱ 2 ሰአት ከ45 ደቂቃ ላይ ፣ የሁለት አመት ህጻንን ጨምሮ 17 ሰዎችን  በባህርዳር ከተማ ቀበሌ 11 ወይም በተለምዶ አባይ ማዶ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ በግፍ የገደለው የፌደራል ፖሊስ አባል ማንነት እና የገደለበት ምክንያት በውል አለመታወቁን ተከትሎ የተለያዩ መላምቶች እየተሰነዘሩ ነው።
ወታደሩ ድርጊቱን የፈጸመው አንድ ያፈቀራት ወጣት ከእርሱ ጋር ለመቀጠል ፈቃደኛ ባለመሆኑ ነው የሚል አስተያየቶች ቢሰሙም በሌላ በኩል ደግሞ ግለሰቡ የሌላ ብሄር ተወላጅ በመሆኑ ጥላቸውን ለመግለጽ በሚል የፈጸመው ነው የሚሉ ወገኖች አሉ።
እሁድ ምሽት ወታደሩ ወደ አፈቀራት ልጅ ቤት ቢሄድም  እናቷን ብቻ በማግኘቱ ተኩሶ የልጂቱን እናት ተኩሶ መግደሉን ከዚያ በሁዋላ መንገድ ላይ ያገኛቸውን ሁሉ መግደል መጀመሩን አንዳንድ ነዋሪዎች ተናግረዋል።
በሌላ በኩል ግን ግለሰቡ ከፍተኛ ወታደራዊ ጥበቃ በሚደረግበት የብአዴን ጽህፈት ቤት እና የሰማእታት ሀውልት በሚገኙበት አካባቢ አካባቢ መሆኑ እና ሌሎች ፖሊሶችም አፋጣኝ እርምጃ ለመውሰድ አለመቻላቸው ፣ ከዚህም በተጨማሪ ገዳዩ ወታደር የሌላ ብሄር ተወላጅ ነው የሚለው ወሬ በስፋት መሰራጨት አብዛኞቹ  ወጣቶች ጉዳዩ ከፖለቲካ ከፖለቲካ ጋር የተያያዘ ነው በማለት አስተያየት እንደሚሰጡ የባህርዳር ዘጋቢያችን ገልጿል።
የባህር ዳር ከተማ ፖሊስ ኮሚሽን መምሪያ ሀላፊ ኮማንደር ደረጀ አቻምየለህ የገዢው ፓርቲ ልሳን ለሆነው ራዲዮ ፋና  ” ግለሰቡ በውል ባልታወቀ ምክንያት በመንገድ ላይ በከፈተው ተኩስ 12 ሰዎች መገደላቸውን በሰዓቱም ወታደሩን በቁጥጥር ስር ለማዋል ፖሊስ ክትትል ሲያደርግ እንደነበርና በመጨረሻም ራሱን በወንዝ ውስጥ በመወርወር ህይወቱን እንዳጠፋ” ተናግረ= ዋል።
የፖሊስ አዛዡ “ድርጊቱን የፈፀመው ግለሰብ የፖሊስ አባል መሆኑን ገልጸው ፥ ድርጊቱን የፈፀመበት ምክንያትም ግለሰባዊ ” ነው ብለዋል።
ኢህአዴግ ድርጊቱ ከፖለቲካ ጋር የተያያዘ አለመሆኑን ለማስረዳት በከተማው ውስጥ የሚገኙ ዋና ዋና አባሎቹን በማሰማራት ከፍተኛ ቅስቀሳ እያደረገ ነው።
ይሁን እንጅ  መንግስት የሟቾቹን ቁጥር 12 አድርጎ ማቅረቡ ህዝቡን ለባሰ ጥርጣሬ እንደከተተው ዘጋቢያችን ገልጿል። በርካታ የአይን እማኞች እንደሚሉት የሟቾች ቁጥር 17 ደርሷል። መንግስት ወታደሩ ራሱን እንዳጠፋ አድርጎ ቢገልጽም፣ ነዋሪዎች ግን ወታደሩ ራሱን ቢያጠፋ ኖሮ አስከሬኑ ይገኝ እንደነበር፣ በተለይም ደግሞ አባይ በአሁኑ ሰአት ከመቼውም ጊዜ በላይ ቀንሶ የሚታይበት ጊዜ በመሆኑ ወታደሩ ራሱን ወደ ውሀው ቢወረውር እንኳ የመትረፍ እድል ሊኖረው እንደሚችል በመግለጽ በመንግስትን በኩል የቀረበውን ዘገባ አልተቀበሉትም።
ከተገደሉት መካከልም አንድ የሁለት አመት ተኩል ህጻን እና ሴቶች ይገኙበታል። የ7ቱ የቀብር ስነስርአት ዛሬ በደብረ አባይ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የክልሉ ፕሬዚዳንት አያሌው ጎበዜ በተገኙበት ተፈጽሟል።
ከወራት በፊት ኮሶበር በምትባል ከተማ አንድ የፌደራል ፖሊስ አባል በርካታ ሰዎችን መግደሉን መዘገባችን ይታወሳል። የፌደራል ፖሊስ አባላት በየጊዜው በህዝቡ ላይ የሚፈጽሙት በደል እየጨመረ ቢመጣም በመንግስት በኩል እርምጃዎች ሲወሰዱ አይታይም።