Monday, August 5, 2013

የግፉዓን ዕድሜ ምን ያህል ይረዝማል?

(ተመስገን ደሳለኝ)
…‹‹የጣር ቀጠሮው ስንት ነው
ለሰው ልጅ ሰው ለምንለው
ላይችል ሰጥቶት ለሚያስችለው
ስንት ቀን ነው? ስንት ሌት ነው?...››
(ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን ‹‹እሳት ወይ አበባ›› የግጥም መድብል)
እነሆም ለቅስቀሳ ሳይሆን፣ አንተንም እራሴንም እወቅስ ዘንድ ብዕሬን እንዲህ አነሳሁ፡- ‹‹ሀገሬ መከታዬ፣ መኩሪያዬ…›› ከምትላት እናት
ኢትዮጵያ ምንድር ነው የምትፈልገው? …ዳቦ፣ ማህበራዊ ፍትህ፣ ፖለቲካዊ ነፃነት፣ ቤት መስራት፣ መማር-አለመማር፣ መደገፍ-መቃወም፣
መተኛት-መነሳት፣ ፈጣሪን ማምለክ-መካድ፣ መስራት-አለመስራት፣ መምረጥ-አለመምረጥ፣ አደባባይ መዋል፣ ሰፈር መዋል፣ መደራጀት-
አለመደራጀት፣ ማልቀስ-መሳቅ፣ መፃፍ፣ መናገር፣ መጮኽ-መመሰጥ፣ የግል መብት፣ የቡድን መብት?
ይህ ይሆን ዘንድ ከወዴት ትሻለህ? …ከሙት መንፈስ፣ ከውርሱ ድንዛዜ፣ ከሰማይ፣ ከምድር፣ ከፀሐይ፣ ከጨረቃ፣ ከርዕዮተ-
ዓለም ወይስ….?
ዳገቱ ላይ ትደርስ ዘንደስ የማንን መንገድ መከተል ትወዳለህ? …የሶቅራጥስን፣ የቡድ
ሀን፣ የኢየሱስን፣ የነብዩ መሀመድን፣ የካርል ማርክስን፣ የማህተመ ጋንዲን፣ የኔልሰን ማንዴላ…?
የወቃሹ ሰው ጥያቄ ይህ ነው (ከተጠያቂዎቹ አንዱ እንደሆንኩ ሳትዘነጋ) ለሺህ ዓመታት ‹‹እነሆ የነፃነት ፀሀይ ከዚህ ፈነጠቀች››
በተባልክበት ሁሉ ያለመታከት ሮጠሀል፤ ዛሬም ትሮጣለህ፤ ግና አላገኘሃትም፤ ምክንያቱም ከዓመታት ልፋት በኋላ ‹ነቢያቶችህ›
(ገዥዎችህ) የተነበዩልህ ጋ ብትደርስም ‹‹በዚህ ጠለቀች›› ይሉህና ባለህበት ያቆዩሀል (ወደ ነበርክበት ይመልሱሀል)
እነሆ ይህ ይለወጥ ዘንድም ‹‹ና እንወቃቀስ››፤ የሰውነት ‹‹ነፃነት››ህን ለዘመናት እንደ አባቶችህ ሁሉ፣ እንደ አያቶችህ ሁሉ፣ እንደ
ምንጅላቶችህ ሁሉ… ከመስኩ፣ ከጥልቁ፣ ከጋራው፣ ከሸንተረሩ፣ ከዱሩ፣ ከወንዙ፣ ከንፋሱ፣ ከአዶከበሬው፣ ከተቀባው፣ ከተረገመው፣
ከዙፋኑ፣ ከመዛግብቱ… ካልተፃፈበት መካከል ስትፈለግ ጉልበትህ ተበዝብዟል፤ ከነገስታቱ ወደ ወታደር፤ ከወታደሩ ወደ ነጋዴው
በቅብብሎሽ አልፈሀል፤ በማይታይ፣ በማይጨበጥ፣ በማይዳሰስ… ‹‹ራዕይ››፣ ‹‹መጪው ጊዜ ብሩህ ነው›› ተብለህ ተታለሀል፤ ‹‹በእኛ
ልማታዊነት በቀን ሶስቴ መብላት ችለሀል፤ አርባና ሃምሳ ዓመት ከታገስከን ደግሞ መኖሪያ ቤትህ በተትረፈረፈ ሃብት ይሞላል›› ብለውህ
ሲያበቁ ‹‹አሜን›› እንድትል ተገደሃል፤ እውነት እውነት እልሀለውም፡- ይህንን ነው ‹‹ሰላማዊ ትግል›› ብለህ የያዝከው፡፡
የግፉዓን ዕድሜ ስንት ነው?
የጣር ቀጠሮ ስንት ነው?
ለሰው ልጅ ሰው ለምንለው…
እነርሱም ቀጥለዋል፤ አንተም ቀጥለሀል፤ …እስክስታ መምታትም ሆነ ጦር ይዘህ፣ በፀጉርህ ላይ ላባ ሰክተህ እንደ ምርኩዝ ዘላይ
በአደባባይ ወደ ላይ፣ ወደ ታች ማለትህን ‹‹የባህል ነፃነት፣ የብሔር ብሔረሰብ መብት›› ብለውህ ሲያበቁ፣ ‹‹አንተ ማለት እኛ፤ ሀገር ማለት
እኛ፤ ህግ ማለት እኛ፤ እኛን አምነህ ካልተቀበልክ ሶማሊያን መሆንህ አይቀሬ ነው›› ሲሉ ያስፈራሩሀል፤ ግና! ማን ነው ተራራን ገትሮ፣
ሸለቆን ፈልፍሎ፣ ወሰን አበጅቶ ቅፅር አንፆ፣ ‹‹ሀገር›› ብሎ ሰይሞ ‹‹ብዙ ተባዙ›› ያለው? ብለህ ብትጠይቅ መልሱን እዛው ውስጥ
ተቀብሮ ታገኘዋለህ፤ ሰው ስለሆንክ ብቻ ተፈጥሮ የለገሰችህን ሰዋዊ ነፃነት፡፡ እናም ማወቅህም፣ መሻትህም የሚነሳው ከዚህ ብቻ ነው፤
በተቀረ ‹‹ጎፈር››ን በ‹‹ዘውድ›› ቀይረው ‹‹ተቀባንልህ››፣ ‹‹ፈነቀልንልህ››፣ ‹‹ታገልንልህ››፣ ‹‹መረጥከን››… የሚሉህን አሳይ መሲዎች
አምነህ መብቶቼን ይሰጡኛል፣ ሰማያዊ ነፃነቴን ያከብሩልኛል ብለህ መጠበቁ ይብቃህ! እነርሱ ሀገሪቷ የታቀፈችውን በረከት ያለ አድልኦ
ለማካፈል፣ ተፈጥሮ የለገሰችህን ነፃነት ከ‹‹ሰው ሰራሽ›› አደጋ ለመከላከል፣ አንተን ወክለው ከድንበር ባሻገር ካሉ ህዝቦች እና አቻዎቻቸው
ጋር ለመነጋገር፣ ለመመካከር፣ ለመተባበር፣ ለመሸጥ-ለመለወጥ… ገደብ ባለው አለቅነት የተሰየሙ ናቸው! ይኸው ነው፤ ስልጣነ-መንበሩም
የሚፀናው የስምምነት ማዕቀፉ ይህ ሲሆን ብቻ ነው፡፡
‹‹ካልሆነስ?›› ብለህ አትጠይቅ፤ ምክንያቱም ያልበጀን ሽሮ፣ የሚበጅን የመሾም መብት የአንተ (የህዝብ) ነውና፤ ሀገርህም ‹‹ሀገር››
የምትሆነው ይህ ሲሆን እንጂ ‹‹አፅም፣ ታሪክ፣ ባህል፣ ሀውልት…›› ጂኒ ቁልቋል ስላወረሰችህ አይደለም፤ በአለቃና ምንዝር አንድምታም
አይደለም፤ ‹‹ዕድገቱ››ን ጨለማ በዋጣት ‹‹ጥቁሯ ድመት››፣ ‹‹ህጉ››ን በስርዓቱ ‹‹እንባ ጠባቂነት›› መስለው ማደናገራቸው፡-
‹‹ሀገሩ ታሰረእስር ቤት መቀለስ፣ እንደ ድሮ ቀረ›› (ግርማ ተስፋው ‹‹የጠፋችውን ከተማ ኀሠሣ›› የግጥም መድበል) የሚለውን ውብ ስንኝ
ያስታውስሀል፡፡
እዚህ ድረስ የተወቃቀስነው ስላለፈው ዘመን ነውና አንድ ጥያቄ ጠይቄህ ወደ መጪው፣ ወደ መፍትሄው ጥቆማ እንለፍ፡- የግፉዓን ዕድሜ
ምን ያህል ይረዝማል? …አርባ ሶስት፣ አስራ ሰባት፣ ሃያ ሁለት …ስንት ምርጊት? …ትከሻህ እስከቻለ፣ ጉልበትህ እስካልዛለ፣ ረሀብና እርዛት
እስካላስቆጣህ ድረስ… እንደ ሰማይ ከዋክብት ተቆጥሮ የማያልቅ ፍስሃ እስካልሰጠህ ድረስ የመከራው ዘመን የበዛ ይመስለኛል፡፡ ማን ነበር
‹‹እራሱ የመጣ፣ በራሱ አይመለስም›› ያለው?
ይህንን ነው እያልኩ ያለሁት፤ ጨቋኞችን በመልካሞች፤ ጨካኞችን በሩህሩዎች፤ አምባገነኖችን በዲሞክራቶች መቀየሩ የአንተ እንጂ ስንዴ
የሚልኩልህ ሀገራት አይደለም፤ እናም መሞትን እንጂ መግደልን በማይጨምረው ‹‹ህዝባዊ እምቢተኝነት›› ለለውጥ መቆጣት፣ ለለውጥ
መዘመርን… ‹‹ለነገ›› አትበል፤ ነገ የራሱን የታሪክ ምዕራፍ ይገልፃል፤ ይህ ይሆን ዘንድም ‹‹አትነሳም ወይ?›› የሚል ቀስቃሽ አትጠብቅ፤
ለጩኸትም፣ ለተመስጦም ‹‹እኔን አስፈቅድ!›› የሚሉህንም አትሰማ፡፡ ሀገር ለዜጎች የወል ዕርስት ናት-ሁሉን ፈቅዳ የለገሰች፡፡ ታዲያ
ስለምን ‹‹ፍቀዱልኝና ለተቃውሞ ሠልፍ አደባባይ ልውጣ›› ብለህ ትጠይቃለህ?
እስቲ! ፊትህን ወደ ቱኒዚያ መልስ፣ መልካሙ ሁሉ የሆነው በገዥዎቻቸው ፍቃድ አይደለም፤ ጥያቄያቸውም ሆነ ጥያቄውን ያቀረቡበት
መንገድ የሀገሪቱ ዜጋ በመሆን ብቻ የሚገኝ መብት ነው፡፡ ምናልባት ቱኒዚያ ከራቀህም ከሁለት ሺህ አራት አጋማሽ ጀምሮ ከኢትዮጵያ
መስጊዶች እየወጣ ያለውን ድምፅ ልብ ብለህ ተከታተለው ‹‹መጅሊስ ይውረድ››፣ ‹‹በሃይማኖታችን ጣልቃ አይገባ››፣ ‹‹አህባሽ
አይወክለንም››… ሲል ትሰማዋለህ፤ እውነትም እውቀትም ይህ ነው፡፡
የእስልምና እምነት ተከታዮች በሰውነታቸው የተጎናፀፉትን የሃይማኖት ነፃነት እየጠየቁ ያለበት መንገድ ኢትዮጵያውያን በሰላማዊ ትግል
ላይ ያለንን ግንዛቤ አጥርቶ የሚያሳይ ነው፡፡ ትግሉ ከተጀመረበት ዕለትም አንስቶ በአምባገነን ስርዓት ውስጥ ያለ ተመሳሳይ እንቅስቃሴ
የሚገጥመውን አይነት ተግዳሮት ህግን በማክበርና በማስተዋል የተሻገረ ከመሆኑም በላይ በርካታ የጠልፎ መጣያ ‹‹ድራማ››ዎችን ጭብጥ
ደካማነት አጋልጧል፡፡
ለዚህ ውጤት መሰረታዊው አበርክቶ ህዝበ ሙስሊሙ ያነሳው ጥያቄ፣ ከእምነቱ ውጪ ያለውን ኢትዮጵያዊ መብት የማይጨፈልቅ
በመሆኑ ይመስለኛል፡፡ የእንቅስቃሴው አስተባባሪዎችም ለእስር ከመዳረጋቸው ሁለት ወር አስቀድሞ ‹‹እውነቱ ይህ ነው›› በሚል ርዕስ
ባሳተሙት መፅሀፍ ወደ ትግል የገቡበትን ምክንያት ብናይ ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው፡፡
‹‹…ታህሳሳ 21 2004 ከመጀሊስ አመራሮች በተለይም የሰላምና ፀጥታ ዘርፍ ሀላፊ በሆኑት በአቶ ጀማል መሐመድ ሳላህ የተፈረመውና
ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ሀምሳ (50) ምሁርንን፣ የጥበቃ ሰራተኞችን፣ የመስጂድ ኢማም እና ሙአዚን፣ የዓረብኛ ተማሪዎችን እና
መምህራን መባረራቸውን የሚያረዳው ደብዳቤ ደረሰ፡፡ ተመራቂ ተማሪዎች ትምህርታቸውን አጠናቀው እንዲመረቁ ቢጠየቁም
‹ለመመረቅ የቀራችሁ አንድ ቀን እንኳ ቢሆን አንፈቅድላችሁም› በማለት የመጅሊስ አመራሮች የተማሪዎችን ልብ የሰበረ ምላሽ ሰጡ፡፡
መጅሊስ አወሊያን የአህባሽ ፍልስፍና ማጥመቂያ ማዕከል ለማድረግ በመወሰን የአሰሪ እና ሰራተኛን ህግ የጣሰ ውሳኔ በአምባገነንነት
መውሰዱን ተከትሎ በተማሪዎች ተቃውሞ ተቀሰቀሰ፡፡ ተማሪዎችም ‹ያለአግባብ የተባረሩ መምህራን፣ የመስኪዱ ኢማም፣ ሙዓዚን እና
ሰራተኞች ይመለሱ የዓረብኛ ኮሌጅ ዳግም ይከፈት፣ የአህባሽን አስተምህሮ አስገድዶ መጫኑም ይቁምልን› ሲሉ ጠየቁ፡፡ ከመጅሊስ
ተወካዮች ጋር እንዲሁም ከክፍለ-ከተማው የመንግስት አካላት ጋር የተለያዩ ውይይቶች የተካሄዱ ቢሆንም ምላሹ ግን የመብት ረገጣ እና
ንቀት ሆነ፡፡ ለአመታት የሙስሊሙን ልብ ሲያቆስል የነበረው መጅሊስ ሙስሊሙ ሊታገሰው ወደ ማይችለው አምባገነንነት ደረጃ
መድረሱን አሳየ፡፡
‹‹የተማሪዎቹም ቁጣ ገንፍሎ ጥያቄው ወደ ተቃውሞ ተቀየረ፡፡ ጥያቄው ከችግሩ ወደ የችግሩ መንስኤ ተሸጋገረና መፈክሩም ‹የመጅሊስ
አመራሮች አይወክሉንም! አህባሽ አይጫንብንም!› ሆነ፡፡ ተቃውሟቸውንም ህዝቡን በአወሊያ በመጥራት ‹ቀጣዩን ሂደት ተረከቡን›
የሚል ጥሪ የሚያስተጋባ ተጨባጭ ውስጥ አስገቡት፡፡››
ዛሬም ድረስ ይህንን ጥያቄ (ከተራ ፕሮፓጋንዳና የፈጠራ ክስ በቀር) በአመክንዮ ፉርሽ ሲያደርግ የተመለከትነው አካል ስላላየን
የሃይማኖት ነፃነታቸው መጣሱን አምኖ ከጎናቸው ከመሰለፍ በቀር አማራጭ የለም፡፡ በርግጥ ትግሉ እንዲህ ከሁከትና አመፅ ዕርቆ
በሠላማዊ መንገድ ቢካሄድም በሁለት ምክንያት ውጤታማ መሆን አለመቻሉ ግልፅ ነው፡፡ የመጀመሪያው የእምነቱ ልሂቃኖች እና
አስተባባሪዎች ጥያቄው የሃይማኖት ነፃነትን የሚመለከት ብቻ መሆኑን፣ እንዲሁም ስርዓቱ ‹‹እስላማዊ መንግስት በኃይል ለመመስረት
የሚደረግ ህገ-ወጥ ተግባር ነው›› ሲል የሚያቀርበውን ውንጀላ ለሁሉም በሚገባ መልኩ ማስተባበል አለመቻላቸው ሲሆን፣ ሌላኛው ሀገር
ውስጥ ያሉ ሚዲያዎች በቂ ሽፋን በመስጠት በእንቅስቃሴው ላይ የሚነሱ አሉባልታዎችን አጥርተው የሀይማኖቱ ተከታይ ያልሆኑ
ኢትዮጵያውያኖችም ከሙስሊሙ ጎን እንዲሰለፉ ለማድረግ ያሳዩት ዳተኝነት ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ይሁንና በዚህ በኩል አንድነት እና ሰማያዊ ፓርቲ ዓላማው ‹‹በአደባባይ ጮኾ መመለስ›› ቢሆንም ጥያቄውን ይዘው ሰልፍ
መውጣታቸው የሚያስመሰግን ተግባር ነው፡፡ የእነሽመልስ ከማልን የከሸፈ ፍርጃ ‹‹ቁም-ነገር›› ብለን አናነሳውም፤ ምክንያቱም የመጅሊስ
ምርጫ በቀበሌ ሲካሄድ የሃይማኖት ነፃነት መከበር፤ ሰማያዊ እና አንድነት ፓርቲ የሙስሊሙ ጥያቄ ይመለስ ሲሉ ‹‹በሀይማኖት ጣልቃ
መግባት›› ተብሎ እንዲወሰድ የሚያደርግ ምንም አይነት የህግ-መሰረት ልክ ሊሆን አይችልምና፣ እንዲህ አይነት ህግ ቢኖር እንኳ ‹‹If the
‘law’ is in such a manner that, it makes you the agent of injustice, I said, break the law›› (ሕጉ የኢ-ፍትሀዊነት
ባሪያ የሚያደርግህ ከሆነ ሕጉን አታክብር /ጣሰው/) እንዲል ታዋቂው የህዝባዊ እምቢተኝነት መምህር ሔነሪ ዴቪድ ቶሮ፣ ራሱ ህጉን
መገዳደሩ ፍትሃዊ አካሄድ ነው፡፡
ከዚህም አኳያ ነው በሀገሪቱ ሕግ መሰረት በሰላማዊ መንገድ ለመታገል የተመዘገቡ የፖለቲካ ድርጅቶች በአደባባይ እስረኛ ‹‹ይለቀቅ››
ለማለት ቀርቶ፣ የስርዓት ለውጥ ለማምጣትም ፍቃድ መጠየቅ አለባቸው ብዬ የማላምነው፡፡ ሰላማዊ የትግል ስልትን በተለያዩ ሀገራት
‹‹ተጨቆንን›› ያሉ ህዝቦች አማራጭ አድርገው ታግለውበት ድል መንሳታቸውን ከአለም የታሪክ ንባብ መረዳት ትችላለህ፡፡ የትግሉ
ፍልስፍና ከበርካታ ክፍለ ዘመናት በፊት የሚታወቅ ቢሆንም፣ በተደራጀ መልክ ወደ መሬት የወረደው በሃያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ
አካባቢ ነበር፡፡ በተለይም ህንድን ከእንግሊዝ የቅኝ አስተዳደር ነፃ ለማውጣት ከሁለት ዓስርተ ዓመታት በላይ በዚሁ መንገድ ተጉዞ
ውጤታማ የሆነው ማሀተመ ጋንዲ ተጠቃሽ ነው፤ በደቡብ አፍሪካ ኔልሰን ማንዴላ፤ በአሜሪካ (የጥቁሮች መብትን ለማስከበር) ማርቲን
ሉተር ኪንግ ፤ በበርማ አን ሳንሱኪ እና በተለያዩ ሀገራት ከፖለቲካ እና ማህበራዊ ፍትህ ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችን ያነገቡ ዜጎች
መፍትሄዎችን በሰላማዊ ትግል ፈልገው አግኝተዋል፡፡ በኢትዮጵያ የአፄ ኃይለስላሴን አስተዳደር ለመቀየር የተደረገው ህዝባዊ ትግልም
በዚሁ ማዕቀፍ ውስጥ የሚወድቅ መሆኑን አትዘንጋ፡፡ ነገር ግን በሰላማዊ ትግል ታሪክ ውስጥ አገዛዙን አስፈቅዶ የረሃብ አድማ ያደረገ
ወይም የትራፊክ መንገድን የዘጋ ስለመኖሩ ሲነገር አልሰማሁም፤ ተፅፎም አላነበብኩም (ሰላማዊ ትግልን በተመለከተ በሌላ ጊዜ በስፋት
እመለስበታለሁ)
የሆነ ሆኖ የህሊና እስረኞች እንዲለቀቁ መጠየቁ ተገቢ ቢሆንም እንዲህ አይነቱ አጀንዳ ለስርዓቱ ሴራ ሰለባ የሚያደርግ መሆኑንም
ግምት ውስጥ መክተት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም የኢህአዴግን ባህሪ ከተከታተልከው አስቦና አቅዶ የተቀናቃኞቹን እንቅስቃሴ
የሚገድበው መሪዎቻቸውን፣ አባሎቻቸውን እና ጋዜጠኞችን አስሮ፣ እንዲፈቱላቸው በሚጠይቅ ትግል እንዲጠመዱ በማድረግ ነው፤
ያለፉትን ሃያ ዓመታት ብናይ (ከ1985 ዓ.ም ጀምሮ) በሀገር ውስጥም ሆነ በአውሮፓና አሜሪካ ከተሞች በኢትዮጵያውያን ከተደረጉ
ሰላማዊ ሰልፎች አብዛኛው እስረኛ እንዲለቀቅ የሚጠይቁ መሆናቸውን ያረዳሃል (እነፕ/ር አስራት ወ/ደየስ፣ ዶ/ር ታዬ ወ/ሰማያት፣ አበራ
የማነ፣ ስዬ አብርሃ፣ እነኢንጂነር ኃይሉ ሻወል፣ ብርቱካን ሚደቅሳ፣ አንዱአለም አራጌ፣ እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት አለሙ፣ ውብሸት ታዬ፣ እነ
አቡበክር መሀመድን… በተመለከተ የተደረጉትን ሰልፍ ማስታወሱ በቂ ነው)
እናም የስርዓቱን የ‹‹ቤት ስራ›› ወደ ጎን ገፍቶ ለሁሉም ችግር መፍትሄው ሰላማዊ በሆነ መንገድ (ከብጥብጥ፣ ከጥላቻ፣ ከአመፅና
ከመሳሰሉት ዕርቆ) አገዛዙ ስልጣኑን ለህዝብ አስረክቦ የሕግ የበላይነትን የሚያከብር ዲሞክራሲያዊ መንግስት በአዲስ ምርጫ እንዲመሰረት
ማድረግ ብቸኛው አማራጭ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ‹‹ህዝባዊ እምቢተኝነት›› ማለትም ይህ ነው፤ በአናቱም በሰላማዊ መንገድ የሚካሄድ
ትግል ህገ-ወጥ፤ ጉልበተኛ መንግስት ደግሞ ህጋዊ ሆኖ መጪዎቹን ሀያ አመታትም እነአንዱአለምን፣ እነእስክንድርን፣ እነአቡበክርን…
በሌሎች በባለተራ ነፃነት ናፋቂ እየቀየረልህ ዕድሜውን ሲያራዝም መመልከትን ከመረጥክ ከአለቃ ዘነብ ‹‹መፅሀፈ ጨዋታ-ስጋዊ
ወመንፈሳዊ›› ይህችን ብታነባት ፍርሃት ምክንያት አልቦ እንደሆነ ትነግርሀለች ‹‹…ሸክላ ከተሰበረ በኋላ ገል ነው፤ መኳንንትም ከተሻሩ
በኋላ ህዝብ ናቸው››፡፡
የትም ሁን የት፤ መቼም ይሁን መቼ ኢ-ፍትሀዊ ድርጊት በአንተ ላይ እስኪፈፀም አትጠብቅ፤ ‹‹በሌላ ቦታ ያለ ኢ-ፍትሃዊነት፣ በየትም ላለ
ፍትሃዊነት ጠንቅ ነው›› እንዲል ማርቲን ሉተር ኪንግ ‹‹መጅሊስ ይውረድ›› ውስጥ አንተም አለህ፤ የ‹‹ቡድሀ››ም ሁን የ‹‹ኢየሱስ››
ተከታይ ከ‹‹ፀረ-ጭቆና›› ድምፅ ጋር ያስተሳሰረህ ሲባጎ ከቶውንም ቢሆን ሊበጠስ አይችልም፤ በሌሎች የሆነው፤ በአንተም ስለመሆኑ
ቅንጣት ጥርጣሬ አይገባህ፤ ‹‹እኔ ምን አገባኝ›› ነገ ባለተራ ያደርግሃል፤ እንዲህ አይነቱን ኢ-ፍትሀዊነትን ለመገዳደርም ቋንቋ፣ ብሔር፣
ሃይማኖት… ሊገድብህ አይገባም፡፡ የአለምን ታሪክ መርመር፤ ቼ ጉቬራን ከሀገር አገር ያንከራተተው የ‹‹ሲራራ ንግድ›› አይደለም፣ ‹‹ሰው
ሰራሽ›› ጭቆና እና የደካሞች ሸክም ይቀል ዘንድ ነው፡፡ የማህተመ ጋንዲ ‹‹ሳትያግራሃ››ስ ምን አተረፈ? ብለህ ጠይቅ፣ ‹‹የሚሊዮኖችን
ነፃነት›› የሚል ምላሽ ታገኛለህ፤ የዙሉዎችን የትግል ጉዞ ፈትሽ፣ የኔልሰን ማንዴላ ረጅም እስር የማታ ማታ አስከፊውን ቀንበር እንዴት
እንደሰበረው ይነግርሃል፡፡
ይህ ሁሉ የሆነው ጨቋኞች በረጅም ገመድ አስረው በሚሰጡት ፍቃድ ሳይሆን፣ በሰላማዊ ታጋዮች ‹‹እምቢ!›› ባይነት ነው፡፡ የአፍሪካ
ቀንድን፣ አሊያም የአፍሪካ አናትን ብትመለከት ተፈጥሮ የፃፈችው የ‹‹ነፃነት መንፈስ›› የሰው ልጅ በፃፈው ‹‹ህግ ተገስሶ ታያለህ፤ ኢ-
ፍትሃዊ አስተዳደር ሰልጥኖ ታገኛለህ፤ ስግብግብነት፣ ጥላቻ፣ ሀፍረት፣ አድርባይነት፣ አታላይነት፣ ክፋት… ዘመኑን ሲመራ ትታዘባለህ፤
የጉልበተኞች መንፈስ ገንግኖ ትመለከታለህ፤ ለዚህም ነው የግፉዓንን የመከራ ፍፃሜ ለማወጅ የማንም ፍቃድ አያስፈልግህም የምልህ፤
ፍቃድህ የሚነሳው ከእውነት እና ፍትህ መሻት ብቻ ነው፤ ከዚህ ባለፈ በየወሩ በጭብጨባ የሚፀድቅ ህግ የለውጥ ጉዞህን እንዲያስተጓጉልመተባበር ግዴታህ አይደለም፤ የከሳሾችህ ፍርደ ገምድልነት፣ የጭካኔ በትር… ከሰላማዊነትህ በላይ ሊያሳስብህ አይገባም፤ ሰንደቅህ ጥላቻን
ያሸነፈ ፍቅር እስከሆነ ድረስ የወህኒውን አጥርም ሆነ እርሳስ የሞላውን ዝናር መፍራት የህሊና ዕዳ ብቻ ሳይሆን ከእውነት መቃረንም ነው፤
ለውጡን በሞትህ እንጂ በመግደል እስካልተመኘህ ድረስ በፈራ-ተባ ማመንታት በማትቀይረው ታሪክ ላይ እንደ ማመፅ ይቆጠራል፡፡
እናም እልሀለሁ፡- ከድንዛዜህ ንቃ፤ ስለፍትህ እንጂ ስለህግ አትጨነቅ፤ የአምባገነኖች ‹‹ህግ›› ሁሉ፣ ‹‹ፍትሐዊ›› አይደለምና የምልህ፡፡
ይህንን እውነት በስነ-አመክንዮ ለመረዳት በሚከተለው ምሳሌ ላስረዳህ፡- ሰው መግደል ወይም የአንተ ያልሆነን ንብረት መስረቅ ‹‹ወንጀል
ነው›› የሚል ህግ-ፍትህ መሆኑ አያከራክርም፤ በተቃራኒው መንግስትን በአደባባይ መቃወም ወይም ‹‹መልካም አስተዳደሪ አይደለህምና-
በቃህ›› ማለት ‹‹አመፅና ሁከት ነው›› የሚል ህግ በፍፁም ፍትሐዊ አይሆንም፡፡ በየትኛውም ሀገር ያለ ጉልበተኛ አገዛዝ ለስልጣን
ማራዘሚያ የሚጠቅመውን ‹‹ህግ›› ማውጣቱ የተለመደ ነው፤ ሆኖም ስርዓቱ ሲቀየር ‹‹ህጉ››ም ፍትሐዊ ስላልሆነ አብሮ መቀየሩ በታሪክ
የታየ ነው፡፡
በጥቅሉ መዘንጋት የሌለበት ቁም ነገር (የዚህ ፅሁፍም አንጓ) የፖለቲካ እና ማህበራዊ ለውጥ በተዓማኒ እና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ
መገኘቱ አንድ እውነት ቢሆንም፣ ተዓማኒ እና ዴሞክራሲያዊ ባልሆነ መንገድ ስልጣን የሙጥኝ ያለን መንግስት በኢያሪኮ ጩኸት ማፍረሱ
ሌላ እውነት መሆኑን ማስታወስ ነው፡፡ እናም ይህ ይሆን ዘንድ የጦር መሳሪያም ሆነ ስለት ሳትይዝ ባዶ እጅህን ውጣና አደባባዩን ሙላው፤
መንገዱን በሙሉ ዘግተህ የመኪና እንቅስቃሴዎችን አስተጓጉል፤ ነፃነትህ የታሰረበት ሰንሰለት በትግል እንጂ በምትሃት መቼም ቢሆን
አይሰበርምና ከአገዛዙ ጋር አትተባበር፡፡ ከ‹‹ደጀ-ሰላማቸው›› አትካፈል፤ ከ‹‹ሰንበቴያቸው›› አትጠጣ፡፡ ግፍ የሞላውን ፅዋ ወደ አፍህ
አታድርሰው፡፡ ከእነርሱ ማዕድ የነፃነት ‹‹ፍርፋሪ›› የለምና አትጓጓ፡፡ ነፃነትህም የተፈጥሮ ለመሆኑ ተንታኝ እስኪነግርህ አትጠብቅ፡፡ መርህ
ፍቅር እንጂ ጥላቻ አይሁን፤ ፍቅር ከጥላቻ ጋር ህብረት የለውም፤ ባለሰይፍን በሰይፍ መቀየሩም፣ ጉልቻ ቢለዋወጥ… ነውና መንገድህ ሁሉ
ፍፁም ሰላማዊ ይሁን!
እውነት እውነት እልሀለሁ፡- ነፃነትን የሰወረ መቃብር የሚፈነቀለው በፍቅር ብቻ ነው፤ ዘላቂ ለውጥም ከምህረት እንጂ ከበቀል
አይሰርፅም፤ አይን ላጠፋ-አይን፣ ጥርስ ለሰበር-ጥርስ የአንተ ትውልድ መርህ አይደለምና አትከተለው፤ ይህ ሲሆን ብቻ ነው፡-
የግፉዓን ዕድሜ ምን ያህል ይረዝማል?
የጣር ቀጠሮው ስንት ነው?
ለሰው ለጅ ሰው ለምንለው… እንጉርጉሮህ መልስ የሚኖረው፡፡ አሊያም ትንቢተ-ማርቲንን ተስፋ ታደርጋለህ፡-
“Those who make peaceful change impossible, make violent change inevitable”
(በሰላማዊ ለውጥ ላይ በር የዘጉ፣ አመፃን በራሳቸው ላይ ይጠራሉ)፡፡
(ማስታወሻ፡- ባለፈው ሳምንት በታተመችው ‹‹ፋክት›› መፅሄት ‹‹ከሙስናው ክስ ጀርባ›› በሚለው ፅሁፍ ላይ አቶ ስዬ አብርሃ ከርቸሌ
ድረስ በመሄድ የቀድሞ መንግስት ባለስልጣናትን ‹‹ለእናንተ ማንም ጥይት አያባክንም፤ በስኳርና ደም ግፊት እዚሁ ታልቃላችሁ!›› ብሎ
ነበር የሚለው ሀረግ ከአንድ የቀድሞ መንግስት ባለስልጣን ታሳሪ የተነገረኝ ቢሆንም፣ አቶ ስዬ አብርሃ ፅሁፉን ካነበበ በኋላ እንዲህ አይነት
ቃል በጭራሽ እንዳልወጣው ገልጾ በኢ-ሜል አድረሻዬ የፃፈልኝን ተቀብዬ ይህንን ማረሚያ መፃፌን በትህትና እገልፃለሁ፡፡) 

የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት ዘመቻ እና የመቀሌያችን መታፈን ከነመፍትሄው!

August 5, 2013

ግርማ ሞገስ (girmamoges1@gmail.com)
ሰኞ ሐምሌ 29 ቀን 2005 ዓ.ም.
የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት ዘመቻ ወደፊት በመገስገስ ላይ ይገኛል። አንድነቶች የኢትዮጵያን ጸረ-ሽብር ህግ ለማሰረዝ የዜጎች ፊርማ በማሰባሰብ ዘመቻ ላይ ናቸው። የቀድሞውን የግብጽ ፕሬዘዳንት ሞርሲን ከስልጣን የማውረድ እንቅስቃሴ ያስጀመረው ከአስራ አምስት ሚሊዮን በላይ የሚገመተው የግብጾች ፊርማ ከተለያዩ ከተሞች የተሰበሰበው በሶስት ወሮች ነበር። በግብጾች አይን ሲታይ አንድነቶች በሶስት ወሮች አንድ ሚሊዮን ፊርማ ማሰባሰብ አይችሉም ብለን መገመት ያዳግተናል። እርግጥ ኢትዮጵያውያን በሰላማዊ ትግል ባህል እና ክህሎት እንደ ግብጾች ብዙ አልዘለቅንም። ይሁን እንጂ ካሰብነው ቁጥር እንደምንደርስ ጥርጥር የለኝም። የአንድነት መሪዎች መታሰር ቢደርስባቸውም የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት የመጀመሪያው ዘመቻ በጎንደር እና በደሴ ከተሞች ሐምሌ 7 ቀን በስኬት ተፈጽሟል። በጎንደር እና በደሴ ከተሞች የዜጎች ፊርማዎች ተሰብስበዋል።Millions of voices for freedom - UDJ
ባለፈው ሳምንት ደግሞ አንድነቶች የየከተሞች አስተዳዳሪዎች እና የጸጥታ ኃይሎች የሚፈጽሙባቸውን የወከባ፣ የመኪና ጎማ በማስተንፈስ መጓጓዣ የማሳጣት፣ የቢሮክራሲ ጫና፣ የአካል ድብደባ እና እስር የተለመደ ጽዋቸውን በቻይነት እና በሆደ ሰፊነት በመቀበል እሁድ ሐምሌ 28 ቀን ከመቀሌ በስተቀር በወላይታ፣ በጂንካ፣ በአርባምንጭ እና በባህርዳር ሁለተኛውን ዘመቻ በስኬት አጠናቀዋል። ይኽን በውጣ ውረድ የተሞላ ዘመቻ አንድነቶች ሳይታክቱ፣ በትዕግስት፣ በፅናት፣ በአርቆ አስተዋይነት እና በድስፕሊን በታነጸ አኪያሄድ ፈጽመዋል። አንድነቶች “አንድነት ፓርቲ ሳይገድል እየሞተ ህገ-መንግስቱን የማስከበር ትግሉን አጠንክሮ ዛሬም ወደፊትም ይቀጥላል፡፡” የሚሉትን መርሃቸውን ምንም ሳይሸራረፍ በተግባር እየፈጸሙት ነው። ከህዝባቸው ጋር ታግለው ህዝባቸውን የመብቱ ባለቤት ለማድረግ ያላቸውን ቁርጠኛነት እያሳያዩን ነው። ሊመሰገኑ ይገባል። በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ እንደሚባለው በአንድ ወገን ፀር-ሽብር ህጉን ለማሰረዝ ሰላማዊ ትግል ዘመቻ ስታደርጉ በሌላ በኩል ደግሞ ከቀድሞው የመገዳደል የፖለቲካ ትግል ባህላችን ወደ ሰላማዊ ፖለቲካ ትግል ባህል ልታሸጋግሩን ታሪክ እየሰራችሁ ነው። ይኽን ሁሉ የምታደርጉት በአስጨናቂ እና በተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ውስጥ እንደሆነ ህዝባችሁ ይረዳዋል። የኢትዮጵያ ጉዳይ የሚያሳስበው በአገር ውስጥ እና ካገር ውጭ የሚኖረው ህዝባችሁ ስራችሁን በአክብሮት፣ በአድናቆት እና በኩራት እያስተዋለ ነው። በስራችሁ እና በስኬታችሁ ልትደሰቱ ይገባል። ታሪክ እየሰራችሁ ነው።
በጅንካ፣ በባህርዳር፣ በአርባምንጭ የምትኖሩ ዜጎቻችም ሐምሌ 28 ቀን ባደባባይ ወጥታችሁ፥ “የታሰሩ የፖለቲካ እና የነፃ ጋዜጣ እስረኞች ይፈቱ! መንግስት ህገ-መንግስቱን ያክብር! መንግስት በኃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን ያቁም! ውሸት ሰልችቶናል! ይቁም!!! የጸረ – ሽብር ህጉ ባስቸኳይ ይሰረዝ! ዘርን መሰረት ያደረገ ማፈናቀል ባስቸኳይ ይቁም!! የዜጎች ሰብአዊ መብቶች ይከበር!! መብት መጠየቅን ከጸጥታ እና ከልማት ጋር ማያያዝ በአስቸኳይ ይቁም! የፓርቲ አባልነት በፍላጎት መሆን አለበት!!” በማለት የሰብዓዊ መብት ይከበር መልዕክቶች አሰምታችኋል። እነዚህ መልዕክቶቻችሁ እና ጥያቄዎቻችሁ የጅንካ ወይንም የአርባምንጭ ወይንም የባህርዳር ብቻ አይደሉም። የኢትዮጵያ ህዝብ ጥያቄዎች ናቸው። የአለም ህዝብ ጥያቄዎች ናቸው። የተባበሩት መንግስታትም እንዲከበሩ የሚታገልላቸው መሰረታዊ መብቶች ናቸው። በትናትናው ዕለት በወላይታ የሚኖሩ ዜጎቻችንም ስለአገራቸው አሳሳቢ ጉዳዮች በአደባባይ ተሰባስበው ተወያይተዋል። ሰላማዊ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። ስለዚህ በጅንካ፣ በአርባምንጭ፣ በባህርዳር እና በወላይታ የምትኖሩ ወንድሞች እና እህቶች በሙሉ ሐምሌ 28 ቀን ባደረጋችሁት የጥሩ ዜጎች ስራ ልትደሰቱ እና ልትኮሩ ይገባል።
በዚሁ ባለፈው ሳምንት ህውሃት በመቀሌ ድምጽ ማጉያ እንዳይሰማ በማድረግ እና አንድነቶችን በማሰር የታቀደው የመቀሌ የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት ዘመቻ እንዳይሳካ አድርጓል። አምባገነኖች ከጠብመንጃ ይልቅ ነፃ ፕሬስ እንደሚፈሩ እናውቃለን። ባለፈው ሳምንት ግን በመቀሌ አምባገነኑ ህውሃት የድምጽ ማጉያ ሲያፍን አስተዋልን። ድምጽ ማጉያ አይገድልም። ህውሃት ግን ለምን ድምጽ ማጉያ ይፈራል? ድምጽ ማጉያ እንደ ነፃ ፕሬስ ከአንድ ሰው የሚተላለፍን መልዕክት ለብዙ ሰዎች በአንድ ጊዜ እንዲደርስ ያደርጋል። አምባገነን ህውሃት የፈራውም እሱን ነው። ስለዚህ የሰብዓዊ መብት መከበርን አስፈላጊነት የሚቀሰቅስ የድምጽ ማጉያ ከሐምሌ 25 ቀን ጀምሮ በመቀሌ ስራ ላይ እንዳይውል ተደረገ በህውሃት። በተጨማሪ የአንድነቶችን የቅስቀሳ ቁሳቁሶች ህውሃት በአደባባይ በፖሊስ አስነጠቀ። በቅስቀሳ ላይ የነበሩትን የአንድነት ፓርቲ ብሄራዊ ምክር ቤት አባል አቶ እንግዳ ወ/ፃዲቅ እንዲሁም የትግራይ ዞን የአንድነት ፓርቲ አመራር አባል የሆኑትን አቶ ክብሮም ብርሃነ እና አቶ አርአያ ፀጋይን አሰረ። የመቀሌ ህውሃት አስተዳዳሪ እና የጸጥታ ኃይሎች እነዚኽን እና ሌሎች ማለቂያ የሌላቸው መሰናክሎችን በመፍጠር የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት ዘመቻ በመቀሌ እንዳይሳካ አድርጓል። ህውሃት የመቀሌን ህዝብ አሳብ በነፃነት የመግለጽ ህገ-መንግስታዊ መብት ጥሷል። ወንጀል ፈጽሟል።
እንግዲህ ህውሃት እና ሰብዓዊ መብት የሚሰብኩ ድምጽ ማጉያዎች፣ ህውሃት እና ሰብዓዊ መብት የሚሰብኩ መኪናዎች፣ ህውሃት እና ሰብዓዊ መብት እንዲከበር የሚጠይቁ በራሪ ወረቀቶች እሳት እና ጭድ መሆናቸውን ባለፈው ሳምንት በመቀሌ ህውሃት ወለል አድርጎ እንዲታየን አድርጓል። ህውሃት እና ሰብአዊ መብት እሳት እና ጭድ ናቸው። ግን ለምን? ከፍ ብለን እንዳነበብነው ደግሞ አንድነቶች በአንድ ወገን ፀረ-ሽብር ህግ ለማሰረዝ ሰላማዊ ትግል ዘመቻ ሲያደርጉ እግረመንገዳቸውን በኢትዮጵያ ከቀድሞው የመገዳደል የፖለቲካ ትግል ባህል ወደ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ባህል ሽግግር መሰረት እየጣሉ ነው። በዚህስ ረገድ ምን ይደረግ? ስለሆነም የዚኽ ጽሑፍ ግብ (1ኛ) ህውሃት እና ሰብዓዊ መብት ለምን እሳት እና ጭድ ሆኑ? እና (2ኛ) የፖለቲካ ትግል ባህል ሽግግሩ ሳያቋርጥ እንዲዳብር እና በህዝባችን ዘንድ እንዲሰርጽ ምን እናድርግ? ለሚሉትን ሁለት መሰረታዊ (መርህ ነክ) ጥያቄዎች መልስ መስጠት ነው።
(1ኛ) ለምን ህውሃት እና ሰብዓዊ መብት እሳት እና ጭድ ሆኑ? የመግደል አቅም የሌላቸውን እንደ ድምጽ ማጉያ አይነት ቁሳቁሶችን ህውሃት ለምን ሊፈራ ቻለ? ለሚለው ጥያቄ መልስ እንስጥ።
የመንግስት ስልጣን ከምርጫ ሳጥን ይመነጫል የሚለው የፖለቲካ ትግል ባህል በሰላማዊ የፖለቲካ ትግል የሚፈጸም ነው። ህውሃት ይኼን የፖለቲካ ባህል ከወሬ ባሻገር አያውቀውም። ባህሉም የለውም። በነፃ ምርጫ እመረጣለሁ ብሎም አያምንም። የመንግስት ስልጣን ከጠብመንጃ አፈሙዝ ይመነጫል የሚለው እርስ በርስ መጨራረስን በይፋ የሚሰብከው ፍልስፍና ነው የህውሃት የፖለቲካ እምነት። ህውሃት ተወልዶ ያደገው ይህን የፖለቲካ እምነት በመከተል እና በመፈጸም ነው። ይኽ የፖለቲካ ፍልስፍና ደግሞ ለስልጣን እንጂ ለሰብዓዊ መብት ዋጋ እንደማይሰጥ ግልጽ ነው። ትጥቅ ትግል እና ሰብዓዊ መብት የተባሉት ሁለት ነገሮች እሳት እና ጭድ ናቸው። ባጭሩ ትጥቅ ትግል እየሰብክ እና እያራመድክ ሰብዓዊ መብት አክባሪ ነኝ አትበለኝ ነው የምልኽ!!!
ህውሃት ሳያቋርጥ ለአስራ ሰባት አመቶች በእርስ በርስ ጦርነት ህዝብ አጫርሶ፣ መንደሮች አፍርሶ እና ህዝብን ለስደት ዳርጎ ለስልጣን የበቃ ድርጅት ነው። እንደሚታወቀው ህውሃት ቲ.አል.ኤፎችን በተኙበት አርዶ፣ ኢ.ዲዩ.ዎችን፣ ኢህአፖችን እና የደርግን ወታደሮች ፈጅቶ ነው እዚህ የደረሰው። በትግራይም ህውሃትን ከተቀላቀሉ ወጣቶች ውስጥ ወደ ቤተሰቦቻቸው መመለስ የፈለጉን በአረመኔነት ገድሎ፣ በውስጡም ቢሆን ከአምባገነኖቹ መሪዎቹ የተለየ አሳብ የነበሩዋቸውን አባላቱን እየፈጀ፣ ገበሬውን ስደተኛ እያደረገ፣ የውጭ እርዳታ ለማግኘት ድርቅ እልቂት በአረመኒነት እንዲባባስ እያደረገ ነው ለስልጣን የበቃው። ይህ ሁሉ ተግባሩ ህውሃትን የሰብዓዊ መብት አፍራሽነት የሻምዮንነት ማዕረግ ያስገኝለታል። ህውሃት እና ሰብዓዊ መብት እሳት እና ጭድ ናቸው።
ህውሃት ስልጣን ላይ ከወጣም ወዲህ አገር አፈረሰ። የባህር በር አሳጣን። የአልቢኒያ እና የሶቪየት ህብረት አምባገነኖች የጻፉትን ቃል በቃል ቀድቶ ኢትዮጵያን ሊያስተዳድር ሞከረ። አልሰራ ሲለው በሽብር በማስተዳደር ላይ ይገኛል። የአገሩን ህዝብ ታሪክ ጠንቅቆ አውቆ፣ ቀደም ብለው የተፈጸሙ ስህተቶችን አስተካክሎ እና እንዳይደገሙ አድርጎ ህዝቡን አቀራርቦ አገር በመምራት ላይ የሚገኝ ቡድን አይደለም።
ስለዚህ ባለፈው ሳምንት ህውሃት በመቀሌ እና በሌሎች ከተሞች የፈጸማቸውን እንቅፋቶች እና ወደፊት ሰላማዊ ትግላችንን ለማራማድ በምናደርገው ጥረቶች ከህውሃት በኩል የሚገጥሙን ፈተናዎች ምንጫቸው ይህ የህውሃት ከሰብዓዊ መብት ማክበር ባህል ጋር እሳት እና ጭድ መሆኑ እንደሆነ መዘንጋት የለበንም። በህገ-መንግስቱ ውስጥ የተዘረዘሩት ሰብዓዊ መብቶችም ቢሆኑ የምዕራቡን አለም ለማጭበርበር እና የገንዘብ እርዳታ ለማግኛ እንጂ አምባገነኑ መለስም ሆነ ዛሬ ኢትዮጵያን የሚያስተዳድረው የመኪና ጎማ አስተንፋሽ ወሮበላ ህውሃት ፍጽም አያምንባቸውም። ህውሃት የፖለቲካ ባህሉ መግደል ነው። ስብዕናው የተሟጠጠ ነው። ታሪኩ ደም ነው። ስለዚህ ህውሃት በኢትዮጵያ ዲሞክራሲ ስርዓት መገንባት የሚያስችለው ባህል ፍጹም የለውም። በዚህ ሁሉ ምክንያት ሰብዓዊ መብት የሚቀሰቅስን የድምጽ ማጉያ ህውሃት ቢፈራ ሊገርመን አይገባም።
(2ኛ) የፖለቲካ ትግል ባህል ሽግግሩ ሳያቋርጥ እንዲዳብር እና በህዝባችን ዘንድ እንዲሰርጽ እንዴት እንርዳ? ህውሃት አምባገነን ነው። አምባገነን ይፈራል። ህውሃት በህዝብ ይሁንታ ስልጣን ላይ አልወጣም። ህጋዊነት እንደሌላቸው ህውሃቶች ብልቦናቸው ያውቁታል። ስለዚህ ከጠበንጃ ይልቅ ህዝባዊ ነፃ መሰባሰብን፣ ህዝባዊ ነፃ ውይይትን እና ህዝባዊ ተሳትፎን ይፈራሉ። ህዝቡ በነፃነት የሚያደርጋቸው ነገሮች አምባገነኖችን ያስደነግጧቸዋል። ያስበረግጓቸዋል። የኢትዮጵያ ህዝብ ሰላማዊ ትግል ወታደሮች ነን የምንል ሁሉ እነዚህን የአምባገነኖች ሁሉ መለያ መሰረታዊ ጸባዮች ጠንቅቀን ልናውቅ ይገባል። የፖለቲካ ትግል ባህል ሽግግር ቀላል እንደማይሆንም በቅድሚያ ልንገነዘብ እና ልንዘጋጅ ይገባል። የሰላም ትግል ሰራዊት ትግባሮች ድርብርብ ናቸው። ለምሳሌ የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት ዘመቻ ለማኪያሄድ እንኳን አንድነቶች የሰላማዊ ትግልን ባህል ለህዝብ ከማስተዋወቅ በተጨማሪ በየከተማው የሚገኙ የህውሃት አስተዳዳሪዎች እና የፀጥታ ኃይሎችን ሲያግባቡ፣ ሲቻል ሲያላምዱ፣ እንዳይፈሩ እና በተወሰነ ደረጃም ቢሆን እንዲያምኑዋቸው ሲጥሩ፣ ወደ ድርድር እንዲመጡ ሲያበረታቱ እና የመሳሰሉትን ሲያደርጉ አይተናል። እንደ አስፈላጊነቱም የተመጠነ ‘የጀግኖች’ መውጫ በር መስጠት ሊያስፈልግ ይችላል። ይኽ ሁሉ መቼ መደረግ እንዳለበት እና እንደሌለበት እና የትኛው መቅደም እንዳለበት ማወቅ ያስፈልጋል።
የፖለቲካ ትግላችንን ባህል ሽግግር ለማፋጠን ህውሃትን የተጀመረው የፖለቲካ ባህል ሽግግር አካል ማድረግ ለሁላችንም ይጠቅማል። ይኽን ለማድረግ ሰለአምባገነኖች ፀባይ ከፍ ብለን የዘረዘርናቸውን ማወቅ እና ተገቢውን ስራ መስራት ይጠቅማል። የሰላማዊ ትግላችን ግብ ህውሃትን ለመበቀል አይደለም። በፍጹም። የሰላም ትግል ወታደር ግቦች ህዝባችንን ወደ ነፃነት፣ ዲሞክራሲ እና ልማት ማሸጋገር ነው። ይኽን ከስኬት ለማድረስ እራስን በዘመናዊ ሰላማዊ ትግል ንድፈ አሳብ እና አፈጻጸም መቃኘት ያስፈልጋል። እንደትናንቱ በሰላማዊ ትግል መዝገበ-ቃላት ትርጉሙ ብቻ መወሰን በቂ አይደለም። የሰላማዊ ትግል ክህሎታችንን ማዳበር አለብን።
ስለዚህ የመቀሌ አንድነቶች የወሰናችሁት የማፈግፈግ ውሳኔ የሚያመለክተው ብስለታችሁን እንጂ መሸነፋችሁን አይደለም። በማፈግፈግ የሰላም ትግል ሰራዊትን ለነገ ማቆየት ጠቃሚ ነው። ይኽን አይነቱ ማፈግፈግ መፍራት አይደለም። የሰላም ትግል ሰራዊት በመቀሌ ያላጠናቀቀው ተጨማሪ ስራ መኖሩን ተገንዝቦ ሰልፉን ወደፊት ማስተላለፉ አኩሪ እርምጃ ነው። አንድነቶች በመቀሌ የደረሰባችሁ ጠንካራ እንቅፋት እና ያደረጋችሁት አይነት ማፈግፈግ እነ ጋንዲም በዘመናቸው ትግላቸውን ወደ አዳዲስ ከተሞች ለማሰራጨት ጥረት ሲያደርጉ ደርሶባቸዋል። አፈግፍገዋልም። አንድነቶች ሰላማዊ ትግላቸውን በመቀሌ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ እና መስከረም 2006 ዓ. ም. ከመግባቱ በፊት ስኪታማ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርጉ ጥርጥር የለኝም። ካለፈው ሳምንት አንድ ነገር ተምረናል። በመቀሌ የተሳካ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ እንደ ጅንካ፣ አርባምንጭ ወይንም ባህርዳር የአንድ እና ሁለት ቀን ቅስቀሳ እንዲሁም የጥቂት አንድነቶች ስምሪት ብቻ በቂ አይደለም። መፍትሄው ዘመቻውን ማጠናከር ነው። ተጠባባቂ ኃይል መመደብ ሊያስፈልግም ይችል ይሆናል። የስለማዊ ትግሉ ነፋስ ከመቀሌ ተነስቶ ወደ አክሱም እና አዲግራትም እንዲነፍስ ማድረግ ይጠቅማል። በመቀሌ የተከማቸውን የህውሃት ኃይል ለመበተን።
በአንድ ወገን የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት ዘመቻ በመቀሌና በቀሩት ከተሞች እንዲቀጥል ስንታገል በሌላ በኩል ህውሃት አንድነት ፓርቲን ለመወንጀል እና ክትግል ሜዳ ለማስወጣት የማይፈነቅለው ድንጋይ እንደማይኖርም ከወዲሁ መገመት እና መከላከያውን ማዘጋጀት ይኖርብናል። ይኽን ምኞቱን ለማሳካት ህውሃት የተቻለውን በማድረግ ላይ ስለመሆኑ ባለፈው ሳምንት በወላይታ የአንድነት ፓርቲ የዞን አመራር አባል በሆነችውን በወ/ሮ ሀድያ መሀመድ ላይ የፈጸመው ተቋሚ መረጃ ነው። ህውሃት ካለ ምንም ምክንያት ወ/ሮ ሀድያ መሀመድን ካሰረ በኋላ የአንድነት ፓርቲ ህዝበ ሙስሊሙን ለአመፅ ያነሳሳል የሚል ሰነድ እንድትፈርም አግባባት። እምቢ አለች። ከዚያ ህውሃት ሊያስገድዳት ሞከረ። በኢንቢታዋ ጸናች። እስሩ ቀጥሏል። አንድነቶች ህውሃት ሊቀድማችሁ አይገባም። ለምሳሌ በወ/ሮ ሀድያ መሀመድ ላይ የተፈጸመውን በአገር ቤት እና በውጭ የሚኖሩ ዜጎች እንዲሁም ዲፕሎማቶች
እንዲያውቁት ሰፊ ዘመቻ ማድረግ ይጠቅማል። ህውሃትን ተአማኒነት ለማሳጣት። ሌላም ይደረግ። ይኽ ፍራቻ አይደለም። ጀግኖች የሚያደርጉት ጥንቃቄ ነው። አንድነቶች በርቱ!!!
አንባቢዎች ሆይ! አንድነቶች ፀረ-ሽብር ህግን ለማፍረስ እና የፖለቲካ ትግል ባህላችንን ለመቀየር የጀመሩትን ዘመቻ እንቀላቀል። እንርዳቸው! የተጀመረው አዲስ ታሪክ አካል እንሁን!!!
የሚከተሉትን በማድረግም በመሰራት ላይ ባለው ታሪክ ማህተማችንን ማስቀመጥ እንችላለን።
እርዳታ፥ በገንዘብ!
እርዳታ፥ በአሳብ!
እርዳታ፥ መረጃዎች በፍጥነት በማሰራጨት!
እርዳታ፥ ፊርማዎች በማሰባሰብ!
እርዳታ፥ እንደገና በገንዘብ!
ድረ ገጻቸው፥ www.andinet.org