Wednesday, February 12, 2014

“ጥቁሩ ሰው” - የጥቁር ሕዝብ አባት (ከስንሻው ተገኝ)

 አንድ ዘመን ሥርዓተ መንግስቱ በመቆየትም ሆነ አባላቱ የአሥራ ሰባተኛው ክፍለ ዘመን የተረት ዓለም ሰዎች ስለ መሰሉን- ሁሉም ነገር ስለገለማን አዲስ ሥርዓት፣ አዲስ መሪ፣ አዲስ ዘመን መናፈቅ ይዘን ነበር። ሰዓሊ ሁሉ፣ ደራሲ ሁሉ፣ ጸሐፌ -ተውኔት ሁሉ እጁን የሚያሟሸው በቴዎድሮስ ሥዕል፣ ተውኔትና ታሪክ ሆነ። ብርሃኑ ዘሪሁን- የቴዎድሮስ እንባ -(መጽሐፍ) ከዚያ በፊት ደጃዝማች ግርማቸው ተክለሐዋርያት- ቴዎድሮስ (ተውኔት) አቤ ጉበኛ - አንድ ለእናቱ (ታሪካዊ ልቦለድ) ጸጋዬ ገብረ መድኅን - ቴዎድሮስ (ተውኔት)…ሥዩም ወልዴ - ሥዕል..ታደሰ ወ.አ….ቅርጻቅርጽ እና የሥነ ጥበባት ትምህርት ቤት ሥስት አራተኛ ተማሪዎች..የቴዎድሮስ ሥዕል ግጥም -ቅኔ- ሥዕል አለፈላት። 
ከአሮጌና ከገለማ ሥርዓት ነፃ የሚያወጣ አመጸኛና አመጻ የሚመራ ጀግና ስንፈልግ ባጀንና ቴዎድሮስን አገኘን። ከመቶ አመት በኋላ ነው ቴዎድሮስ የተፈለገው። በአጤው ሥርዓት በአንዳንድ ደራስያንና የዘመን ታሪክን በውዳሴና በነቀፋ በሚያቀርቡ ግለሰቦች ዘንድ እንደጭራቅ ይቆጠር የነበረው መይሳው ካሣ በለውጥ መሪነት የተፈለገበት መሪ ነበር። አብዮታዊው መሪ ጓድ መንግሥቱ እንኳ፥ “ቴዎድሮስ” (ምናልባትም ዳግማዊ ቴዎድሮስ) እኔ ነኝ። የዚህን ሕዝብ አብዮት እንድመራም ከሙታን የተጠራሁ ነኝ” እስከ ማለት ደርሰው ነበር። በቴዎድሮስ መንገድ አልተጓዘም እንጂ። በተረተኞች፣ በተረበኞችና በዋልጌዎች፣ በጐታቾችና በክፍፍል በኖሩ ዘንድ ተወዳጅ ያልሆነው ሕልመኛው ቴዎድሮስ በእርግጥ ከዘመኑ አርቆና አልቆ የሚያይ ስለሆነ ከወቅቱ ደባትርና ከመሳሰሉት ጋር ስምምነት አልነበረውም።
የአገር አመራር በተበላሸና ሕዝቡ የሚያምነው መንግስት ባጣበት፣ ብሔራዊ አንድነቱና ዳርድንበር አስከባሪ በሚሻበት ሰዓት ከመሐሉ የወጣ የጐበዝ አለቃ ሲያደንቅ ይገኛል። እንዲያ ካልሆነ ደግሞ ከአባት መሪዎቹ መካከል ያደነቀውን፣ የሚያደንቀውናና የሚያከብረውን መናፈቅ ይጀምራል። ባያውቀውም። ዛሬን ያስቡአል። አገር እንደ አቃቂ በሰቃ (ኮሎናልቤ) ብስኩት ፍርክስክሱ በወጣበት፣ ሕዝብ እንዲከፋፈልና እንዲጨራረስ ማናቸውም ዓይነት ሴራ በሚጐነጐንበትና መቀበሪያ ሳይቀር “እናገኝ ይሆን” የሚል ስጋት በተጫጫነን ሰዓት “የአንድነትን ጌታ” የአገሪቱን እውነተኛ አባት መናፈቅ ያለ ነው። እነዚህማ ሸጡን። እነዚህማ ለወጡን። መሬቱን ጋጡት። ከትውልዱ አባልነት መብታችን አንዲቱንም አላከበሩልንም። የአንድነትን አባት፣ የዘላለም ኩራታችን ምንጭ፣ ሁሉንም አበሻ በእኩልነት የመራውን ጀግና እንድንናፍቅ ጊዜው አስገድዶአል። ምኒልክን! ይኸ ደግሞ ከመካከላችን እንደ ምኒልክ ያሉ የአንድነት እምነት አራማጆች እስኪንቀሳቀሱ ድረስ ነው።
ነፃነት አንድን ሕዝብ ወደፊትና ወደላይ የሚያንደረድር (የሚወስድ) ኅይል ይሻል። ስለዚህ እውነተኛና ከዚህ በኋላ የሚመሩን (ከዘመኑ ቀድሞ እንደ ተወለደው ምኒልክ) ሰዎችም ወደፊት ብቻ ሳይሆን ወደ “ላይም” ሊመሩን የተዘጋጁ ናቸው። እነዚህ ቆነጃጅት አልተወለዱም አይባልም። እንዲያውም አይተናቸዋል። ዳስሰናቸዋል። ዓለምም አውቆአቸዋል። እኛ ግን ከጥቃት፣ ከእሥራት፣ ከእንግልት…ከመከራ አላዳናቸውም፥ እስክንድርን፣ አንዱዓለምን፣ በቀለን…ካድናቸው። ለወያኔ ወረወርናቸው ለአውሬ። አገርን የሚያድን መሪ ብቻ አይደለም። ዋናው ሕዝቡ ነው። በአድዋ ወሳኙን የመሪነት ሚና የያዘው ምኒልክ ነበር። የተዋጋው ሕዝቡ ነበር። ሕዝባችን ቅንና ጀግና መሪ፣ መሪውም ታማኝና ቆራጥ ሕዝብ ያገኘበት አንድ ወቅት ይኸ ነው።
በአንጻሩ በአመራር የጊዜ ማኅፀን ውስጥ ያሉት ወይም ቢወለዱም በአመራር ጉልምስና ዘመን ላይ የሚገኙት “መልካካም የኢትዮጵያ ልጆች” ወደ አገር አዳኝነቱ መንበር ሲመጡ የሚገጥማቸው ፈተና የትየለሌ ነው። ሁላችሁም አስቡት። የተሸጠ አገርና መሬት የማስመለስ ግዴታ ሊሸከሙ ነው። የተከፋፈለ የሕዝብ ይዞታ ሊያስተካክሉ ነው። የኢኮኖሚውን ሥርዓት መስመር ሊያስይዙት ነው። “ወደ ላይ መምራት” ባልሁት የአመራር ፈርጅ ደግሞ የሚጠብቃቸው ከዚህ ሁሉ በላይ ነው። በታላላቅ ዲታዎችና መንግሥታት ትእዛዝና መሪነት ሥር የወደቀችውን አገር ዜጐችዋ ባለሥልጣናት ይሆኑ ዘንድ መንገዱን መጥረግ አለ። የሕዝብን ነፃነት፣ መብትና ሕዝቡ በአገሪቱ ላይ ያለውን ሉዓላዊነት ማወቅና ማክበር አንዱ ነው። የሕብረተሰቡን መንፈሳዊና ባሕላዊ መብቶች ማረጋገጥና የመንግስትን ጣልቃ ገብነት ማስወገድ፣ የጽሑፍና አሳብን በነፃ የመግለጥ ተፈጥሮአዊ መብቶቹን መንከባከብ፣ ፍትሕና ርትእ በራሳቸው ጐዳና ከመጓዝ እንዳይታወኩ ማድረግ ማለት ነው። ዝርዝሩ በዚህ ይቀጥላል። በመሰረቱ ደግሞ ታሪክ ስትቆፍሩ ብትውሉ አገር የሸጠ፥ የአገር መሬት የቸበቸበ መሪ ታይቶ ተሰምቶ አይታወቅም። በውጭ ምስጢር ባንክ የተቀመጠውን ገንዘብ ቁልፍ መለስ ለሚስቱ ካልሰጣት እሱም በሞቱ ከስሮአል። እኛም ያንን ለማስተካከል ብዙ ጥረት ማድረግ ይጠበቅብናል። የእሱን ወንጀል።
አጼ ምኒልክ
ጆርጅ ኦርዌል በ1984 መጽሐፉ በአምባገነኖች አገዛዝና ዘመን “እውነት ውሸት፣ ማይምነት እውቀት፣ ጥላቻ ፍቅር..ይሆናል” ይላል። ስለዚህ የወያኔን ባሕርያት የምንረዳው ዛሬ አይደለም። አብረን ኖረን የመንግስት ጠባያት ያልሆኑ- መሆንም የማይገባቸውን ስርቆትን፣ ተራ ውንብድናን፣ ቅጥፈትን፣ የጅምላ ግድያን፣ ፀረ ሃይማኖት አቋምን፣ የመብት ረገጣን…በየዓይነቱ እንደ ቡልኮ ተከናንቦ አይተነዋል። አንዳንድ ፀረ ሕዝብ ተግባራት ከየት መጡ ሳይባል እንኳ “የእሱ ሥራዎች ናቸው” ማለት ቀላል ሆኖአል። ትግርኛ ተናጋሪ ወገኖቼ ፀላዔ ሰናይ ይሉአቸዋል። አንዳችም በጐነት ያልተፈጠረባቸው ለማለት ነው። የሰሞኑን ደንባራ ፖለቲካ ለአብነት ማውሳት ለተነሳንበት ጉዳይ ብርሃን ይፈነጥቃል ባይ ነኝ። 
በቅጥፈት የተካነው ሰውየ ከተለያቸው ወዲህ ወያኔዎች ያንኑ የተለመደ ውሸት ከመደጋገም በቀር ሌላ መፍጠር፣ በሌላ ስልት ማወናበድ አልሆንላቸው ብሎአል። ውሸት እንደ ቅርስ በነገሠበት አምባቸው ደግሞ ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ ያላትና ያፈራችው መንፈሳዊና ስጋዊ ቅርስ ሁሉ አንደኛ መጥፋት አለበት፣ ዳግመኛም- አገሪቱ ካልጠፋች..ታሪክዋ ከዛሬ ተጀመረ መባል አለበት። ታሪክ ከእነሱ አልነሳ ሲላቸው አሁንም ያለፈውን በጐ ታሪክ፣ አኩሪ ባሕልና ጀግንነት፣ የአንድነት ጥበቃ መንፈስ…እንደ ቀላል ነገር ለመግደል ወጥተዋል።
                   ውሸታቸው ባያልቅም እውነት መናገር እንጀምር
ለዚህ ሥርዓት ማንኛውም ያለፈ ታሪክ፣ ታላላቅ ጀግኖች፣ ዳር ድንበር…የረከሰና የተናቀ፣ መለወጥና መደምሰስም አለበት። ሁላችሁም ለወያኔ ዓላማና ዛቻ፣ ቅጥፈትና ፀረ አንድነት እንግዳ አንዳለመሆናችሁ የሟቹንም ዛቻና አቋም ታስታውሳላችሁ። ስለ ሰንደቅ ዓላማ ምን አለ? ስለ አገሪቱ አንድነት ምን አለ? ምንስ ፈጸመ? ተከታዮቹስ ምን እያሉና ምን እያደረጉ ናቸው? በአጭሩ የሚነገረው ውሸት፣ የፈጠራ ታሪክና ከፋፋይ ፕሮፖጋንዳ አልቆ እናርፈዋለን ብለን ስናስብ ከቶውንም ወፍጮው ይበልጥ እየፈጨ ስለሆነ በውሸቱ መካከል ስለእነሱም እውነቱን መናገር መጀመር ያለብን ይመስለኛል። የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ትሩማን “ሪፐብሊካኖች ስለእኛ ውሸት መናገርን ካላቆሙ ስለእነሱ ያለንን እውነት መናገር መጀመር ያለብን ይመስለኛል” ብለው ነበር።
ስለ ዳግማዊ ምኒልክ ጥቂት ከመናገሬ በፊት ስለ መለስ ጥቂት-እጅግ ጥቂት ለማለት እወድዳለሁ። የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ሲዘልፍ..ዋና ዓላማው የኢዮጵያን ስም መለወጥ ነበር። ስለዚህ ለብዙ ዓመታት ኢትዮጵያን በስም ከመጥራት ይልቅ “አገሪቱ” ነበር የሚለው። ሥልጣን ሲጥመውና አገሪቱም የማትፈርስ (በቀላሉ) ስትመስለው “ኢትዮጵያ” ማለት ይዞ ነበር።
ቀደም ሲል ጆርጅ ኦርዌልን ያነሣሁበት ምክንያት “ውሸት እውነት” የሚሆንበትን ትክክለኛ አጋጣሚ መከሰት በሚመለተው ነው። እንደሚባለው በአምባገነን መንግሥት ሥር የመጀመርያው ጥቃት የሚደርሰው “በእውነት” ላይ ነው። በሕዝባዊ እውነት ላይ! በታሪኩ ላይ ነው። በጀግኖቹ ላይ ነው። ስለዚህ በአገር የተገኘው ቀጣፊ ሁሉ ዛሬ በፕሮፓጋንዳው ሰፈር፣ በአራት ኪሎ ቤተ መንግስትና በየክልሎቹ አመራር አምባ የተሰባሰቡት የሥነ አእምሮ ጠቢባን (pathological liars) የሚሉአቸው የሚታዘንላቸው ሕመምተኞች፣ እውነትን የሚፈሩ፣ እውነት ሲነገር የሚደነግጡ፣ እውነት ሲወጣ የሚረበሹ ናቸው። ስለዚህ “አንድነት” በተፈተነበትና የአገር ሽያጭ በደራበት ሰዓት አንዱ ማወናበጃ ስልት ያው ምኒልክን በወንጀል መክሰስ ነው። “አምስት ሚሊዮን ኦሮሞ ገደለ” ነው አዲሱ አማርኛ። ለመሆኑ በምኒልክ ጊዜ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር ከ5 ሚሊዮን ይበልጥ ነበር? ከዚህ ውስጥ የኦሮሞው ቁጥር ስንት ነበር? ለመሆኑ ምኒልክ ማነው? ምን ሰራ? ሕዝብን ከጫጫታው (ከዘመኑ) ለማዳን መሞከር አለብን ወይስ ታሪክ ነፃ ያወጣዋል በሚል አደብ እንግዛ?
                      “ጥቁሩ ሰው” -  እንደ ሰው
ታሪክ የበጐነት ምስክር - ወይም ለበጐነት የሚያደላ እማኝ ብቻ አይደለም። የአጥፊዎችን ጥፋት፣ የከሐዲዎችን አሳፋሪ ተግባር፣ የአምባገነኖችን ክፋትና ኢሰብአዊ አገዛዝ ጭምር ዘግቦ ለትውልድ ያስተላልፋል። ይሁንና ታሪክ የማያውቁ አዋቂዎች በመምሰል፣ አዳዲስ ድርሰት በመጻፍ ከሐቅ ግድግዳ ጋር የሚላተሙ፣ በባሕርያቸው ፀላዔ -ሰናይና የእውነት ጠላትነት ያላቸው ደካማ ፍጡራን መድረክ ሲደላደልላቸው የሚያዥጐደጉዱት ቅጥፈት መታለፍ እንደማይገባው እየተከሰተልን መጥቶአል። እስካሁን ግን “ለቅጥፈት ማስተባበያ” ወይም ማስተካከያ አያስፈልገውን በሚልና ውሎ አድሮ ሐቅ ይረታል በሚል እምነት ቅጥፈት ቅጥፈትን፣ ፈጠራና ድንፋታ ራሱን ሲፈጥርና እንደአሜባ ሲራባ በቸልታ ያለፍናቸው ጉዳዮች ሞልተዋል። ከሁሉም ከሁሉም አንድን ኅብረተሰብ የሚያቃጥለው የታሪኩና የጀግንነቱ መታወቂያ ሰነዶች፣ ግለሰብ ጀግኖችና ብሔራዊ መከበሪያ ሐውልቶቹና ቅሪቶቹ መደፈር ነው። በዚህ ረገድ ብዙ ተደፈርን። በዓለም አቀፍ ደረጃ የ”ታላቅ መሪነት”ን ደረጃ የተቀዳጁትን፣ ጠላት ሳይቀር የሰገደላቸውን መሪዎቻችንን ሳይቀር ዛሬ የራሳችን ልጆች በእነዚህ ላቅ ያሉ ሰዎች ላይ ሲያቅራሩ ስንሰማ እንቅልፍ መንሳቱ አልቀረም። 
       የወያኔ ቀዳሚ ሰልፍና ፍልስፍና ሕዝብን መከፋፈልና አገሪቱንም ማፍረስ መሆኑን ለመጀመሪያ ጊዜ ተጠራጥረው ይከራከሩን የነበሩ ሰዎች ዛሬ ከግንዛቤ በመነሳት ራሳቸው “አገር እየጠፋ” መሆኑን እያረዱን ነው። በወያኔዎች በኩል ደግሞ የአገሪቱንም ሲሳይ እያፈሱ መልሰው አገሪቱን ለማጥፋት ማናቸውንም ሴራ እየፈፀሙ ናቸው። የትሮትስኪ ታሪክ መዝጋቢና የሩሲያን አብዮት ክሽን አድርጐ ያቀረበው አይዛክ ዶቸር ስለ ሩሲያ አብዮት መሪዎች ሲጽፍ “እነዚህ ሰዎች የማያውቁትንና ሊያውቁ ያልቻሉትን አገር ተረከቡ። ወይም በእጃቸው አስገቡ። ቀጥሎም የሚያምኑበትን አቃጠሉት። አቃጥለውም ሰገዱለት” ይለናል። አዎን ወያኔዎች ጥገትዋን አልበው እየጠጡ፣ አርደው ሊበሉአትም ፈለጉ” ለማለት ይቻላል። በተአምር በእጃቸው የገባችውን አገር ማዳን የብዝበዛቸውና የዘረፋቸው ዋስትና በሆነ ነበር። ይልቁን እዚህ ከደረሱ በኋላ እንኳ የዚህን አገር አንድነት ማዳን ቢሞክሩ ቢያንስ ልጆቻቸው አገር አለን እንዲሉ ባስቻላቸው ነበር። ይልቁንም ኦሮሞዎች ነን የሚሉ በዕድሜም፣ በግንዛቤና በአእምሮ ያልበሰሉ ልጆችን በመመልመል የሚያንጫጩብን እነዚሁ አገር በእጃቸው የወደቀ ሰዎች ናቸው። ምኒልክን ለመወንጀል የክሱን ነጥብ ሁሉ ከየት አገኙት?
 እውን እነዚህ ጨርቋ ሕፃናት - የጨርቋ አእምሮ ውጤት የሆነ ፕሮፓጋንዳ በጩኸትና ሰላላ መላላ በሆነ ልሳን ሲያስተጋቡ የዚህ አገር ዋልታና ወጋግራ የሆነው ኦሮሞው ኅብረተሰብ ምንኛ እንደሚያፍርባቸው ትገነዘባላችሁ?  ለመሆኑ ከኢትዮጵያ ታሪክ ባለቤትነትና ክብር ሊነጥለን የሚችል ማነው? ጃዋር? አያት ቅድመ አያቶቻችን ደምና አጥንት የሰጡአት አገርኮ ናት! የወያኔ የመስዋዕት ጠቦቶች ለሆኑት እነዚህ ኅፍረተ ቢሶሽስ የኦሮሞን ውክልና ማን ሰጣቸው? ስለማያውቁት፣ ስላላወቁትና ሊያውቁትም ስላልፈለጉት ሕዝብ በድፍረት መናገርን ከየት አመጡት? እነዚህ ልጆች “ወገኔ ነው” የሚሉትን ኦሮሞውን ኢትዮጵያዊ ከሌሎች (ለምሳሌም አማራው) ብሔሮች ጋር በማጋጨት ሊያመጡ የሚችሉትን ትርፍ ሊነግሩን ይችሉ ይሆን? ወይ ልክፍት!
ከሶቪየት ኀብረት ኤምፓየር መፍረስ በኋላ አንዳንድ የአሜሪካ የፖለቲካ ፈላስፎች እንደ ሶስተኛ አገር የሚታዩ የኅብረተሰብ ጽናትና ሰላም ያላቸው አገሮች በተቻለ መጠን ተሸንሽነው ብዙ አገሮች እንዲወጣቸው ሰፋፊ ጽሑፎችን በገበያ አውለዋል። ከእነዚህም መካከል መለስ ዶላር ያፈስስለት የነበረው የሐርቫርዱ ሳሙኤል ሐንቲንግተን  ይገኛል። ከዚያም ሌላ አንዳንድ የሲአይኤ ቅጥረኞች ጽሑፎች በየጥናቱ መደብር አሉ። ዩጐዝላቪያ የዚህ ፍልስፍና “ጊኒፒግ” ናት። ከ1991 ወዲህ ደግሞ ኢትዮጵያ የምትታመሰው በዚሁ ረቂቅ የጥፋት አውሎ ነፋስ መሆኑን አንዘንጋው። እነሆ እንደ ጃዋር ያሉ አለማወቃቸውን እንደ እውቀት፣ ጮኾ መናገርን እንደ ሐቅ፣ የፈለጉትን ጥጃ የአምልኮ ጸጋ በመቁጠር አየረ አየራቱን ሲያተረማምሱት ከእንግዲህስ “ተመከር! ተሳስተሃል! በአገር፣ በሕዝብና በታሪክ ላይ ያመጽህ ባለጌ ነህ” ማለት የሚገባ ይመስለኛል። ልድገመውና “በአባቴ ሙስሊምና ኦሮሞ፣ በእናቴ ክርስቲያንና አማራ ነኝ” በማለት ጅምሩን በማይጠቅመው መደምደሚያ ያበላሸዋል። ጃዋር መሐመድ። ሙስሊም፣ ክርስቲያን፣ አማራ፣ ኦሮሞ! ከኢትዮጵያዊነት ውጭ ምን ይሁን?
ጐበዝ በዚህ ዓይነቱ ጊዜ ከየጉድጓዱ ብዙ አይጦች ሊወጡ ይችላሉ። አትደነቁ። አንዳንዶቹ የመታወቅ አባዜ (የእንክብካቤ እጦት አባዜ…ወዘተ) የተከሰተባቸውና “እገሌ” ለመባል የሚጣባ ሕመም ተሸካሚዎች ናቸው።     አንዳንዶቹ ቀጥታ ራሳቸውን ለማያውቁት ተልእኮ በመስዋዕትነት ለመሰጠት በምንዳ የተገዙ ናቸው። ለዚህ ዓይነቱ ተልእኮ የተመደበ በጀት ስላለ ሰው ከተገኘ ገዥ አለ። ሕሊና ለሌለው፣ ለሚሸጥ ወይም ለሚያከራይ ዘወትር ክፍት ቦታ አለ። እነ እንቶኔ በዚህ የሕመም ዘርፍ ላይ በመሆናቸው ሊታዘንላቸው እንጂ ሊታዘንባቸው አይገባም። ቀደም ሲል የተጠቀሰውን ጉብል አንድ ጊዜ በአንድ የቨርጂኒያ አዳራሽ ትልቅ ስብሰባ ላይ አይቼዋለሁ። እዚያ ስብሰባ ላይ ወደ ዘጠኝ መቶ የሚጠጉ ሰዎች ነበሩ። ይሁንና እስኪታወቅ ሳይሆን እስክንሰለቸው ድረስ የባጡንም የቆጡንም ሲናገር ቆይቶ “እዚህ ሥፍራ ኦሮሞና ሙስሊም ለምን አልተጋበዘም?” ይላል። መቸም “ከእናንተ መካከል ኦሮሞ የሆናችሁ ተነሱ! ሙስሊም የሆናችሁ ተነሱ!” አይባልም። ይኸ ደግሞ ከቅን አእምሮ የመነጨ ነው አይባልም። የሌሎቹንም “ዋልጌ ጭንቅላት” ባለዶላሩ ዋሐቢ፣ የሽብሩ ልጆች እነ…..በማናቸውም ሂሣብ ሊገዙአቸው አይፈልጉም አይባልም። ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን እስከ ተዋጉላቸው ድረስ።
አንዳንድ የዋሐን ወገኖቼ የእነዚህን በጥላቻ የተፀነሱ፣ በጥላቻ የተወለዱና የጥላቻን መርዝ በመካከላችን የሚዘሩ ሰዎችን ተጽእኖ እስከ መፍራት ደርሰዋል። ኦሮሞው ኅብረተሰብ እንዳይቀበላቸው ነው? ያፍርባቸዋል። ከአገር እድር ያስወጣቸዋል። ስለዚህ በሶሻል ኔትወርኩ ረገድ ኅላፊነት የወሰዱ ሁሉ ለኦሮሞ ወገኖቻችን የመናገር ዕድል (በሰፊው) መክፈት አለባቸው። በአንድ በኩል ደግሞ ታሪክ የሚያቆሽሹትና ወደ ኋላ እየተመለከቱ የሚናገሩት እነዚህ ወገኖች ርስበርሳችን ስለጀግንነት፣ ስለታሪክ፣ ስለታላቋ ኢትዮጵያ ማንነትና ምንነት….እንድንነጋገር ዕድል እያስገኙልን ይመስለኛል።
                    ጥቁሩ ሰው - ለጥቁር ሕዝቦች
ጀርመኖች በኦቶፎን ብዝማርክ፣ ጣልያኖች በጁሴፔ ጋሪባልዲ፣ ፈረንሳዮች በናፖሊዮን ቦናፓርቲ፣ በዣንዣክ ሩሶ፣ በዣን ደ አርህ፣ አሜሪካኖች በጆርጅ ዋሽንግተን፣ አብርሃም ሊንከን…..እንግሊዞች በዊልያም ዘኮንከረር፣ በዊንስተን ቸርችል፣..ይኰሩም ይኩራሩም
ይሆናል። የእነዚህን ሰዎች ጀብዱ ስንሰማ፣ በትምህርት ቤቶች ዝናቸውን ስናወሳና ስናጠናቸው ስለኖርን የራሳችን ሰዎች እስኪመስሉን ድረስ በልባችን ጽላት ላይ ታትመዋል። ሰዎቹ በየዘመናቸው ለአገሮቻቸው ባበረከቱአቸው አስተዋጽዎችና የተለዩ አገልግሎቶች የየአገራቸው “አባቶች” እስከ መባል ደርሰዋል። በፖለቲካና በወታደራዊ መስክ ብቻ ሳይሆን እነዚህ አገሮች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም አያሌ አገሮች ለአለም ጸጋ በሆኑ ልጆቻቸው አማካይነት በኪነ ጥበባት፣ በሳይንስ፣ በሥነ ጥበባትና በኬንያ (ቴክኖሎጂ) ባርከውናል። ልጆቻቸውን ተጋርተናል።
እንደገና ጀርመኖች በሒትለር፣ ጣልያኖች በሙሶሊኒ፣ ካምቦድያውያን በፓልፓት፣ ኡጋንዳውያን በኢዲአሚን፣ወዘተ እጅግ እንደሚያዝኑና እንደሚሸማቀቁ ይሰማኛል። እኛም የዚች አገር ጐስቋሎች  ኢትዮጵያውያን በሃያ አንደኛው ምዕት ዓመት መለስ የሚሉት እኩይ ነፍስ ለኢትዮጵያ የዛሬው ትውልድ በመስጠታችን ጭብጥ ልናክል ነው። ሞተ ከተባለ ወዲህ እንኳ አገር እየሰጠ፣ አረብና ሕንድ እያነገሰብን፣ ምውት መንፈሱ እንዳሸበረን ነው። ሁላችንም የዓለም ዜጎች ይቺን የጋራ መሬት እኩል እንደምንባረክባት ሁሉ ጀግንነታቸው ያሞቀን የሃያኛው ክፍለ ዘመን ግዙፋን ባለታሪኮች ነበሩ። ጀኔራል ድዋይት አይዘንሐወርን፣ ጀኔራል ጆርጅ ፓተንን፣ ፊልድ ማርሻል ሞንትጐመሪን…እንደራሳችን እንጋራለን የሚል እምነት አለኝ። “እነዚህ ሰዎች ምነው ኢትዮጵያውያን ቢሆኑ ኑሮ” ብዬ በቁጭት አልናገርም። የአንዲት ምድር (ራችን) ልጆች በመሆናቸው ብቻ እንደራሳችን ጀግኖች- የሁላችንንም እምነት በተግባር ያዋሉ፣ የሁላችንንም ጦርነቶች ተዋግተው ያሸነፉ ስለሆኑ “የሁላችንም” እናደርጋቸዋለን። እንደ ምኒልክ ያሉ - እንደ ጐበና ያሉ- እንደ አሉላ ያሉ- እንደ አበበ አረጋይና በላይ ዘለቀ ያሉ ጀግኖች አባቶች ያሉት አገር ልጆች በመሆናችን እኛም ለዓለም ባበረከትናቸው ጀግኖቻችን ኩራት ይሰማናል። በምኒልክ የተመራው የኢትዮጵያ ሠራዊት በአንዲት ጀንበር የአንድ አውሮፓ ኅይል ካንኮታኰተ በኋላ በማግሥቱ የጠቅላይ ሚኒስትር ክሪስፒ መንግሥት (በኢጣክያ ሕዝብ እንደጐርፍ መውጣት ምክንያት) ከሥልጣን ከመወገዱም በላይ በናፖሊ ከተማ የነበረውን የንጉሡን (አምቤርቶ) አልጋ ወራሽ ሕዝቡ በትከሻው ተሸክሞ “ታላቁ ምኒልክና የአድዋ ጀግኖች ኢትዮጵያውያን ለዘላለም ይኑሩ ብለህ ጩኽ” በማለት ቀኑን በሙሉ በዚህ መልክ ሲያንባርቅ እንዲውል አድርገውታል። በማግሥቱ የወጡ የኢጣልያ ጋዜጦች ኢጣሊያ ራስዋ እንደተማረከች አድርገው ጽፈዋል። ምኒልክ!
አንዳንድ የጦርነት ዘገባዎችን፣ መጻሕፍትንና ታሪኮችን ለተከታተሉ ጀግኖች የሠራዊት አዛዦች ድል ካደረጉ በኋላ “ጠላት ነው” በማለት አይንቁትም። ወይም በእጄ ገብቶአል ብለው አይበቀሉትም። እንዲያውም በ”ተቃራኒ መስክ” የተሰለፈውን በክብር ያስተናግዱታል። በጦር መሪነታቸው እጅግ የተደነቁና በመሠረቱ በተቃራኒ ዐውድ ተሰልፈው ታሪክ የሰሩ ጄኔራል መኰንኖችን ላስታውስ እወዳለሁ። በአሜሪካ የሲቪል ጦርነት የኮንፌደሬሽኑ ጦር አዛዥ ሮበርት ሊ በአሜሪካ ሕዝብ ዘንድ ከሜጀር ጄኔራል ጆርጅ ማክሊላን የበለጠ ይታወቃል። በየከተማው መንገዶች ተሰይመውለታል። የጦር ምሽጐች በስሙ ተጠርተዋል። ከስለጠነው ዓለም ሌላም ማስረጃ ለማምጣት ይቻላል።
የሁለተኛው ዓለም ጦርነት ከሚያውቃቸው ታላላቅ ጄኔራሎች መካከል ሒትለር በሰሜን አፍሪካ በዋና አዛዥነት ያሰለፈው ፊልድ ማርሻል አርዊን ሮሜል (የበረሃው ተኩላ) በምዕራብም ሆነ በምሥራቅ- በአክሲስ ፓወርስም ሆነ በአላይድ ፎርስስ እጅግ የተደነቀ ነው። በመሠረቱ ለጀግና ሠራዊት ባላንጣው የተከበረ ነው። በሬሳው አይጫወትም። ወይም ወያኔዎች በኢትዮጵያ ሠራዊት ሬሳና የደከመ አካል ላይ ቆመው እንደ ፈነደቁትና እንደሸለሉት ሳይሆን የሰብአዊነት ክብርና መገመቻ ጠላትን እንደአግባቡ ማድነቅ መቻልም ነው። ለተፋላሚ ክብር መስጠትና እንክብካቤ ማድረግ ነው። እነዚህ ሰነፎች ገዥዎቻችን ምንኛ ደካሞች እንደሆኑ አያችሁት?
ከአገራችንምኮ ለዚህ ክርስቲያናዊ አርአያነትና የሰለጠነ ወታደራዊ ባሕል ምሳሌ አንቸገርም። አድዋ ላይ በአንድ ጀምበር በርከት ያሉ ጄኔራል መኰንኖችን ድባቅ የመታውና ያንኑ ያህል የማረከው እምዬ ምኒልክ በእጃቸው የገቡትን ምርኮኞች ማለፊያ ምግብ እየሰሩ (ፓስታ፣ ሞኮሮኒ ወዘተ) በደንብ ከመመገብ ባሻገር ራሳቸውና ደገኛይቱ ባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ እንደ ሐኪም ቁስል መጥረግ፣ ፋሻ ማሠርና የመሳሰሉትን የሕክምና አገልግሎቶች ጐንበስ በማለት ፈጽመዋል። ጦርነቱ እንዳለቀ ምሽት ላይ በየድንኳኑ እየተዘዋወሩ “ገደልን ብላችሁ እንዴት እንዲህ ያለ ፍከራና ሽለላ ታደርጋላችሁ?” በማለት ኅዘናቸውን እስከ መግለጥ ደረሰዋል። (አንቶኒ ሞክለር ኅይለስላሴስ ዋር በሚለው መጽሐፉ በመጀመሪያው እትም እንደ መግቢያ አድርጐ ገልጦታል።
በሌላው ታሪካቸው እንደ ተገለጠው አጤ ምኒልክ ከንጉስ ተክለሃይማኖት (ራስ አዳል ይባሉ ከነበሩት) ጋር እምባቦ ላይ ሲዋጉ የጐጃሙ ገዥ ቆስለው ሲማረኩ ራሳቸው ከመሬት ተቀምጠው ቆስሉን በጨውና በአልኮል እየጠረጉ እንዳስታመሙአቸው ይታወቃል። በኋላ ደግሞ አጤ ዮሐንስ ያለ የሌለ ጦራቸውን አስከትተው ጐጃምን ወርረው፣ ሥፍር ቁጥር የሌለውን ሕዝብ ዓይን በጋለ ብረት አቃጥለው፣ ሠራዊታቸው ቤት እየዘረፈ፣ በወንዱ  ፊት ሚስቱን እየደፈረና ጐተራ እያራገፈ በጠቅላላው ንጉሰ ነገሥቱ እያዩ ሲያቃጥሉ አጤ ምኒልክ “እባክዎ ጃንሆይ ከንጉሥ ተክለ ሃይማኖት ጋር ተጋጨሁ ብለው ሕዝብዎን አይጨርሱት” በማለት እንደተማጸኑአቸው የተጻፈ ታሪክ ሞልቶአል። እንዲያም ቢሆን የትናንት የአገሪቱን መሪዎች ለመወንጀል አልሻም።
ወደ ሃምሳ ዓመት የሚገመት ሙያዬ ከብዙ ሰዎች ጋር አገናኝቶኛል። እንደ ደጃች ኅይለ ሥላሴ ጉግሳ ካሉ ከሐዲዎች- እንደ ራስ መስፍን ካሉ አርበኞች- እንደ ጋዜጠኛ (ከንቲባ) ደስታ ምትኬ ካሉ በየአድዋው ጦርነት ላይ ከዋሉ የታሪክ ምስክሮች፣ እንደ ፊታውራሪ ተክለሃዋርያት ካሉ በ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ አንስቶ አገሪቱን ከፊውዳል ሥርዓት ለመጠራረግና የፖለቲካውን ሥርዓት ግልብጥብጡን ለማውጣት ከደከሙ ምሁራንና መሪዎች ጋር ትከሻ ለትከሻ ባልተሻሽም አጠገባቸው ተቀምጨ ያልነበርሁበትን ዘመን ልኖረው ሞክሬአለሁ። የሁሉም የጋራ ምስክርነት (የጀግናውም የባንዳውም) ኢትዮጵያ እንደ ምኒልክ ያለ መሪ ታድላ አታውቅም። እግዚአብሔር ይመስገን፤ ጻድቁ ዮሐንስ በጐ አእምሮ የወለደው ነው።
አዎን የዚህ መጣጥፍ አጀማመሬ አውሮፓውያንና አሜሪካውያን (ሌሎችም ሕዝቦች) የሚኮሩባቸው መሪዎችና በመሰረቱም የሚያፍሩባቸው አምባገነኖችም ሊኖሩባቸው እንደሚችል ላመለክት ሞክሬአለሁ። እንዲያውም አገር በችግር ማጥ ውስጥ ስትገባ ልባቸውን፣ ጭንቅላታቸውንና እጃቸውን አስተባብረው ሕዝብን በአንድ ጐራ አሰልፈው ከታላቅ ውጤት ላይ ያደረሱት እንዲህ ያሉ መሪዎች የየአገሮቻቸው አባቶች እስከ መባል ደርሰዋል። ጆርጅ ዋሽንግተንን አላነሣሁምን? የመቶዎች ባሪያዎች ባለቤት ቢሆን እንኳ ሁሉም አሜሪካዊ የአገሪቱ አባት ይለዋል። በዚሁ ልክ የኢትዮጵያን ታሪክ የመረመሩ የውጭ አገር የታሪክ ስዎችና ኢትዮጵያውያን ምሁራን ሁሉ አጤ ምኒልክንና አሳዳጊ አባታቸው አጤ ቴዎድሮስን የኢትዮጵያ አባቶች ይሉአቸዋል። ለከፈሉት የሞት ዋጋ፣ ለተሸከሙት የኢትዮጵያ ግዙፍ ተራራ፣…ይኸ የሚበዛባቸው ክብር አይደለም። ሁለቱ ሰዎች (ባይሆን ጣይቱን እንጨምራለን) ይህን ክብር ካልተቀዳጁ ማን ሊቀዳጅ ነው? ጣይቱን እናታችን ብንል ምንኛ ደስ ባለኝ!
ያለፈው ወር የእምዬ ምኒልክ መቶኛ ሙት ዓመት ነበር። አሸናፊዎች ሁሉንም እንደ ፈለጋቸው በሚያደርጉበት፣ በብር በወርቁ በሚያዙበት፣ ታሪክ ድርሰት ሆኖ በማረሻ በሚጻፍበት፣ የአገር ዳር ድንበር ያለ ጠባቂ በሚቀርበት፣ ጀግኖች የወደቁለት አንድነት መጫወቻ በሆነበት፣ ዜጐች እየተነቀሉ ነጩ፣ ብጫው፣ ጠይሙ…የባዕድ አገር ነጋዴ የሚምነሸነሽበት መሬት ጥንቡን በጣለበት ዘመን ላይ፣ መንግስት ሌባ፣ ሌባም መንግሥት በሆነበት ወቅት-እንደ መገኘታችን ብዙ ብዙ -የለም፤ ሁሉም በጐ አገራዊ ባሕል ትርጉም ባጣበት ሰዓት በሕዝብ ዘንድ ያለው ሐቅ ሁሉ ተጠቂ መሆኑ አንድና ሁለት የለውም። እነሆ ከሃያ ሦስት ዓመታት ወዲህ የኢትዮጵያ ታሪክ ተለውጦ ስለኢትዮጵያ አንድነትና ታሪክ የቆመው ሕዝብና ተቃዋሚ ኅይሎች ከሐዲ ሲባሉ…ወርቁም ሚዛኑም እንዳልነበረ ሆኖአል። ስለዚህ በምኒልክና በጣይቱ ላይ የሚወርደውን የፕሮፓጋንዳ መዓት፣ የፈጠራ ድርሰትና ልብ ወለድ ድርሳን ስታስቡት ለመሆኑ ከወያኔ አምባ የተጠበቀው ሌላ ንግርት ምን ነበር? በግልጽ የኢትዮጵያን አንድነት ተቋቁመው ከዚህ ደረጃ ያደረሱት ግለሰቦች በረከት፣ ስብሐት ነጋ፣ ዐባይ ጸሐይና ግልገል ወያኔዎችና እንደ ወያኔ የማሰብ በሽታ ከሸመቱ ግለሰቦች ምን ይጠበቅ ነበር? የኢትዮጵያን አንድነት አባቶችና ጠባቂዎች እንዲያወድሱ ነበር? ቀደም ሲል እንዳልሁት ታሪካችንን በጽሞና እንድንመረምር ዕድል የሰጡን ይመስለኛልና በበጐነት እንጠቀምበት።
ቀደም ሲል ስማቸውን ያነሣኋቸውን ጋሪባልዲንና ቢዝማርክን ለምክንያት ነበር የጠቀስሁአቸው። ጋሪባልዲ ኢጣልያንን ለማዋሐድ፣ ቢዝማርክ ተበታትና የቆየችውን ጀርመንን አሰባስቦ አንድ አገር (ኔሽን) ለማድረግ ሲወጡና ሲወርዱ የነበሩበት ሰዓት (በዘመነ ጓድነት) አንድ ነው። አፍሪካዊው መሪ (ጥቁር ሰው) ምኒልክ በተመሣሣይ ጥሪ በታሪክ መድረክ ላይ የታየውም በዚሁ የታሪክ ወቅት ነው። በዚህ ታሪካዊ ወቅት ምን ተፈጠረ? በዘመናት ውስጥ ተሸርሽራና ተበጣጥሳ የቆየችውን ኢትዮጵያ ዳር ድንበር አንድ አደረጉ። ሰበሰቡአቸው። በእነዚህ ተግባራት ብቻ ዓለም ካደነቃቸው ከነጋሪባልዲ ጋር ታሪክን ሊሻሙ የሚገባቸው ምኒልክ ዛሬ በወያኔና አንዳንድ አጫፋሪዎች ምን እየተባሉ ነው? አንዱና ጥሩ ውሸት መፍጠር ያልቻሉት ፀረ አንድነቶች የጡት ቆረጣ ወንጀል ነው። ይኸ ከየት የመጣ ነው? ለመሆኑ ወንጀሉስ የት ነው የተፈጠረው? ትክክለኛም ሆነ አልሆነ መልስ የመስጠቱን ዕዳ የሚሸከሙት ወያኔና ሁሉም ፀረ አንድነት የሚያቀነቅንበት ዜማ የሚጫወቱት ናቸው።
በሌላ በኩል ደግሞ የኦሮሞ ሴቶችን ጡት ስለማስቆረጥ የተፈጠረው አጉል ነጥብ ከአማራው (ማለትም ከክርስቲያን) ባሕልና እምነት ጋር ጨርሶ የሚሄድ አይደለም። በአንጻሩ ለጋብቻና ለመሳሰለው ዕድሜና እጆቹ እርፍ ለመጨበጥ የደረሰ ኦሮሞ ገበሬ ሚስት ሊያገባ የሚችለው አማራ በመስለብ መሆኑን እንኳ ለመስማት ፈልጌ አላውቅም። በእውነቱ ግን ወንጀሉ በየዘመኑ ለሚፈጠር ኦሮሞ ሁሉ እንዲቆየው አልሻም። በዚሁ ዓይነት አጤ ዮሐንስ ወሎንና ጐጃምን “ፈጅተውታል፣ አቃጥለውታል” በሚል የዛሬና የወደፊቱ ጐጃሜና ወሎየ ሁሉ ትግሬንና አጤ ዮሐንስን እንዲጠላ አላደፋፍርም። በውነቱ ደግሞ ዘወትር የምናወድሰው ታሪካችን አላስፈላጊና አሳፋሪ ጓዝም አለው። ቀደም ሲል ያነሳናቸው የኢጣልያንና የጀርመን የዛሬ ትውልዶች የየራሳቸው አንካሳ ታሪክ አላቸው። እኛ ላይ ሲደርስ ነው ከተደረገውና ከተፈጸመው ሁሉ በላይ የታሪክ ድሪቶና ቡትቶ ያየነው።
                        ኢትዮጵያዊነት አረጀ?
ኢትዮጵያን፣ ኢትዮጵያዊነትንና የዚችን አገር ቁሳዊና መንፈሳዊ ሀብታት፣ ዜግነትንና እሴትን የሚጸየፍ አንድ ምስኪን ልጅ በአልጀዚራ ሲናገር ብዙ ኢትዮጵያውያን ሰምተውታል። የጋናው ኒክሩማህ፣ የኬንያው ኬኒያታ የኮትዲቮሩ ሑፌትቧኘ፣ የማላዊው ካሙዙባንዳ…በጆርጅ ፓድሞን መሪነት..ወደ አንድ የለንደን የስብሰባ አዳራሽ (በ1953 እ.አ.አ) የገቡበት ሁኔታ ትዝ ይለኛል። አዳራሹ በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አሸብርቆአል። እነዚህ በኋላ የአፍሪካ ታላላቅ መሪዎች የሆኑ የዚያን ዘመን የነፃነት ታጋዮች አረንጓዴ፣ ብጫና ቀይ የሆነውን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ እያውለበለቡ ወደ አዳራሹ ሲገቡ የነበረበትን የክብር ሰልፍ ሳስብ በቦታው ለመገኘት እንደ ታደለ ሰው ዛሬ የልቤ ኩራት ወደር ያጣል! የጃንሆይ አጤ ኅይለሥላሴን ምስል በኮታቸው ክሳድ ላይ ያደረጉት እነ ንክሩማህ ሁኔታ ወለል ብሎ ይታየኛል። አዳራሹ በአእምሮዬ ይመጣል። ኢትዮጵያዊነትና “ኢትዮጵያዊ ነኝ” የዓለም ጭቁን ሕዝቦችና በተለይም የጥቁር ሕዝብ ኩራት እንደሆነ እነ ጃዋር ሰምተው ያውቃሉ? ለጥቁር ሕዝቦች ሁሉ “ኢትዮጵያ” ምን ትርጉም እንደምትሰጥ ለመሆኑ እነዚህ ይቺን አገር ካላፈራረስን እንሞታለን የሚሉ ሰዎች በመጠኑስ ቢሆን ያውቁ ኖሮአልን? “ኢትዮጵያዊነት” ከተራ ስያሜና ከአንድ ተራ አገር መጠሪያ በላይ መሆኑን ያውቁ ኖሮአልን?  ለእነዚህ ሕዝቦች ዞሮ መግቢያና መመኪያ …መንፈሳዊ ቤታቸውና ምስለ-ገነት የመሆንዋን ሐቅ ምን ያህል ሰምተዋል? የማርከስ ጋርቪን ፍልስፍና ያውቁታልን? ዛሬ ዛሬ ደግሞ እግዚአብሔር (ያህዌ ኤሎሒም) ለአዳምና ለሔዋን የፈጠረላቸው ገነት በአንደኛዋ የኢትዮጵያ ክፍል የመሆንዋ ግልጽነት አማራውን፣ ኦሮሞውን፣ ትግሬውን፣ ከምባታውን፣ ሐድያውን…ለሁሉም የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ አባላት ተጨማሪ ኩራት በሆነ ነበር። (ከላይ የነካካኋቸውን ነጥቦች በይበልጥ ለማወቅ ማርከስ ገርቪንና ዱቢድ ሜሬዲትን ያነብቡአል።) በነገራችን ላይ ማርከስ ገርቪና ራስ መኮንን ይባል የነበረው ጃሜይካዊ ጓደናው በጃንሆይ ቅሬታ ያደረባቸው እነሱ ካሰናዱአቸው 3ሺ ዓለም አቀፍ ተጋዳዮች ይልቅ በእንግሊዝ ጦር በመጠቀማቸው መሆኑ ይነገራል።
በኢትዮጵያዊነት ማፈር እንደ አልጀዚራው ጉብል ባሉ የሐቅ ማይማን እየተነገረ ነው። ያ ጉብል - ጃዋር ደግሞ በሌላ ጊዜ በመቅለስለስ መልክ “ እኔ በአባቴ ኦሮሞና ሙስሊም፣ በእናቴ አማራና ክርስቲያን ነኝ።” ሲል አድምጨዋለሁ። የልጅነት ተማሪዬ ሌንጮ ለታ የደረሰበትን አጉል አጋጣሚ ያስታውሰኛል። የኦነጉ መሪ ኢትዮጵያ ውስጥ እንደ ልብ ሲዘዋወር በነበረባቸው ወራት በጣም የተከበሩ አባቶች ወደ ነበሩበት ወደ ጅባትና ሜጫ ሄዶ ነበር። ያ አካባቢ እጅግ አስተዋይ የሆኑት ፊታውራሪ አባዶዮ ሠርገኛ ጤፍ አስመጥተው “ከዚህ መካከል ነጩንና ጥቁሩን ለይልኝ” ብለው ጥላቻንና ጠላትነትን ያወገሁበት አካባቢ ነው። ታዲያ ሌንጮ “አማሮች ያገኙን እንደእነዚህ እንስሳት ከብቶች አድርገውን ነው” ብሎ ሲጀምር “ልጆቻችንና ወንድሞቻችን..አንተ የምትላቸው አማሮች ናቸው። እኛም አማሮች፣ አማሮችም ኦሮሞዎች ናቸው።” ብለው በማስጠንቀቂያ ሸኝተውታል። የሮይተርን ቀጥታ ምስክርነት ለመጥራት እችላለሁ። ታዲያ ጃዋር እንደ ነገረን፣ ኦሮሞም ነው። አማራም ነው። ሙስሊምም ነው ክርስቲያንም ነው። ኢትዮጵያዊ ካልተባለ ምን ሊሆን ፈለገ? ቅጥ አምባሩ የጠፋበት አይደለም ትላላችሁ?
እነዚህን ሰዎች ሳስብ ኢሳይያስና መለስን አስባለሁ። የኦሮሞ ነፃነት ግንባር የሚለውን ድሪቶ የለጠፈባቸው ኢሳይያስ አፈወርቂ ነው። ወይም ኦነግን ጠፍጥፎ የሰራው እሱ ሲሆን “ኦሮሚያ” የሚለውን በታሪክም በተረትም የማይታወቅ የሕልም ዓለም ክልል ስያሜ ደግሞ በዳቦ ስምነት ያሸከማቸው አስመሮም ለገሰ የተባለው የእኛው ዩኒቨርሲቲ ውጤት ነው። በነገራችን ላይ የአስመሮም ለገሰ የገዳሥርዓት መጽሐፍ እስኪወጣ ድረስ ኦሮሚያ የሚባል ቃል አላውቅም ነበር። እንደ ነገሩ ደግሞ መጽሐፍ አገላባጭ ሰው ነኝ፥ እላለሁ።
የኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ-ይልቁንም መንግሥታዊው መድረክና አጀንዳ የፀረ አንድነቱ አቋም ማራገቢያ እንደ መሆኑ አገሪቱን ወደ ማፍረስ እየረሸጋገሩም ይመስላል። ለሱዳን፣ ለሳዑዲ፣ ለሕንድ፣ ለቻይና፣ ለፓኪስታንና ዶላር ላለው ሁሉ ተከፋፍሎ የተረፈውን ማለቴ ነው። ከዚህ መሠረትነት በመነሳት የሺህ ዘመናት ሥልጣኔ የነበረው የኦሮሚያ በአማሮች ተወርሮ “ኢትዮጵያ” የተፈጠረችው ከአንድ መቶ ዓመታት ወዲህ በዚያ መንግስት ፍራሽ ላይ ነው እየተባልን ነው። የዜጐች፣ የታሪክ ተመራማሪዎች ዝምታ ለተረትና ለቧልት መፈጠር፣ ለልብ ወለድ ታሪክ መፈብረክ አስተዋጽዖ አድርጐአል። ኦሮሞው ኅብረተሰብ (በብዙዎች አካባቢዎች- ለምሳሌ በወሎ ወዘተ ጋላ ማለት ስድብ ሳይሆን የተከበረና ትርጉሙም ትልቅ ማለት ነው) የዚህ አገር ታሪክ ተጋሪ፣ ፈጣሪና በግንባር ቀደምም እንደ አገሪቱ ዳር ድንበር ተከላካይና መከታ ሆኖ የቆየ ነው። አንዲት የምኒልክ ስንኝ በማስታወሻነት ከእናንተ ጋር ባቆይስ? እነሆ! 
“ጐበና ጐበና ጐበና የኔ
የጦር ንጉሥ አንተ ያገር ንጉሥ እኔ” አዳዲሱ ድርሳናቸው ከዚህ ሐቅ ጋር የሚጋጭባቸው ደራስያን “አዳዲስ ታሪክ የመጻፍን የአሸናፊዎች አንበሶችን ሚና” ይዘዋል። እኛም ማፈሪያዎች እነሱም ማፈሪያዎች ነን። ይህን እንቀበል!
                                     ስለ ጥቁሩ ሰው
 ወደ ሌላ ከመሻገሬ በፊት ከምኒልክ የተለያዩ ጠቅላይ ገዢዎች መካከል ዋነኞቹ (ሦስቱ) ስለ አገርና ስለ ምኒልክ የነበራቸውን ቁምነገሮች ለማንሳት እወድዳለሁ፤   
“ምኒልክ ትንሽዋን ወላይታ ወስዶ ትልቂቱ ኢትዮጵያን ሰጠኝ። በእውነት ምኒልክ የእኔም የኢትዮጵያም አባት ነው። - ካዎ ጦና ጋጋ - የመላው ወላይታ ርእሰ መሳፍንት ልጅ እያሱ ቀድሞ ኩምሳ ሞረዳ ይባሉ የነበሩትን የደጃች ገብረእግዚአብሔር ሞረዳን ልጅ ለማግባት ጥያቄ ሲያቀርቡላቸው - “ ምነው! ምነው ጌታዬ! እኔና እርስዎ ኮ ወንድማማች ነን። እኔ በመንፈስ ከአጤ ምኒልክ ተወልጃለሁ (አበልጅ) ስለዚህ እርስዎና እኔ ወንድማማች ነን። የእኔን ልጅ ሊያገቡ አይችሉም። ( አንዳንድ የወለጋ አረጋውያን በዚህ ላይ ሲጨምሩ ሰምቻለሁ። ተጨማሪው ቃል “ሲሆን ባል ሲመጣለት አባት ሆነው የሚለመኑ፣ ቆመው የሚድሩ መሆን ይገባዎታል”)
የደጃዝማች አባ ጅፋር አባ ጆብር (የከፋው ገዥ) ዘመድ የሆነ አንድ ሰው ዘወትር ይሹሙኝ እያለ ደጅ ይጠናቸው ነበር ይባላል። እንዲያውም አንድ ቀን እጅግ አምርሮ “ለመሆኑ እነዚህ ለሹመት ያበቁአቸው ሰዎች ከእኔ ይቀርቡዎታልን? ለእኔ አንድ የሹመት ቦታ አጥተው ነው?” ይላቸዋል።
  አባ ጅፋር በተለመደው ስል አነጋገራቸው “የሕዝብ አደራን በተመለከተ ምኒልክ እጄን ይዞ ነው የነገረኝ። ያ ባይሆን ኖሮ እኔ እዚህ አልገኝም ነበር። ምኒልክ እጁን ይዞ “ሹመት የሕዝብ ነው- ሹመት ሺህ ሞት ነው” ብሎናል። ወንድሜ! ወደ ሥልጣን የገቡት እንዴት በነፃነት እንውጣ እያሉ ይጨነቃሉ። ይህንን የማያውቁ ደግሞ እየዘለሉ መግባት ይመኛሉ። እንድታውቅልኝ የምመኘው ከዓለም መንግስታት እኩል ያደረገን ምኒልክ አደራ ከባድ መሆኑን ነው።”
በነገራችን ላይ አጤ ምኒልክ ዘወትር ምሳና ራት ሲበሉ አብረዋቸው ማዕድ የሚቀርቡ (ሁል ጊዜ) ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ፣ ደጃዝማች ወልደሚካኤል ጉዲሳ (የአጤ ኅይለሥላሴ አያት)፣ ፊታውራሪ ቱሉ፣ አፈ ንጉሥ በዳኔና ብላታ አቲከም ነበሩ።
 በአንድ ነጥብ እንለያይ። አጤ ምኒልክ በአንድነት አሰባሳቢነትና ተበታትና የቆየች አገራቸውን ወደ አንድ ኅብረት በማምጣት ረገድ የየአካባቢው መሪዎችን ትብብር በግድን በውድም ተቀዳጅተዋል። ስለዚህም በወለጋ ደጃዝማች  ገብረ እግዚአብሔር፣ በከፋ ደጃዝማች አባጅፋር፣ በወላይታ ካዎ ጦና ጋጋ አካባቢያቸውን ይዘው፣ የውስጥ አስተዳደራቸውን አደራጅተው ሕዝቡን ይመሩ ነበር። ይሁንና በአርሲ በኩል ለጊዜው ሕዝብ የሚቀበለው ጐላ ያለ ተወላጅ በመታጣቱ አጐታቸው ራስ ዳርጌ ተመደቡ። ራስ ዳርጌ ደግሞ እጅግ ሃይማኖተኛ፣ ሕዝቡን በርኅራኄ የሚመለከቱ የአባትነት ተቀባይነት የነበራቸው ስለሆኑ አንዳች ዓይነት ግፍ ለመፈጸም ባሕርያቸው የማይፈቅድላቸው ሰው ነበሩ። እንግዲህ “አጤ ምኒልክ ጡት አስቆረጡ” የሚባለው አነጋገር አርሲ ውስጥ መሆኑ ነው። ማንም እንደሚገምተው ጡት የመቁረጥ የአረመኔ ተግባር የአማራ ባሕርይም የክርስቲያን ሕዝብም ተግባር አይደለም። በአንጻሩ እነ አባ ባሕርይና ሌሎችም ሥፍር ቁጥር የሌላቸው የታሪክ ጸሐፊዎችም ለአካለ መጠን የደረሰ አንድ ኦሮሞ ጐልማሳ ከማግባቱ በፊት ብልት እስከ መስለብ፣ ጡት እስከ መቁረጥ የደረሰ “ጀብድ” መቁጠር መቻል አለበት፥ ይሉናል። ይኸም የትናንት ታሪክ ነው።
ለማንኛውም ተረት እየፈጠሩ ታሪክ፣ ድርሳን እየጻፉ በሕዝብ ዴሞክራሲ ስም ወደ ኋላ እየሄዱ የአገር ጊዜና ዕድሜ ከማባከን ይልቅ ጥላቻን ቀብረን፣ ፍቅርንና አንድነትን አንግበን ሰላም የተጠማችውን አገር ወደ ሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ማሸጋገር አይበጅም ኖሮአል? ዓለም እየታዘበን አይደለምን? ምን ይሁን ነው የምንለው?
 በሕብረተሰብ ትክክለኛ አመራር ባሕርይ መንጸባረቅ ያለበት አንድ ክስተት “የነገው ከዛሬው” የተሻለ፣ ብሩሕ፣ አሰባሳቢ፣ እኩልነት የዳበረበት፣ ነፃነት የከበረበት መሆን አለበት። ያለፈው ጓዝና ጉዝጓዝ እንደ ጸሐይ ማብራት የሚገባውን “ነገ”ን በጨለማማ ገጽታው ሊያደበዝዘው አይገባም። ከትናንትና ከዛሬው ይልቅ “በነገው” ተስፋና አለኝታ መጣል ይገባናል። እንዲያም ቢባል ከትናንቱ ብሔራዊ ውርስና ቅርስ -ከትናንቱ የእድገትና የአንድነት መሠረት መካከል- ምኑም ማናምኑም በዛሬና በነገው ቀጣይ ታሪካችን ውስጥ ሥፍራ ሊኖረው አይገባም አይባልም። ታሪካችንም ሆነ የነገው “ጸጋችን” ምንም ዓይነት ተቀባይነት አይኖረውም አይባል። አያቱንና አባቱን የማያውቅ ትውልድ በፈንታው ለነገው ትውልድ አባትነትና አያትነት አይሰማውም። አዎን የምንኰራባቸው አባቶችና እናቶች አያቶችና ቅም አያቶች ያሉንን ያህል አሳፋሪዎች፣ ፈሪዎችና ደካሞች፣ መልቲዎችና ሰነፎች የሆኑ ዜጐችም ነበሩብን። አሉብንም።
እነዚህን ማወቁ-ታሪካችንን ጠንቅቀን መረዳቱ፣ ጀግንነትን ለማደስና ከቶውንም ያንን አዳብረን የዓለም “ጨው” እስከምንባል ድረስ ለመጓዝ ዓለማቀፋዊነት መሠረት ይሆነናል። አፍሪካውያን ብቻ ሳይሆን፣ ጥቁር ዓለምንም ብቻ ሳይሆን- የዓለምን ነፃነት ወዳጅና አክባሪ ሕዝቦች ሁሉ የሚያደንቁት “ምኒልክ” ከዚች አገር የጐን አጥንት የተከፈለ ነው። አንድን አገር ታላቅና ገናና፣ የተከበረችና የታፈረች
የሚያደርጉአት ሕዝብዋ ሲሆኑ ለዚያ ሁሉ ታሪካዊ ሥፍራ ተቀዳጅነት የሚያስፈልጉ መሪዎች ናቸው። ኢትዮጵያ ውስጥ በመሪነት የተነሡትን ልዩ ልዩ ነገሥታትና የዛሬዎችንም አምላክ ለቅጣት የሰጠንን ጨምሮ- ለኢትዮጵያ አንዳች ክብር ያመጣውን ዋነኛ ሰው ለማግኘት ብዙ ማሰስ አስፈላጊ አይደለም። የዶክተር ሥርግው ሀብለ ሥላሴን “አጤ ምኒልክ” ማንበብ የአሰሳው ፍጻሜ ሊሆን ይችላል። ደራሲው በዚህ መጽሐፍ ከሳባ ንግስት አንስቶ እስከ ቀዳማዊ ኅይለሥላሴ ድረስ ይዘልቃል። ለዚህ አገር ታዋቂነት- ይልቁንም ዳር ድንበርዋንና ነፃነትዋን በማስከበር ረገድ ድንቅ አስተዋጽዖ ያደረጉ፣ በመንፈሳዊና ቁሳዊ ሥልጣኔ ታስደመሙ መሪዎችን ታሪክ ለላንቲካ ያቀርባል። ከሙሉው- ከዚያ ሁሉ ጀግናም ሆነ ሰነፍ መሪ መሐል አንድ ሰው ነጥሮ ይወጣል። በፀረ አንድነት ኅይልነት ጸንቶ ያለው ወያኔ ይንጨርጨር እንጂ- ወያኔና ሻዕቢያ የፈጠሩአቸው ትንንሽ ጩዋሒዎች ይንጨርጨሩ እንጂ ሰውዬው ወጣቱ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን “ጥቁሩ ሰው” የሚለው ነው።
ይቺ አገር በነፃነት የተፀነሱ፣ በነፃነት ያደጉና ድሀም ቢሆኑ በነፃነት የሚራመዱ ዜጐች እናት ናት። ያቺ አገርና ሕዝብዋ ከምን ጊዜውም በላይ ያልተጠናቀቀ ብሔራዊ ዕዳ፣ ለትውልዶች የሚጠቅም ቅርስ ለማቆየት በጥድፊያ ላይ ያሉ ወገኖች እናት ናት። እዚህ መሬት ማሕፀን ውስጥ የተከበሩ ጀግኖች ተኝተዋል። በዚች ዛሬ የታሪክ መጫወቻ በሆነች አገር ማኅፀን ውስጥ ታላላቅ ጀብዱ ፈፅመው ያንቀላፉ፣ በልዩ ልዩ ሙያና በፍልስፍናም ጭምር ልቀው ያላቁን ታላላቅ ነፍሳት የእናት አገራቸው እቅፍ ሞቆአቸው ተኝተዋል። ዓምደ ጽዮን፣ ያሬድ፣ በካፋ፣ ቴዎድሮስ፣ ዮሐንስ፣ ምኒልክ፣ ሀብተ ጊዮርጊስ፣ አሉላ፣ አብዲሳ አጋ፣ በላይ ዘለቀ፣…የተኙባትና እረፍት ላይ ስላሉም መሬቲቱ በጥንቃቄ መረገጥ ያለባት ናት። እነሱን ያህል ለመሥራት ያልቻልን ሰነፎች እንደ መሆናችን ቆምብለን ራሳችንን መርገምም የሚገባን ነን። ይኽ ሁሉ የወያኔ ልዑካን ጫጫታ አያሳፍርም? ይኸ ድምፅ ከየት መጣ? ወሮበሎች አያሰኝንምን? ስድ አደግ ማለት- የእምነት ድህነት ማለት- የሕሊና ባዶነት ማለት - የአቋም ምስኪንነት ማለት ምን ማለት ነው? ይኸው በአደባባይ እየታየ ነው። (በዚህ ጉዳይ ላይ እመለስበታለሁ)