Sunday, July 21, 2013

ብርቱ ሰው! (The Iron Man) (ከተመስገን ደሳለኝ)

ብርቱ ሰው! (The Iron Man) (ከተመስገን ደሳለኝ)  
ቅዳሜ  ከሰዓት በኋላ 
…አራት ኪሎ በሚገኝ አንድ ካፍቴሪያ ከጓደኞቼ ጋር የደራ ወግ በመያዜ፣ የእጅ ስልኬ የ‹‹መልስ ስጠኝ›› ጩኸቱን ደጋግሞ ሲያሰማ ልብ አላልኩትም፤ እናም ጮኾ ጮኾ ሲጨርስ፣ እንደገና ይጀምራል፡፡ ይኼኔ ጥሪውን እንዳላስተዋልኩ የተረዳው ጓደኛዬ ወደ ስልኩ ሲያመላክተኝ፣ ቁጥሩን አየሁት፤ አውቀዋለው፡፡ የእስክንድር ነጋ ባለቤት የጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል ነው፤ አነሳሁት፡፡
‹‹በጣም ይቅርታ! ከሰዎች ጋር ጨዋታ ላይ ሆኜ ነው ያልሰማሁት…››  
‹‹ለአስቸኳይ ጉዳይ ፈልጌህ ነበር፤ የት ነህ?›› 
‹‹ምነው? ምን ተፈጠረ?››
‹‹በስልክ አልነግርህም፤ መገናኘት አለብን››
‹‹እኔ አራት ኪሎ አካባቢ ነኝ›› 
‹‹ጥሩ! እኔም ፒያሳ ስለሆንኩ ‹ቲሩም ካፌ› እንገናኝ›› 
‹‹አሁኑኑ መጣሁ፡፡›› 
የሆነ ሆኖ የስልክ ንግግራችን ቢቋረጥም ድምጿ ከወትሮ የተለየ ስለሆነብኝ በእጅጉ ግራ ተጋባሁ፤ ምን አጋጠማት? እስክንድር ምን ሆነ? መቼም ኢህአዴግ ‹‹አስተዳድረዋለሁ›› የሚለውን ህዝብ ከፋሽስቱ ጣሊያንም በከፋ ጭካኔ እያሰቃዩ መደሰትን መገለጫው አድርጎታል፤ ታዲያ ዛሬ ደግሞ ምን ፍጠሪ እያላት ይሆን? ጥቂት ጥያቄዎች በውስጤ ቢመላለሱም፣ ጓደኞቼን በአጭሩ ተሰናብቼ በፍጥነት ‹‹ቲሩም ካፌ›› ደረስኩ፤ ቀድማኝ ስላገኘኋትም ወንበር ከመያዜ በፊት፡- 
‹‹እስክንድር ከነበረበት ዞን ተቀይሯል!›› ስትለኝ በደንብ አልሰማኋት ኖሮ ‹‹ወደ ዝዋይ ተቀየረ›› ያለች መስሎኝ ደነገጥኩ፤ በሁኔታዬም የተናገረችውን አለመረዳቴ ገባትና፡-
‹‹ወደ ሌላ ዞን ተቀይሯል›› ብላ ደገመችው፡፡ ኡፍ-ፍ… በእፎይታ ተንፍሼ ሳበቃም፣ ወንብር ከሳብኩ በኋላ ወዴት እንደተቀየረ ጠየኳት 
‹‹ወደ ዞን ሁለት›› 
‹‹ማን ነገረሽ?››
‹‹ዛሬ አግኝቼው ነበር፤ ‹በጣም ስለምፈልገው፣ ነገ ምንም ጉዳይ ቢኖረው ይሰርዝና ይዘሽው ነይ› ብሎኛል፤ ከባድ ጉዳይ ከሌለህ ሄደን እናግኘው›› አለችና መልሴን መጠበቅ ጀመረች፡፡ …ለጥቂት ደቀቃዎች ያህል በፀጥታ ከራሴ ጋር ተነጋገርኩ፡፡ ‹‹ከባድ ጉዳይ ከሌለህ…›› ያለችውን አስፈላጊ ስላልሆነ ችላ አልኩት፤ ምክንያቱም እስክንድር ነጋ ለምን እንደታሰረ እና ይህ ሁሉ መዓት ለምን እንደወረደበት ጠንቅቄ አውቃለው፤ ታዲያ! ነገ እርሱን ከማግኘት የከበደ ምን አይነት ጉዳይ ሊኖረኝ ይችላል? ያልገባኝ ነገር ግን የቃሊቲ ኃላፊዎች ከቤተሰቡ ውጪ ማንም እንዳይጠይቀው ከልክለውት እያለ እንዴት ብዬ ላገኘው እንድምችል ነው? ለደቂቃ ያህል በውስጤ ባስበውም መግቢያ ቀዳዳ አልታይህ ስላለኝ ይህ እንዴት ሊሳካ እንደሚችል እርሷኑ መልሼ ስጠይቃት፣ በፈገግታ ተሞልታ፡- 
‹‹ከነገ ጀምሮ ማንም ሰው እንዲጠይቀው ተፈቅዷል፤  ሆኖም ፍቃዱ ብዙ ላይቆይ ይችላል የሚል ጥርጣሬ ስላለው ሌላ ሰው ከመስማቱ በፊት መጀመሪያ አንተን ማግኘት ፈልጓል›› አለችና ምርጊት የሆነብኝን ስጋት ገፈፈችው፡፡ መሀል ፒያሳ ድንገት የወረደ-ታላቅ የምስራች!
…አቤት! ጀግናዬ! እንዴት ናፍቆኝ ነበር? ለመጨረሻ ጊዜ ያየሁት በህዳር ወር 2004 ዓ.ም ሲሆን፣ ያን ጊዜ ከታሰረ 45ኛ ቀኑ ነበር፡፡ ዛሬስ? በልቤ መቁጠር ጀመርኩ፤ ታህሳስ፣ ጥር፣ የካቲት… ድፍን አስራ ዘጠኝ ወር (አንድ ዓመት ከሰባት ወር) አልፎታል፡፡ …በመጨረሻም ከስርዓቱ ተለዋዋጭ ባህሪ አኳያ በ‹‹አማኝነት›› እና በ‹‹መናፍቅነት›› መሀል ብዋልልም፣ ጠዋት ሁለት ሰዓት ቃሊቲ እንድንገናኝ ተቀጣጥረን ተለያየን፡፡      
   በቀጥታ ወደ ‹‹አሲምባ›› (መኖሪያ ቤቴ) አመራሁ፡፡ 
ከአንድ ቀን በፊት ደብረዘይት ሄደው የነበሩት ባልደረቦቼ ሙሉነህና ዳዊት በፍጥነት ወደ ‹‹አሲምባ›› እንዲመጡ በስልክ ነገሬያቸው ሳበቃ አልጋዬ ላይ ጋደም ብዬ ነገን መናፈቅ ጀመርኩ፡፡ ኦ! እንዴት አይነት ግሩም ቀን ነው! ብቻዬን አወራለሁ፤ እስቃለሁ፡፡ እስክንድር ሆይ! በአይነ ስጋ ልንተያይ የሰዓታት ዕድሜ ብቻ ቀርቶናል!! 
     …በኢትዮጵያ ምድር፣ በኢህአዴግ መንግስት ‹‹ሃሳብን በነፃ የመግለፅ መብት›› እንዲከበር እና ስርዓቱ ከጠመንጃ ማምለክ ህግን ወደ ማክበር ይመጣ ዘንድ የከፈለው መስዕዋትነት በአንድ መጣጥፍ ተዘርዝሮ እንደማያልቅ ለውጥ ፈላጊው ወገን ብቻ ሳይሆን፣  እንደ‹‹ክፉ እንጀራ አባት›› ከስር-ስሩ እየተከተሉ በሾኬ የሚጥሉት እነበረከት ስምዖንም ያውቃሉ፡፡ በፍርድ ቤት የአስራ ስምንት ዓመት እስር የተወሰነበትም ለ‹‹ጥፋተኝነቱ›› ማስረጃ ተግኝቶበት እንዳልሆነም ጨምረው ያውቃሉ፡፡ ሀገሬውም ያውቃል፡፡ እኔም አውቃለሁ፤ ወዳጄ እስክንድር ንፁህ ነው፤ በተለይም ‹‹በህቡዕ ህገ-ወጥ ድርጅት መስርቶ ፀረ ህገ-መንግስት እንቅስቃሴ ሊያደርግ ሲል  ደረስንበት›› ያሉት ውንጀላ ፍፁም ሀሰት ለመሆኑ በነፍሴም በስጋዬም እምላለሁ፤ ዘመኔን ሙሉ እንዲህ አይነት ነጭ ውሸት ሰምቼ አላውቅም፡፡ ምክንያቴን በአዲስ መስመር ልንገራችሁ፡፡
     (ታሪኩ የሚጀምረው ግንቦት 22/2003 ዓ.ም ከቀኑ አምስት ሰዓት አካባቢ ስልክ ደውሎ የት እንዳለው ጠይቆኝ፣ በአስር ደቂቃ ውስጥ ተገናኘተን ለምን እንደፈለገኝ ካስረዳኝ በኋላ ነው፤ እናም በዕለቱ የተነጋገርነውን  እንደወረደ ላስቀምጠው) 
‹‹ምን ታስባለህ?››
‹‹ስለምኑ?››
‹‹ስለአጠቃላይ ሁኔታው››
‹‹እስኬ! አልገባኝም?››
‹‹ከዚህ በኋላም ዝም ብለን እየፃፍን ነው መቀጠል ያለብን ብለህ ታስባለህ?››
‹‹ታዲያ! ሌላ ምን አማራጭ አለን?›› በአግራሞት ጠየኩት፡፡ ያሰበውን ዘርዝሮ ነገረኝ፡፡ …ለየትኛውም የፖለቲካ ፓርቲ የማይወግን የ‹ሲቪክ ማህበር› መስርተን ህዝቡ መብቱን እንዲጠይቅ ከመቀሰቀስ ጀምሮ ፓርላማው ህጋዊ ስላልሆነ ፈርሶ በአስቸኳይ (ሁሉንም የፖለቲካ ድርጅቶች በዲሞክራሲያዊ መንገድ የሚያሳትፍ) አዲስ ምርጫ እንዲደረግ የአደባባይ ስብሰባና ሰልፍ ማዘጋጀትና የመሳሰሉትን እንቅስቃሴ መፍጠር እንደሚቻል ጆሮ-ገብ በሆነ ድምፁ አብራራልኝ፡፡ በተመስጦ አዳመጥኩት፡፡ እፁብ ድንቅ አሳብ!  
   በመጨረሻም በተግባራዊው እንቅስቃሴ ላይ ከተነጋገርን በኋላ፣ ኢህአዴግ ለውንጀላው ክፍተት እንዳያገኝ እያንዳንዷን ድርጊት በህጋዊ መንገድ ብቻ እንዲሆን ጥንቃቄ ማድረግን ጨምሮ ስራችንን ለመጀመር የሚያስፈልገውን ገንዘብ ከሀገር ውስጥም ሆነ ውጪ ካሉ ኢትዮጵያውያን ሳንጠይቅ በጋራ ለመሸፈን ተስማምተን፣ መስራች አባል የሚሆኑትን ስድስት ሰዎች የማሰባሰቡ ስራ የእኔ ሆኖ (ይህንን ሰበብ አድረገው ፍትህ ጋዜጣን ሊነጥቁን ስለሚችሉ እኔ በቀጥታ የቡድኑ አባል እንዳልሆን ያቀረበውን ስጋት ተቀብዬ) ከአራት ቀን በኋላ ምስረታው እውን መሆን እንዳለበት ወስነን ተለያየን፡፡ 
   በቀጠሮው ቀን እስክንድርና ስድስቱ ወጣቶች ተገናኝተው ስለጉዳዩ በስፋት አብራርቶላቸው፤ በሃሳቡ ከተስማሙ በኋላ እስክንድርን ሰብሳቢ፣ የጋዜጣችንን ምክትል አዘጋጅ ሙሉነህ አያሌውን ም/ሰብሳቢ፣ ሪፖርተራችንን ዳዊት ታደሰን ፀሀፊ አድርገው መርጠው፣ በቃለ- ጉባኤው ላይ ፈርመው ቀጠሮ ይዘው ተለያዩ (በተሰበሰቡ ቁጥር በሁለት ኮፒ ቃለ-ጉባኤ ይያዛል፣ አንዱ እስክንድር ጋ፣ አንዱ እኔ ጋ
ይቀመጣል) ደግመው ተገናኙ፤ ሰለሱ…፡፡ ከዚህ በኋላ እቅዱን የተመለከተ ዝርዝር መግለጫ በጋዜጣችን ላይ የሚወጣበት ቀን ተወሰነ፡፡ ሆኖም መግለጫው አርብ ከመውጣቱ በፊት ረቡዕ እስክንድር ‹‹የግንቦት ሰባት አባል እና የህዕቡ ድርጅት መስርተሃል›› በሚሉ ክሶች ከደረዘን በሚልቁ የፌደራል ፖሊስ አባላት ተከቦ ተያዘና ማዕከላዊ ምርመራ ጣቢያ ታሰረ፡፡ መርማሪ ፖሊሶቹም የእምነት-ክህደት ቃሉን ሲጠይቁት ህጋዊ የ‹‹ሲቪክ ማህበር›› ከስድስት ወጣቶች ጋር በመመስረት ላይ መሆኑን አስረድቶ ሲያበቃ የግንቦት ሰባት አባልም ተባባሪም አለመሆኑን አፅንኦቶ ሰጥቶ ተናገረ፡፡ ምርመራውም ተጠናቆ ክሱ በፍርድ ቤት መታየት ሲጀምር ሙሉነህና ዳዊት በመከላከያ ምስክርነት ቀርበው ማህበሩን አብረው እንደመሰረቱ፣ ሃሳቡ የእስክንድር ብቻ ሳይሆን የእነርሱም መሆኑን ህዝብ በታደመበት ችሎት መሰከሩ፤ ግና! ለ‹‹ካንጋሮ ፍርድ ቤት›› ከዕውነታው ይልቅ የእነበረከት ስምዖን ድራማ ይበልጣልና ሀቁን ሊቀበል አልወደደም፡፡ …በቃ! እውነታውም የንፅህና ማረጋገጫውም ይህ ነው፤ ሌላ አይደለም (አሁን ወደ ርዕሰ-ጉዳያችን እንመለስ)   
መንግዶች ሁሉ ወደ ቃሊቲ …   
     እሁድ ጠዋት
     ከጋዜጠኛ ሰርካለም ቀድመን በመድረሳችን እንደ ሊማሊሞ ዳገት ጠመዝማዛና ረጅም የሆነውን የእስረኛ ጠያቂዎች ሰለፍ ተቀላቅልን ተራችንን መጠበቅ ጀመርን፤ ከድፍን ሀምሳ አምስት ደቂቃ ጥበቃ በኋላ ተራችን በመድረሱ አሰልቺውን ፍተሻ አልፈን ወደ ውስጥ ገባን፤ ስለፍትህ የሚጮኸው ሰው ወደ ተጣለበት-‹‹ዞን ሁለት›› 
     ‹‹እስክንድርን አየዋለሁ›› ብዬ እርግጠኛ ስላልሆንኩ፣ ሙሌ ወደ ዲጄው (ጠያቂዎች የሚፈልጉትን እስረኛ ስም ሲነግሩት በማይክራፎን የሚጠራ ታሳሪ ነው) ተጠግቶ ‹‹እስክንድር ነጋን›› ሲለው በስጋት ነበር የማስተውለው፤ ይኹንና ዲጄው የተነገረውን ተቀብሎ ‹‹እስክንድር ነጋ፣ እስክንድር ነጋ….›› እያለ ሲጮኽ ድንገተኛ ደስታ አጥለቀለቀኝ፤ ኦ አምላኬ! ምኞቴ እውን ይሆን ዘንድ እርዳኝ! …በስሜት ተሞልተን እስረኞች በሚወጡበት በር ላይ ለበርካታ ደቂቃዎች አፈጠጠን፤ ሆኖም ጥቂት ታሳሪዎች ተከታትለው ከመምጣታቸው በቀር እስክንድር የለም፤ ዝምታ በተጫነው ገፅታ እርስ በእርስ ተያየን፤ ኩም-ኩምሽሽ ልንል ይሆን? …የዲጄው ድምፅ ‹‹ታምራት ገለታ፣ ታምራት ገለታ…›› ብሎ ያሰመጠንን የስጋት ፀጥታ አደፈረሰው፤ ይህን ስም አውቀዋለሁ፤ አንድ ሰሞን ከዜናነትም አልፎ፣ የመፅሄቶች እና የጋዜጦች ዋነኛ ማሻሻጫ ሆኖ እንደ ነበር አስታውሳለሁ፤ የጥሪው ድምፅ አየር ላይ ናኝቶ አፍታም ሳይቆይ ‹‹እያንገዋለለ/ አባባ ታምራት›› ውሃ ሰማያዊ ቀለም ያለው ሙሉ ልብስ በጥቁር ከረባት ለብሶ፣ አይኑ ላይ ጥቁር መነፅር ሰክቶ በፈገግታ ወደ ሚመለከቱት ሶስት ወጣት ሴቶች ወደ ቆሙበት አቅጣጫ ሲሄድ አየሁት፤ ሶስቱም ብስል ቀይ ናቸው፡፡ የሰውየው አለባበስ የእስረኛ አይመስልም፤ ምናልባት ተከታዮቹ ሊጠይቁት ሲመጡ ‹‹ዛሬም አምላክ ነኝ-አርጋለሁ፣ እበራለሁ›› ብሎ እያጭበረበረ ሊሆን ይችላል፡፡ …እስክንድር ግን አሁንም አልመጣም፡፡ ለዲጄው ነገርኩት፤ በተሰላቸ ድምፅ፡-
‹‹ጠብቀው ይመጣል›› አለኝ፤
‹‹ከእርሱ በኋላ የተጠሩ እስረኞች እየመጡ ነው›› መለስኩለት፤ በፀበኛ አስተያየት ገረመመኝና ‹‹እስክንድር ነጋ፣ እስክንድር ነጋ…›› ሲል አምባረቀ፤ ሰከንዶች አለፉ፡፡ አንድ ደቂቃ፣ ሁለት ደቂቃ… ሰዓታት ያለፉ ቢመስለኝም፣ አይኖቼን ከእስረኛ መውጫው ላይ አልነቀልኩም፤ ሸምገል ያሉ አንድ እስረኛ መጡ፤ ከኋላቸው ደግሞ ሌላ ሰው ተከትሏል፤ አየሁት፤ እርሱ ራሱ ነው፤ ልቤ በደስታ ወከክ ሲል ይታወቀኛል፡፡ አይን-ለአይን ተያየን፤ ደግሜ አየሁት፤ አላመንኩም፡፡ አዎን! ራሱ እስክንድር ነጋ ነው፡፡ ባርኔጣውን አጥልቋል፤ ፊቱ በማራኪ ፈገግታ ተሞልቷል፤    እርሱም በጣም የተደሰተ ይመስላል (ለነገሩ እንዴት አይደሰት! ከአስራ ሰባት ወራት በኋላ ከቤተሰቡ ውጪ ለመጀመሪያ ጊዜ ከጠያቂዎች ጋር ሲገናኝ!) አጠገባችን እስኪደርስ አፍጥጬ ተመለከትኩት፤ በጭራሽ እስር ቤት የቆየ አይመስልም፤ አብሬው በዋልኩባቸው ጊዜያት ሁሉ ከራሱ አልፎ በእኔም ላይ ይጋባ የነበረው ያ ጠንካራ መንፈሱ ዛሬም አብሮት አለ-ክቡድ መንፈስ፡፡ ‹‹ብሶት የወለደው›› ገዥው ፓርቲ ለሃያ ዓመታት የመከራ ናዳ ቢያወርድበትም-አልተበገረም፡፡ ይህ ሰው መቼም የሚሸነፍ፤ መቼም እጅ የሚሰጥ፤ መቼም የሚከሽፍ አይመስለኝም፡፡ የእስር ቤት ኑሮም የትግል ፍላጎቱን ይበልጥ ኃያል አድርጎታል፡፡ ብርቱው-ሰው  (The Iron Man) እስክንድር ነጋ፡፡ 
    የሆነ ሆኖ መሀላችን ያለው የሽቦ አጥር የፈቀደልንን ያህል እጅ-ለእጅ ተነካክተን ሰላምታ ተለዋወጥን (ናፈቆትን የማያረካ-ሰቀቀን) እና ያሰብኩትን ያህል ባይሆንም ለተወሰኑ ደቂቃዎች አውርተን ስናበቃ ለምን እንደፈለገኝ ነገረኝ፡፡ 
‹‹ትግሉ መቆም የለበትም፤ እጅ አንሰጥም፤ አሁን የምነግርህን በሙሉ በአእምሮህ እንድትይዘው እፈልጋለሁ›› 
‹‹ግዴለም፤ ንገረኝ ለሶስት ተረዳድተን እናስታውሰዋለን››
‹‹በጣም ጥሩ! መልዕክቱን ራስ ከፃፍከው በኋላ ለአሜሪካ ፕሬዘዳንት ባራክ ኦባማ እንዲደርስ እና በመረጥከው ሚዲያ ላይ እንዲታተም አድርገው›› አለና ከሸሚዝ ኪሱ የተጣጠፈ ወረቀት አወጥቶ ከዚህ በታች የምታነቡትን መልዕክት ያለ ማስታወሻ ደብተር እንድይዘው አብራራልኝ፤ (በድጋሚ ወደ ቃሊቲ አምርቼ፣ መልዕክቱን በትክክል መረዳቴን አረጋግጫለሁ)   
        ግልፅ ደብዳቤ ለኦባማ አስተዳደር!
      ሁላችንም እንደምናውቀው በሀያኛው ክፍለ ዘመን የመጨረሻ  ዓስርታት በተለያዩ ክፍለ አህጉራት ውስጥ ባሉ ታዳጊ ሀገር ህዝቦች የተነሱ የፖለቲካ እና የዲሞክራሲ ጥያቄዎች በቀዳሚነት በጠመንጃ ኃይል የተደገፉ ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያም በተመሳሳይ የታሪክ ክስተት ማለፏን የሚመሰክረው ዛሬም ወታደራዊ ስርዓቱን ብቻ ሳይሆን፣ ይህንን መንገድ የመረጡትን ጥቂት  የተቃዋሚ ድርጅቶችንም በጦር ኃይል ድል አድርጎ ስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ መሆኑ ነው፡፡ ይሁንና የቀዝቃዛው ዓለም ጦርነት ማብቃትና የአሜሪካ ብቸኛ ልዕለ ሀያል ሀገር ሆኖ መውጣት በኃይል የሚደረጉ ‹‹ፀረ-አምባገነን›› ንቅናቄዎች ሰላማዊውን መንገድ ብቻ እንዲከተሉ ሁኔታዎችን አመቻችቷል፡፡ የለውጡም ዋነኛ መግፍኤ አሜሪካ ለሰላማዊ ትግል የምትሰጠው ከፍ ያለ ቦታ ብቻ ሳይሆን የምታደርገው እገዛም መሆኑ አከራካሪ አይደለም፡፡ በእርግጥ የአሜሪካ አስተዳደር በሰላማዊ ትግል ላይ ያለው አቋምና ለትግሉ የሚያደርገው ቀጥተኛ አበረታችነት የሀገሪቱ መስራች አባቶች ካነፁት የሞራል እና የፖለቲካ እሴት እንደሚነሳም አውቃለሁ፡፡
       በኢትዮጵያ የ1983 ዓ.ምን የመንግስት ለውጥ ተከትሎ የተስተዋለው ‹‹ሰላማዊ የትግል አማራጭ›› እምነት አውድም ከዚሁ የአሜሪካ መንግስት አቋም ጋር የተዛመደ ሲሆን፣ ባለፉት ሀያ ሁለት ዓመታትም በሀገራችን ዓላማቸውን በሰላማዊ ትግል ያራመዱ ወገኖች በሙሉ በዚህ ከመሰረታዊ የነፃነተ እሴቶች የሚነሳውን የአሜሪካንን ድጋፍ እውነተኝነት በፍፁም ልብ በመቀበል መሆኑ አይሳትም፡፡ ነገር ግን በዚህ እምነት ተቀኝተው የትግሉን አማራጭ ለመከወን ሲታትሩ እጅግ ከፍተኛ የሆነ ስቃይ እንደደረሰባቸው ለማወቅ ‹‹ስቴት ዲፓርትመንት›› በየዓመቱ የሚያወጣውን ሪፖርት መመልከት ብቻ በቂ ነው፡፡ እናም ሞት፣ እስር፣ ስደት እና ሌሎች መከራዎች በትግሉ አራማጆች ላይ የደረሰ (እየደረሰ) መሆኑ ለአሜሪካን የተደበቀ ጉዳይ አይደለም፡፡
     ይኽም ሆኖ በግሌ የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አስተዳደር ‹‹ካለ ዲሞክራሲ ዕርዳታ የለም!›› የሚለውን መሰረታዊ የውጪ ጉዳይ መርሁን ለማስከበር አሁንም ቢሆን ጊዜው አልረፈደበትም የሚል እምነት ስላለኝ፣ ኢህአዴግ ለህግ የበላይነት ተገዢ እንዲሆን ከሀገሪቱ ነባራዊ የፖለቲካ ሁኔታም ሆነ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ካለው አጠቃላይ ግንኙነት አንፃር፣ አሜሪካ የሚከተሉትን ተፅእኖ መፍጠሪያ አማራጮች ብትከተል በሀገር ውስጥ እየተካሄደ ያለውን የነፃነት እንቅስቃሴ በእጅጉ ይጠቅማል ብዬ አስባለሁ፡፡ 
                1. የኢኮኖሚ ማዕቀብ 
    አሜሪካ በየዓመቱ የምታደርገውን ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ ደረጃ በደረጃ የሚቀንስ ኢኮኖሚያዊ ማዕቀብ ብትተገብር ኢህአዴግ ህግ አክባሪ እንዲሆን የሚገደድበትን ሁኔቴ ማመቻቸት ትችላለች ብዬ አምናለሁ፡፡ ሆኖም ማዕቀቡ ዋነኛ ግቡ ማድረግ የሚኖርበት ስርዓቱ ለአፈና የሚጠቀምባቸውን (ምንም አይነት የኢኮኖሚ ፋይዳ የሌላቸውን) ተቋማትና መንገዶች መሆን ይኖርበታል፡፡                                
                   2. የበረራ ማዕቀብ /Flight Embargo/ 
   በሁለተኛነት መተግበር ያለበት ማዕቀብ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ከሀገር ሀገር የመዘዋወር መብትን የሚያግድ ቢሆን አስፈላጊውን ውጤት ያመጣል፡፡ ይህ የበረራ እግድ የተወሰኑ የስርዓቱ ቀዳሚ ባለስልጣናትን ብቻ የሚመለከት መሆን ይኖርበታል፡፡ 
                    3. የሰብዓዊ ዕርዳታ /Humanitarian Aid/   
ሁለቱ ማዕቀቦች ሲጠነክሩ ሀገሪቱ ለኢትዮጵያ የምትሰጠውን ሰብዓዊ ዕርዳታዎችን /Humanitarian Aid/ ማቋረጥ አይኖርባትም፡፡ ምክንያቱም የዚህ አይነቱ የዕርዳታ መስተጓጎል ዜጎችን ለከፋ ስቃይ ሊዳርግ የሚችልበት ዕድል ሰፊ ነውና፡፡ 
     ዩናይትድ ስቴት ኦፍ አሜሪካ እነዚህን ማዕቀቦች በኢህአዴግ አስተዳደር ላይ ከጣለች፣ በኢትዮጵያ ውስጥ እየተደረገ ያለውን ሁሉን አቀፍ የዲሞክራሲ መብቶችን የማስከበር ትግል በከፍተኛ ሁኔታ ታግዛለች፡፡ ይህን ማድረግ ደግሞ ሀገሪቷ ከቆመችበት ስለሰው ልጆች ነፃነት የመቆርቆር የሞራል ኃላፊነት ጋር በጥብቅ ይተሳሰራል፡፡ 
     የማዕቀቦቹ መተግበር ለኢትዮጵያ አምስት ዋና ዋና ጥቅሞችን ያስገኛል፡፡ 
                   1. የሰላማዊ ትግል ተዓማኒነትን ያጠናክራል
  በኢትዮጵያ ውስጥ እየተሞከረ ያለው ሰላማዊ ትግል የተሻለ አማራጭ እንደሆነ የትግሉ አራማጆችና ደጋፊዎች እንዲያምኑ ያደርጋቸዋል፡፡ 
                     2. ለለዘብተኞቹ
     ይህ አይነቱ ጫና ከሚፈጥራቸው አዎንታዊ ለውጦች አንዱ በኢህአዴግ ውስጥ ያሉ ለዘብተኛ የአመራር አባላት እና ካድሬዎች ለበለጠ የፖለቲካ መብቶች መከበርና የተሻለ ስርዓታዊ ክፍትነትን ለማበረታታት ያላቸውን ተነሳሽነት እንዲያጠናክሩ ማድረግ ማስቻሉ ነው፡፡
 
                     3. ለአክራሪዎቹ
    በድህረ-መለስ ኢህአዴግ ውስጥ ለዘብተኛ እና እጅጉን ፅንፈኛ ኃይሎች እንዳሉ ተስተውሏል፡፡የዚህ ማዕቀብ ተፅዕኖም ፅንፈኞቹ የስርዓቱ ባለስልጣናት ከሚያቀነቅኑት ኢ-ዲሞክራሲያዊ አካሄድና የጥላቻ ፖለቲካ እንዲታቀቡ አድርጎ ፖለቲካዊ መቻቻልን እንዲቀበሉ ያስገድዳቸዋል፡፡   
                     4. ለሲቪክ ማህበራት እና ጋዜጠኞች
     በሰላማዊው መንገድ በነፃነት እንቅስቃሴው ውስጥ በጉልህ ሲሳተፉ የነበሩትን እና እየተሳተፉ ያሉትን ጋዜጠኞች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችና ሲቪክ ማህበራት እየከፈሉ ያለው መስዕዋትነት ከፍ ያለ ዋጋ እንዳለው ከማረጋገጡም በላይ የተሻለች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ብቸኛው መንገድ ሰላማዊና ህገ-መንግስታዊ የትግል አማራጭ እንደሆነ እንዲያምኑና ትግላቸው ውጤት ሊያመጣ እንደሚችል እርግጠኛ ሆነው በመንገዳቸው እንዲፀኑ ያደርጋቸዋል፡፡
                     5. ለአሜሪካ መንግስት
     የአሜሪካ መንግስት እነዚህን ሀገራዊ ጠቀሜታ ያላቸውን እርምጃዎች መውሰዱ፣ ለኢትዮጵያውያን አሜሪካ ያለባትን የሞራል ኃላፊነት እየተወጣች መሆኑን ከማሳመን በዘለለ የገባችውን ቃል በመተግበር በሰላማዊ መንገድ አላማቸውን ሲያራመዱ ለስርዓቱ ጥቃት የተጋለጡ ፖለቲከኞች እና የመብት ተሟጋቾችን መታደግ አስችሎ፣ ከታሪክ ተጠያቂነት ዕዳ  ነፃ ያወጣታል፡፡
       በጥቅሉ እነዚህ ተመጋጋቢ ሂደቶች ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት የሚደረገውን ትግል በማፋጠን ሰብዓዊና ፖለቲካዊ መብቶች የተከበሩባት ሀገር ለመፍጠር ከፍተኛ ድርሻ እንደሚኖራቸው የማይናወፅ እምነት አለኝ፡፡
                                                             እስክንድር ነጋ / ከቃሊቲ እስር ቤት /                      
                                                                                              ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር !   

No comments:

Post a Comment