Saturday, January 25, 2014

አቡጊዳ – የአራና አመራር አባላት በሕወሃት ካድሬዎች በአዲግራት ተደበደቡ

ወጣት አብርሃ ደሳትን ጨምሮ በርካታ የአራና አመራር አባላት በሕወሃት ካድሬዎችን በአዲግራት እንደተደበደቡ በስፋት ኡእይተዘገበ ነዉ። አራና፣ አዲግራት በሚያደርጋቸው ስብሰባ ሕዝቡ እንዲሳተፍ በከተማዋ እየተዘዋወሩ ሲቀሰቀሱ ነዉ ተይዘው የተደበደቡት። ከአቶ አብርሃ በተጨማሪ፣ አቶ አሰግዴ ገብረስላሴ፣ አቶ አምዶም ገብረስላሴ ይገኙበታል። የተደበደቡት የአመራር አባላት ፣ ወደ ፖሊስ ተወስደዉ ፣ ለአራት ሰዓታት ታስረዉ፣ ስብሰባዉን እንዲሰርዙ ማስጠንቀቂያ ተሰቷቸው ተመልሰዋል። የደረሰባቸው ድብደባ በጣም የከፋ በመሆኑ አቶ አምዶም እና አስቶ አሰገዴ ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል።
የአዲግራትን ስብሰባ በተመለከተ፣ ከመደብደቡ በፊት በአብርሃ ደስታ የቀረበዉን ጽሁፍ እንደሚከተለው አቅርበናል ፡
የዓረና-ዓጋመ የእሁድ ስብሰባ – አብርሃ ደስታ
=====================
ዓረና መድረክ ከዓጋመ (ዓዲግራት) ህዝብ ጋር በፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ለመወያየት ለእሁድ ጥር 18, 2006 ዓም በዓዲግራት ህዝባዊ አዳራሽ (ከጠዋቱ 2:30 ጀምሮ) ቀጠሮ መያዙ ይታወቃል። ዓረና ፓርቲ ለተሰብሳቢው ህዝብ አማራጭ ፖሊሲው ያስተዋውቃል፣ ፖለቲካዊ ትምህርት ይሰጣል፣ ያደራጃል፣ መረጃ ይለዋወጣል። የዓረና ዋነኛ ዓላማ ህዝብ ከጭቆናና ባርነት ለማላቀቅ ማስተማር ነው።
ህዝብ ካሁኖቹ ጨቋኞች እንዲሁም ለወደፊቱ ሊመጡ ከሚችሉ ጨቋኞች ነፃ እንዲወጣ ለማድረግ ፖለቲካ (ስለ መብትና ነፃነት) እናስተምራለን። ምክንያቱም አንድ ህዝብ (ወይም ብዙ ህዝቦች) ከጭቆና ለማላቀቅ ህዝብ መሳርያ ማስታጠቅ አለብን። የፀረ ጭቆና ሚሳኤል ፖለቲካዊ ትምህርት ነው። የፖለቲካ ትምህርት በመስጠት የህዝብ የፖለቲካ ንቃተህሊናው ከፍ እንዲል ማድረግ ይቻላል። ህዝብ የፖለቲካ ንቃተህሊናው ካዳበረ ለማንም ጨቋኝ ስርዓት አሜን ብሎ አይገዛም። መብቱ ማስከበር ይችላል። ነፃነቱን አሳልፎ አይሰጥም። ስለዚህ ፖለቲካዊ ትምህርት ፀረ ጭቆና ሚሳኤል ነው። ህዝብ ራሱ ከጨቋኞች ነፃ ለማውጣትና ለመከላከል ከፈለገ (አንድ) ፖለቲካ ማወቅ አለበት፣ (ሁለት) መደራጀት አለበት። ወደ ዓዲግራትና ሌሎች አከባቢዎች የምንቀሳቀሰውም ይህንን ፀረ ጭቆና ሚሳኤል ለማስታጠቅና ለማደራጀት ነው።
ህወሓቶች ግን ይህን ዓላማ እንዳይሳካ ጥረት ማድረጋቸው አይቀርም። ምክንያቱም ህዝብ ፀረ ጭቆና ሚሳኤል ከታጠቀ ለህወሓቶች አሜን ብሎ የሚገዛ አይሆንም። መብቱ ይጠይቃል፤ ነፃነቱ ይፈልጋል። ስለዚህ ህወሓቶች ህዝብ ይህንን ፀረ ጭቆና ሚሳኤል እንዲታጠቅ አይፈልጉም። በዚህ መሰረት ህዝብ ዓረና በጠራው የህዝብ ስብሰባ እንዳይሳተፍ የተለያዩ ዕንቅፋቶች መፍጠራቸው አይቀርም። ህዝቡ በስብሰባ እንዳይሳተፍ ማስፈራራታቸው አይቀርም። ምክንያቱም ህወሓቶች የህዝብን ማወቅ ያስፈራቸዋል። ምክንያቱም የህዝብ ማወቅ ለስልጣናቸው ስጋት ነው። ህዝብ አሜን ብሎ የሚገዛ እስካላወቀ ድረስ ብቻ ነው። ስለዚህ የህወሓቶች ስትራተጂ ህዝብ ወደ ስብሰባው እንዳይገባና እንዳያውቅ መከልከል ነው የሚሆነው።
የህወሓቶች ዕንቅፋት ሳይበግረን እንገባበታለን። ምክንያቱም የህዝብን የማሳወቅ ዓላማ አንግበናል። የኛ ዓላማ ህዝብ ስለ ፖለቲካዊ መብቱ ግንዛቤ ኖረት የራሱ ዕድል በራሱ እንዲወስን ማስቻል ነው። ለዚሁ ዓላማ ሟቾች ነን። ህወሓቶችም ለስልጣናቸው ሟቾች ናቸው። የህወሓት ሃይማኖት ስልጣን ነው። ስለዚህ ህወሓት ለስልጣኑ መስዋእት ይከፍላል። ለስልጣኑ ይሞታል። እኛም ለዓላማችን እንሞታለን። ሁለታችን ለተለያየ ዓላማ እንሞታለን፤ እንፎካከራለን። በመጨረሻም ሁላችን ፖለቲከኞች ሞተን የመጨረሻ ድሉ የህዝብ ይሆናል። ህዝብ ያሸንፋል።

No comments:

Post a Comment