Wednesday, November 12, 2014

ኢትዮጵያ፡ “መፍትሔው ፍቺ ነው” (ጌታቸው ኃይሌ)

ጌታቸው ኃይሌ

ስለ ኢትዮጵያ ለማወቅ ፈልጎ መጻሕፍት የሚያገላብጥ ባይተዋር መጀመሪያ የሚታየው የሀገሪቷ ጥንታዊነትና ውበቷ፥
የነዋሪዎቿ መልከ መልካምነትና በብዙ ጎሳዎችና ነገዶች መኖሪያነቷ ሲሆን፥ እነዚህ መልካካም ኢትዮጵያውያን በፖለቲካው
ረገድ ዕድለ ቢሶች መሆናቸው ነው። የፖለቲካ ለውጥ ለማምጣት፥ በተለይ በኛ ዘመን፥ ከፍ ያለ እንቅስቃሴ ተካሂዷል፤ ብዙ
ሕይወትም አልፏል። ግን እንቅስቃሴውን መርተው መንግሥት ለመገልበጥ የቻሉ ሁሉ፥ “ካስወገድነው አገዛዝ የኛ አገዛዝ
ይሻልሃል፤ እነ እገሌን አደኽይተን አነ እገሌን አናበለጽጋለን፤ በረዢም ዘመን ትግል ካስወገድነው እስር-ቤት መሰል አገዛዝ
የኛ እስር-ቤት መሰል አገዛዝ ይሻላል” የሚሉ እንጂ ሕዝቡን ከአገዛዝ ነፃ የሚያወጡ አልሆኑም። እንዲያውም ያቋቋሙት
አገዛዝ “ከድጡ ወደ ማጡ”” የሚባል አገዛዝ ነው። አይፈረድባቸውም፤ እነሱ የሚያውቁት ምን እንደሚፈልጉ እንጂ ሕዝቡ
ምን እንደሚፈልጉ አያውቁም። ከየት አግኝተው ይወቁት? የሚያውቁት አያገባቸው ገብተው መፈትፈትና መጕረስ ነው።
“ኢትዮጵያን ከአገዛዝ ነፃ አውጥቶ ዴሞክራሲን አጎናጸፋት” የሚል የታሪክ ክብር የሚቀዳጅ ጀግና ማን ይሆን? ለጊዜው
የሚታየኝ እንከን የለሽ ንጹሕ ምርጫ የሚፈቅድ ባለሥልጣን ወይም የምርጫውን ሕግ የሚያስከብር የፖሊስ አዛዥ ነው።
የወንጀል ወንጀል
እነዚህ ለውጥ እናመጣለን ባዮች መንግሥት ለመገልበጥ የሕዝብን ድጋፍ ያገኙበት ዘዴ የወንጀል ወንጀል ነው፤ “ብሶትህን
እንድናስወግድልህ ደግፈን” ሲሉት፥ እውነትም ከረኀብ፥ ከበሽታ፥ ከድንቁርና፥ ከሁሉም ይልቅ ከብዝበዛና ከጭቆና
የሚያላቅቁት መስሎት ነበር። የፈለጉትን ድጋፍ አግኝተው በለስ ሲቀናቸው፥ ቃላቸውን አምኖ የደገፋቸውን ሕዝብ፥
“መስሎሃል” ብለው ቀለዱበት፤ ልክ የሞተ አባቱን አመጣልሃለሁ እያለ እጓለ ማውታውን ብዙ ዓመት እንደገዛው እንደዚያ
ተንኮለኛ ሰው ተሳለቁበት። እንኳን ብሶቱን ሊያስወግዱለት፥ እንዲያውም አዲስ ብሶት ጨመሩለት--ራሳቸውን አበልጽገው
እሱን አስራቡት፤ አገር አልባ እያደረጉትም ነው።
በስሟና በዝናዋ እንኳን እንዳንኖር ስሟን ጥላሸት ለቀለቁት፤ ዝናዋንም እያጠፉብን ነው። ከጥንት ጀምሮ አብረን የኖርነውን
ኢትዮጵያውያንን ትናንት በመጥፎ አጋጣሚ የተገናኘንና የተዋወቅን ሰዎች ሲያደጉርን ይታያሉ። ሀገር የሚፈጠረው፥ ሕዝብ
የሚገነባው እንዴት እንደሆነ ካላነበበ ሕዝብ ድጋፍ ለማግኘት ብሶቱ ያልሆነውን ነገር ሳይቀር ብሶቱ እያደረጉ፥ መራራውን
በማር እያድቦለቦሉ ያጎርሱታል። ምን ማለቴ እንደሆነ፥ ከዚህ በታች ያለው ጥቅስ ያስረዳል፤
ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. በስመ አንድነት፥ ወይም በወረራ የተመሠረተ የባርነትና የግዛት አንድነት የሕዝብ አንድነት
ይሁን ብሎ ለመከራና ለጭቆና አሳልፎ አይሰጥም። ማንኛውም ብሔርና ብሔረሰብ የራሱን ዕድል በራሱ
በመወሰን ነፃ መንግሥት መሥርቶ በአስፈለገው መንገድ እንዲጓዝ ይበልጥ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ሲታገልለት የቆየ
ዲሞክራሲያዊ መንገድ ከመቸውም ጊዜ በላይ ፍቱን መፍትሔ መሆኑን አሥምሮበታል። በኤርትራና
በኢትዮጵያ ለ30 ዓመታት ሲካሄድ የቆየውን ጦርነት በተመለከተ ማንም ወሳኝ ሳይሆን የኤርትራ ቅኝ ግዛት
ጥያቄ በሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ እልባት አግኝቶ ኤርትራውያን ከኢትዮጵያ ቅኚ አገዛዝ
ቀምበር ተላቅቀው ነፃ አገራቸውን እንዲመሠርቱ ሁሉ ኢትዮጵያዊ አምኖበት መቀበል አለበት።1
በዚህ ጥቅስ ውስጥ ስለተነሣ ብቻ፥ ይህ ድርሰት የኤርትራን አሳዛኝ ታሪክ እንደገና አይተርክም። ሰሚ ጆሮ፥ አስተዋይ
አእምሮ ያለው ቢያገኝ ከሚያስፈልገው በላይ ተተችቷል። ኤርትራን የመሸጥ ወንጀላቸውን ካመነው የትግሬ ወያኔ ከነበረው
ከአቶ ገብሩ አሥራት መጽሐፍ አንድ አንቀጽ ብቻ ጠቅሼ ልለፈው፤
ህወሐት/ኢሕአዴግ ኤርትራን በቅኝ ግዛትነት ዐውቆ ነጻነት ይገባታል የሚል አቋም ሲደርስም ይሁን
ለኤርትራ ነጻነት ዕውቅናን ሲሰጥ የኢትዮጵያ ጥቅም እንዴት መስተናገድ እንዳለበት የሚያመለክት ስትራቴጂ
አስቀድሞ መንደፍ ነበረበት። በማንኛውም መንገድ አንድ አገር የነበረ ግዛት ለሁለት ሲከፈል [መከፈልን
መቀበል ምን አመጣው?] ይህ መከፋፈል ሊያስከትል የሚችለው እንድምታ በሚገባ መጤን ነበረበት። . . .
የኤርትራ እንደ አገር መፈጠር ግን በኢትዮጵያ ላይ መሠረታዊ ችግር አስከትሏል። የኤርትራ አገር መሆን
የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ ጥቅምና ደኅንነት አደጋ ላይ የጣለው በአስራ ዘጠነኛው ክፍለ ዘመን ቅኝ ገዥዎች
የነበሩ ኢጣልያ፣ እንግሊዝና ፈረንሳይ የቀየሱትን ኢትዮጵያን ከባሕር በር ባለቤትነት የማግለል ስትራቴጂ ተግባራዊ በማድረጉ ነው። ህወሐት/ኢሕአዴግ ኢትዮጵያን ወደዚህ ቅኝ ገዥዎች ወደወጠኑት ወጥመድ
የከተታት ኢትዮጵያን የሚጠቅመውን የውል ክፍል ወደጎን በመተውና ኤርትራን የሚጠቅመውን የውል
ክፍል በመቀበሉ ነው።2
አቶ አሥራት ይኸን ሲጽፍ ወያኔዎች ያመፁት ከመነሻቸው እስከ መጨረሻቸው ኢትዮጵያን ሊጎዱ እንጂ ጥቅሟን ሊጠብቁ
እንዳልነበረ እያወቀ ነው። ዓሰብን መልቀቅ ጭንቅላት ያለው ሰው ሲያስበው ያለ በቂ ምክንያት ከመሆኑም በላይ፥
ኢትዮጵያን ይጎዳል እንጂ ለኤርትራ የአንድ ሳንቲም ጥቅም አያስገኝላትም። ኢነዚህ ሰዎች ኢትዮጵያን ለመጕዳት
ለመነሣታቸው ከዚህ የበለጠ ማስረጃ ያለ አይመስለኝም።
የፍች መፍትሔነት
ይህን ድርሰት ለመጻፍ ያነሣሣኝ እንኳን የፍችውን መፍትሔነት አብረን እንድንመረምረው መፈለጌ ነው። ምሳሌውን የሀገርን
መፍረስ የሚደግፉ ብዙዎች ለመከራከሪያ ሲጠቀሙበት ሰምቻለሁ። ላሁኑ ድርሰቴ ግን መነሻ የማደርገው የኢሕአዴግ
ካድሬ የነበረው አቶ ኤርምያስ ለገሰ የጻፈውን ነው። አቶ ኤርምያስ “ቄሴ” የሚለው የኢሕአዴግ ደጋፊ ስለ ሀገር መገነጣጠል
ስለሚያውጀው ስለ አንቀጽ 39 ጥቅም የሚያሳይ ምሳሌ አምጥቶ እንዳሳመነው እንዲህ ሲል ይጽፋል፤
አባትና እናትህ ተፈቃቅደው ነው የተጋቡት። አንተም ነገ ሚስት ስታገባ የፈቀድካት[ን] እና የወደድካትን
መሆኑ አይቀርም[፤] እሷም እንደ[ዚያ]ው [ታደርጋለች]። በጋራ መኖር ጀምራችሁ በፍጹም የማያግባባችሁ
(የማ[ያስታርቅ]) ነገር ቢፈጠር እና ከፍተኛ ጉዳት እያስከተለ ቢሄድ ምን ታደርጋላችሁ? . . . ወይ መ[ፋ]ታት
አ[ለዚ]ያም ዘላለም እየተጨቃጨቁ መኖር [ነው]። የኢህአዴግ የህዝቦች የራስን [እ]ድል በራስ የመወሰን
እስከ መለያየት አቋም ምንጩ ይሄ ነው። የህዝቦች[ን] መብት ሳይሸራረፍ [የ]ማክበር ቁልፍ የዲሞክራሲ
ጥያቄ በው። የኢፌዲሪ ህገ-መንግስት ይህን የኢህአዴግ መርሆ እንዳለ በመቀበል የኢትዮጵያ ብሄር
ብሄረሰቦች የራስን እድል በራስ የመወሰን መብት ያለአንዳች ገደብ እስከ መገንጠል እንዲሆን አደረገ።
ከሚስትህ ጋር እስከተፈቃቀዳችሁ ድረስ አብራችሁ ለመኖር እንደምትወስኑት ኢትዮዮጵያዊነትም
በመፈቃቀድ ላይ መመስረት ይኖርበታል።3
እስቲ ይኸን ምሳሌ አብረን እንመርምረው፤ ባልና ሚስቱ የተጋቡት በሰማኒያ ነው ወይስ በሃይማኖት ሕግ? በሰማንያ ከሆን
በተጋቡበት ዕለት ሌሊቱን አብረው አድረው ሲነጋጋ መፋታት ይችላሉ። የእሱን ጋብቻ ከትችት እናሶጣው። ምክንያቱም፥
እስካሁን ድረስ ጎሳዎቹንም ሆነ ነገዶቹን “አብረው የኖሩት ከአንድ መቶ ዓመት በታች ነው” ብሎ ያማቸው ጸሐፊ አላየሁም።
በሃይማኖት ከሆነ፥ በየትኛው ሃይማኖት ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል? በክርስቲያን ሃይማኖት ከሆነ፥ ትእዛዙ የሚለው፥
“እግዚአብሔር ያፃመራቸውን ማንም ሰው ሊያለያያቸው አይችልም” ነው። በዚህ ዓይን የሚታይ ከሆነ፥ ምሳሌነቱ እስከ
መጨረሻው አብሮ ለመኖር ተስማሚ ነው። የተሰጠው ለፍቺ ከሆነ ግን፥ መረቻ ምሳሌ በራስ ላይ ማምጣት ይሆናል።
ሌላ ነጥብ፤ የሁለቱም ምሳሌዎች ምንጫቸው ኢሕአዴግ ሆኖ ሳለ፥ በሁለቱ ጥቅሶች አንጻር ሲታዩ መሠረታዊ ልዩነት
አለባቸው። እመጀመሪያው ጥቅስ ውስጥ ጋብቻው የተፈጸመው በአንድ ጎረምሳና በተፈነገለች የጭን ባሪያ ነው።
እሁለተኛው ውስጥ ግን በኋላ ሰይጣን ገብቶ አጣላቸው እንጂ፥ ጋብቻውን ሲጀምሩስ በፍቅድ፥ በፍቅር ነበር።
ሁለቱንም ምሳሌዎች ቀረብ ብለን ብንመረምራቸው፥ ጎሳዎች እንዴት የአንድ ኢትዮጵያ ሕዝብ እንደሆኑና የአብሮ መኖር
ችግራቸው ምን እንደሆነ ለማሳየት አቅም አንሷቸው እናገኛቸዋለን። ያሉን ሰነዳዊ ማስረጃዎች ጥንታዊት ኢትዮጵያ
ከተመሠረተች በኋላ የሠራችውን ታሪክና ጠላት ያደረሰባትን ችግር የሚያሳዩ ናቸው። ከዚያ በፊት የሆነውን (ማለት እንዴት
እንደተመሠረተች) የምናውቀውስ በሰነዳዊ ማስረጃ ሳይሆን ተቀባይነት ባለው ግምት ነው። ስለዚህ፥ በግድም ሆነ በፍቅር
ለመመሥረቷ የተሰጡት እነዚ ሁለት ምሳሌዎች ከንቱዎች ናቸው።
ጎሳዎች እርግጥ መንግሥት ሲጀመር እንደተጋቡ ባልና ሚስቶች አብረው መኖራቸው ቢገመት ስሕተት ላይሆን ይችላል፤ ግን
ዛሬ የምናወራው አብሮ መኖርን ስለጀመሩቱ ስለጥንቶቹ ሳይሆን፥ እነሱ ስላፈሩን እንደ አቶ “ኤርምያስ ለገሰ ዋቅጂራ ሀዋዝ”
ስላለነው ስለኛ ስለልጅ ልጆቻቸው ነው። ተጋቡ የተባሉት ዛሬ የሉም፤ ስለኛ ስለልጅ ልጆቻቸው እናውራ። ልጆች ደግሞ
ራሳቸውን እንጂ፥ ወላጆቻቸውን ወክለው የማያውቁትን የወላጆቻቸውን ጋብቻ አይፋቱላቸውም። የጥንቶቹ ከየትኛውም ጎሳ
ቢመጡ፥ የኛ የተዳቀልነው የልጆቻቸው ጎሳ ኢትዮጵያዊነት ሆኗል። ካልታወቀ ወደ ሀዋዝ፥ ከሀዋዝ ወደ ዋቅጂራ፥ ከዋቅጂራ ወደ ለገስ፥ ከዚያ ወደኤርምያስ ወዘተ. የሚወስድ ረጂም የታሪክ ዘመን በመጓዝ ርቀናቸዋል። ታዲያ፥ ይኼ
የጋብቻና የፍቺ ምሳሌ አለ ለተባለው ችግር እንዴት አጥጋቢ ማብራሪያ ሊሆን ይችላል?

የሥልጣን ግዴታ
እኛ የምናውቀው፥ ሰዎች ሥልጣን የሚይዙት የሀገርን አንድነት ለመጠበቅ፥ ዳር ድምበር ለማስከበር እንጂ ወያኔ
እንደሚያደርገው ሀገርን እንደሚጣል አሮጌ ወረቀት መቀዳደድ በዓለም ታሪክ ሲታይ የመጀመሪያው ነው። ኢጣልያ እንኳን
ሳትቀር ኤርትራንና ሁለቱን የሱማሌ ሀገሮች ጅውቲንም ጨምራ ከቀረው ኢትዮጵያ ጋር አዋሕዳ የጥንቷን ኢትዮጵያ መልሳ
አቋቁማ ልትገዛ በተግባር ላይ እያዋለችው ያለ አቅድ ነበራት። የትግሬ ወያኔዎች ግን ሌሎች ገዢዎች ያለደረጉትን “በወረራ
የተመሠረተ የባርነትና የግዛት” መንግሥት ማቋቋም ብቻ ሳይሆን፥ “አልገዛም ካልክ ተበታተን” አሉት። መሳሳቴን ለማሳየት
የዩጎዝላቪያን፥ የሶቬት ኅብረት፥ የቸኮዝሎቫኪያን ታሪክ ሊያመጣ ይችላል። ግን የነዚህ ሀገሮችና የኢትዮጵያ ታሪክ የተለያየ
ነው። እነሱ ዱሮውንም ጥምረቶች እንጂ እንደ ኢትዮጵያ አንድ ሀገር እንዳልነበሩ ስማቸው ሳይቀር ይመሰክራል።
“ብሔርና ብሔረሰብ”
ለመሆኑ፥ መንግሥት እንዲያቋቁሙ ወያኔ የሚገፋፋቸውና የሚያስፈራራቸው “ብሔርና ብሔረሰብ” ስንት ናቸው?
አንዱ ከሌላው “ብሔርና ብሔረሰብ” የሚለየውና አብሮ ለመኖር የማያስችለው ልዩነት ምንድን ነው?
ከአያት ከቅድመ አያት ጀምሮ በአንድ ሃይማኖት፥ በአንድ ታሪክ፥ በአንድ ባህል የኖሩ ሰዎች በቋንቋ መለያየት
ብቻውን አንድ “ብሔረ ሰብ” ወይም የአንድ ሀገር ሰው አለመሆንን ያስከትላል?
የተለያየ ቋንቋ የሚናገሩ፥ ግን በአንድ አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች “የተለያዩ ብሔረሰቦች” ይባላሉ?
በሸዋ፥ በወሎ፥ በጎንደር፥ በጎጃም የሚኖሩ ሰዎች፥ በተለያየ ብሔር እየኖሩ አንድ ብሔረ ሰብ ይባላሉ? (ብሔር ማለት አገር
ማላት ነው ብለናል።) ከመረብ በላይና በታች ያለውን ሕዝብ አንድ ብሔር እንዳይሆን የከለከለው ምንድን ነው? ወንዙ?
የተለያየ ሃይማኖት የሚከተሉ ሰዎች አንድ ብሔር ውስጥ እየኖሩ፥ የተለያዩ ብሔረ ሰቦች ይባላሉ ወይስ አንድ ብሔረ ሰብ?
እውነት ትግርኛ ተናጋሪው ሕዝብ ራሱን አማርኛ ከሚናገረው ሕዝብ ጋር አብሮ የማያኖር ልዩነት እንዳለ ያምናል ወይ?
ከተንኮል በቀር ጎሳን ከፖለቲካ ውስጥ ምን አገባው? ጎሳንና ሀገርን ምን አገናኛቸው፤ ምንስ አጋጫቸው? የግል መታወቂያን
(ሃይማኖትን፥ ቋንቋን፥ ጾታን፥ ቀለምን፥ ቁመትን) እና ሀገርን ምን አገናኛቸው?
ውስጥ ዐዋቂው የኢሕአዴግ ካድሬ የነበረው አቶ ኤርምያስ የሚነግረን ወያኔዎቹን የገጠማቸው ዋና ችግር ብዙው ሕዝብ
ጎሳን ከፖለቲካ ማስገባትንና የሕገ መንግሥታቸውን አንቀጽ 39 (“የፈለገ የኢትዮጵያን አንዱን ክፍል ይዞ መሄድ ይችላል”
የሚለውን አንቀጽ) አንቀበልም ማለቱ ነው። ለምንድነው አብሮ ለመኖር የሚጥረውን ሕዝብ መገነጣተልን እንደ ሃይማኖት
ካልተቀበልክ ብለው የሚያስጨንቁት? ለመግዛት ከሆነ፥ አንድ አድርገን እንግዛህ ቢሉት የበለጠ ይታዘዝላቸዋል።
የወያኔዎች ዓመፅ
አቶ አሥራትና አቶ ኤርምያስ ከውጪ ሆነን የምናውቀውን ከውስጥ ሆነው የነገሩንን ስንመረምረው፥ ወያኔዎቹ ያመፁት
በኢትዮጵያ ጨቋኝ ገዢዎች ላይ ሳይሆን በኢትዮጵያ፥ በኢትዮጵያውያን እና በኢትዮጵያዊነት ላይ ነው። አማርኛ ተናጋሪውን
በጠላትነት የፈረጁትና ጠላትነቱን አማርኛ በማይናገረው አእምሮ ስር በማስያዝ የሚጥሩት ኢትዮጵያዊነትን አጠንክሮ ስለያዘ
ነው። ጉልበት ላለው እንዲህ ያለውን ክፋት እንኳን ችግረኛውን ያልተቸገረውንም ለማሳመን ቀላል ነው። ለምሳሌ፥
ነጋዴዎች አስፈልጎን የማያውቀውን ዕቃ ሲያሳዩንና ያስፈልጋችኋል ሲሉን ሲያስፈልገን እናገኘዋለን። ወያኔዎች ይህን
ለማድረግ የሚያስፈልገው አቅም ነበራቸው፤ አሁንም አላቸው። በነጋ በጠባ ቍጥር (ስሙን በኮድ እየጠሩ) ሆድ ለባሰው
ሰው፥ “አማራ ጠላትህ ነው” ካሉት፥ ብዙ ሳይቆይ አማራን ጠላቱ ያደርገዋል። በእዚያ ላይ አንጎሉ እነሱ የሚነግሩትን
በሚያስተያይበት ትምህርት ያልተገሠሠ ድንግል መሆኑን አንርሳ። “ዴሞክራሲ ማለት ጠላት ያልነውን ሁሉ ሰብአዊ መብቱን
መግፈፍ ነው” ሲሉት ስለዴሞክራሲ ያላነበበ ሰው አሜን ብሎ እንደሚቀበል አቶ ገብሩ አሥራት እንዲህ ሲል ነግሮናል፤
ቻርተሩ ከጸደቀ ከአንድ ወር በኋላ በተጻፈውና በምሥጢር ለከፍተኛ ካድሬዎች በተሰራጨ ሰነድ . . . 
“የኢሕአዴግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ዓላማ ዴሞክራሲያዊ መብቶች ለዜጎች ሁሉ ያለምንም ልዩነት በእኩል
ማረጋገጥ አለብን የሚል መነሻ የለውም።” አብዮታዊ ዴሞክራሲ የአንድን አገር ዜጎች እንደጠላትና
እንደወዳጅ ሲከፋፍል፣ ዓይነተኛው ዴሞክራሲ ደግሞ ዜጎች ሁሉ እኩል ናቸው ብሎ ያምናል። አብዮታዊ
ዴሞክራሲ ጨቋኝ መደቦች መብትና ነጻነት ሊነፈጉ ይገባል [ይላል።]
4
ወያኔዎች ሳያስቡት የሠሩት ዋናው ሀገራዊ ጥቅም ከግብር አበሮቻቸው ብዙዎቹን በእስራትም ሆነ በማስፈራራት
ማባረራቸው ነው። እነዚህ ተበራሪዎች በእነሱ ሲደርስባቸው ነቅተዋል፤ የሚጽፉትና የሚናገሩትም ከውስጥ ዐዋቂነት
ተነሥተው ስለሆነ ወያኔዎች የኢትዮጵያ ጠላቶች እንደሆኑ የሚጠራጠረውን ከጥርጣሬ ያወጡት ይሆናል።
የጥላቻ ፖለቲካ መሠረቱ 
ብዙዎች አማራን የሚጠሉት እውነት የወያኔዎቹን ፕሮፓጋንዳ አምነው ብቻ ነው ወይስ ሌላ ተጨማሪ ምክንያት አላቸው? 
መጀመሪያ የጥላቻ በሽታ የተጠናወታቸው ስንት እንደሆኑ ማወቅ ያስፈልጋል። ለማንኛውም፥
(አንደኛ) የአንድ ጎሳ ሰው አንዱን የሌላ ጎሳ ሰው ቢበድል፥ ተበዳዩ በሁሉም የጎሳ አባላት ላይ እንደሚያቄም የታወቀ ነው፤
አዲስ ነገር አይደለም፤ “ያ አማራ፥ ያ ጉራጌ፥ ያ፥ ያ፥ የሠራኝን ብነግርህ . . .” የሚለው አነጋገር የተለመደ ነው። ይኼ
በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የዓለምን ሕዝብ በማሠቃየት ላይ ያለ መድኃኒት ያልተገኘለት ወረስሽኝ በሽታ ነው።
(ሁለተኛ) የአማራና የክርስቲያን መንግሥት በሚባለውና በሙስሊሞች መካከል የተነሣው የዓሥራ ስድስተኛው ምእት
ዓመት ግጭት ያስተጋባው ድምፅ አሁንም ይሰማል። የዚያን ጊዜው የሙስሊሙ ጂሃድ የበላይነቱን ለመያዝ ስለነበረ፥ ከተሳካ
በኋላ መጨናገፉ በብዙዎች ሙስሊሞች ዘንድ ቁጭት ጥሏል። ቢሳካ ኖሮ ክርስቲያኖቹ ዘንድ ቁጭት ይኖር ነበር። 
(ሦስተኛ) ኦሮሞዎች ማህል ኢትዮጵያን ለመውረስ ሲገሠግሡ፥ በሰላም አልነበረም፤ ታሪክ የማይረሳው እልቂት ደርሷል።
እልቂቱ የደረሰው በኦሮሞችና በወላስማ ሙስሊሞች ጭምር ቢሆንም፥ ኦሮሞዎቹ በምሬት ሲያስታውሱ የሚሰሙት ሲዳማ
ከሚሉት የአማራ ሕዝብ ጋር የተፈጸመውን መተላለቅ ብቻ ነው። ከወረሩና ከወረሱ በኋላ፥ እንደሌላው ሕዝብ የአንድ
መንግሥት ዜጋ ለማድረግ የተደረገው ጥረት በአንዳንዶች ዘንድ አብሮ የመኖር በሌሎቹ ዘንድ የተሸናፊነት ስሜት ፈጥሯል።
(አራተኛ) የመንግሥቱ ቋንቋ አማርኛ መሆኑ ሌላ ቋንቋ በሚናገሩ ዜጎች አእምሮ የአማራ የባህል የበላይነት ስሜት
አስነሥቷል። ስሜቱ ጥላቻንና ቅናትን ያመጣል። የበላይ አይወደድም። ግን ብዙ ጊዜ እንደተገለጸው፥ አማርኛ ተናጋሪው
ሁሉ አማራ ተባለ እንጂ፥ በመነሾው ሁሉም በዘር አማራ አይደለም። አማራ ከሚባለው ውስጥ አብዛኛው የወላጆቹን ቋንቋ
እየተወ አማርኛን የራሱ ቋንቋ ያደረገ ሕዝብ ነው፡ ግን ታሪኩ እንዲህ መሆኑን ልብ አንለውም፤ ወይም ልብ ማለቱ ጭብጥ
ስለሚያስለቅቅና ነገር ስለሚያባላሽ ልብ ማለቱን ሁሉ አይፈልገውም።
(አምስተኛ) መንግሥት በአገረ ገዢነት በየጠቅላይ ግዛቱ የሚልካቸው ሹማምንትና ጋሻ ዣግሬዎቻቸው (ነፍጠኞች
የሚባሉት) በሕዝባቸው ላይ ጌትነት እንዳሳዩ ይነገራል። ጌታ አይወደድም።
(ስድስተኛ) የዕውቀት ምንጫቸው ተማሪዎቹ የሚበትኑት በራሪ ወረቀት ለሆነ ሰዎች፥ የጥንቱ የገባርነት ሥርዓት አማሮችን
የበላይ ሌሎቹን የበታች የሚያደርግ ሥርዓት የሚመስላቸው አሉ። የበላይ አይወደድም። ግን የአምስተኛውና የስድስተኛው
እውነታ እንደ አራተኛው የሚገባውን ያህል አልታወቀም። አማሮች ተገዢዎችና ብዙዎቹም እንደሌሎቹ ገባሮች ነበሩ።
ተደጋግሞ እንደተነገረው፥ ነፍጠኛውም አማራ ብቻ አልነበረም። የመንግሥት ወታደር አማራ ብቻ ሆኖ አያውቅም።
(ሰባተኛ) የሕዝቡን ሕይወት ስናየው፥ ጥላቻ ያለው በአማራው ላይ ብቻ አይደለም፤ የኦሮሞ ጎሳዎች አሁንም እንደተጋደሉ
ነው። ኦሮሞዎች ጎሳዎች እንጂ አንድ ነገድ አይደሉም። አንድ ነገድ የማድረግን ሁኔታ የፈጠረላቸው አፄ ምኒልክ ሲሆኑ፥
የአማራ ጥላቻ የመገቧቸው የኦሮሞ ምሁራንና ደጋፊዎቻቸው ናቸው።
እንዲህ ከሆነ፥ ጥላቻ ግጭት መኖራቸው ግልጽ ቢሆንም፥ ወያኔዎች ፈጠሯቸው ከማለት ይልቅ፥ “ወያኔዎች አጋንነውና
በአማራው ላይ አጥብበው ለከፋፍለህ ግዛ ተጠቀሙባቸው፤ ጎሰኝነትን ከፖለቲካ አስገብተው መለያየት የማይፈልገውን አብዛኛውን ሕዝብ፥ ግንኙነቱን የጋብቻ አስመስለው፥ ‘በአንድነት እመኑ’ በማለት ፈንታ ‘በመፋታት እመኑ’ እያሉ
ያስጨንቁታል” ማለቱ ትክክል ይመስለኛል።

ስሜታዊና ኋላ ቀር ምክንያት 
ዓለም ለኢኮኖሚ እድገትና ለብልጽግና ሲሯሯጥ፥ እኛ ለመለያየትም ሆነ አብሮ ለመኖር የምንሰጠው ምክንያት ስሜታዊና
ኋላ ቀርነት ነው። “ኢትዮጵያ አንድ ሀገር፤ አንድ ሕዝብ” የሚለው ክፍለ ሕዝብ “ታሪክ የፈጠረች እናት ኢትዮጵያ
የማንነታችን መታወቂያ ስለሆነች ለዘላለም ትኑር” ባይ ሲሆን፥ ሁለተኛው ክፍለ ሕዝብ ደግሞ፥ “ኢትዮጵያ ታሪክ ስትፈጥር
አያቶቻችን ስላልተካፈሉ፥ ታሪክ የፈጠረች ኢትዮጵያን እናታችንም የማንነታችን መታወቂያም አናደርጋትም” ባይ ነው።
የያንዳንዱን ወገን ብዛት የሚያውቅ የለም፤ ግን እንበታተን የሚለው ይበዛ አይመስለኝም።
የሁለተኛው ክፍል አስተሳሰብ እርግጥ ይኼ ከሆነ፥ የፕሮፓጋንዳ ሰለባ ሆኗል። እንኳን ለዘመናት እብሮ የኖረ ሕዝብ
ለዓመታት የተጎራበተ እንኳን የጋራ ታሪክ ከመሥራት አያመልጥም። ከታሪክ ውስጥ አንዳንድ ድርጊቶችን ቀነጫጭቦ
የፖለቲካ ዓላማ ያለው ልብ ወለድ ታሪክ ካልተጻፈላቸው፥ እውነተኛው የኢትዮጵያ ታሪክ ይኸንን አቋም የያዙትን
አይደግፋቸውም። እንደ እውነቱ ከሆነ፥ እነዚህን ሰዎች ከታሪክ ጋር ያለቸውን ዝምድና የደበቀባቸው፥ (ሀ) ታሪኩ በግዕዝ
ቋንቋ መጻፉ፥ (ለ) ግዕዝ የሴማውያን ቋንቋ መሆኑ፥ (ሐ) ሴማውያን የሚባሉት ውስጥ እነሱ ለመካተታቸው፥ (መ) 
ጸሐፊዎቹ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ሊቃውንት (ካህናት) መሆናቸውና እነሱ ምንም ሚና አልተጫወትንም ማለታቸው ነው።
ታሪካችን በግዕዝ ቋንቋ መጻፉና ጸሐፊዎቹ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ሊቃውንት (ደብተሮች) መሆናቸው እውነት ነው። በግዕዝ
ቋንቋ የተጻፈው የዘመኑ የሀገሪቱ የዕውቀት ቋንቋ ግዕዝ ስለሆነ፥ ጸሐፊዎቹ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ሊቃውንት (ደብተሮች) 
መሆናቸው ደግሞ የሀገሪቱ ባለሥልጣኖች የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮች ስለነበሩ ነው። ይኼ ታዲያ ግዕዝንና
ጸሐፊዎቹን አጥፊዎች አያደርጋቸውም። ዐውቆ በማሳሳት የተጻፈ ነገር የለም። ጥላቻ የሚያቃጥላቸው ማስረጃ ጠቅሶ፥
“እዚህ ላይ የተሳሳተ ታሪክ ጽፈዋል” በማለት አይደለም። ሁለተኛም፥ ግዕዝ ዐውቆ በግዕዝ መጻፍና የኦርቶዶክስ ሃይማኖት
መከተል በዘር፥ በጎሳ፥ በነገድ ላይ የተመሠረተ አይደለም። ዐረቦች ሳይቀሩ የተሳተፉበት ሰፊ ሜዳ ነው።
ለመለያየትና አብሮ ለመኖር የምንሰጠው ምክንያት ስሜታዊና ኋላ ቀርነት ቢሆንም፥ “ኢትዮጵያ አንድና የአንድ ሕዝብ ሀገር
ናት” የሚለውን ሐሳብ የሚያራምደው ወገን እንዳጋጣሚ ለኢኮኖሚ እድገትና ለብልጽግና ከሚሯሯጠው ዓለም ጋር ይበልጥ
አብሮ ተራማጅ ነው። መነሻው መቀራረብና አብሮ መጓዝ ሰፊ ገበያ መዘርጋት ነው። ድምበርን ማጥበብ ገበያን ማጥበብ
ነው። ኤርትራ ብቸኝነቷን ባወጀች ማግስት ረግጣው የሄደችውን የራሷ የሚሆነውን ሀብት መቀላወጥና መስረቅ እንደ
ጀመረች ከላይ የጠቀስኩት የአቶ ገብሩ አሥራት መጽሐፍ ይነግረናል። የልመናውና የሌብነቱ ምንጭ “የራስን መጠን በራስ
እስከማሳጠር” የሚለው ፖለቲካ መሆኑ ግልጥ ነው። ኦሮሞዎች ወያኔ የዳረጋቸውን የኢትዮጵያ መሬት ይዘው ቢሄዱ፥
በኢኮኖሚው ረገድ ከኤርትራ የተሻለ ሁኔታ ይኖራቸዋል። አብሮ መኖር ከሚያመጣው ጥቅም ጋር ግን አይወዳደርም።
ስለሚቀጥለው ምርጫ የአቶ አሥራት ምክርና ማስጠንቀቂያ 
 
ተጠንቀቁ፤ “ኢሕአዴግ ተቃዋሚዎችን ለመድፈቅና ለማጥፋት ከሚጠቀምባቸው ስልቶች [ዋና ዋናዎቹን ልንገራችሁ።]
1ኛ/ በደኅንነቶች አማካይነት በእያንዳንዱ የተቃዋሚና አመራርና አባል ላይ ጥናት በማኪያሄድ ለመግዛትና ድርጅቱን
ለመከፋፈል መሞከር፣ [እንደ ባሪያ በመናኛ ብር የሚሸጡ ተወዳዳሪዎች አትሰይሙ ማለት ነው።]
2ኛ/ ተቃዋሚው ድርጅት በኅብረተሰቡ እንዲጠላና እንደጠላትነት እንዲታይ እንደየ ሁኔታውና እንደየ አካባቢው ነፍጠኛ
ነው፤ ትምክሕተኛ ነው፤ ጠባብ ነው፤ ጎሰኛ ነው፤ መላው አማራ ነው፤ ኢዴኅ [የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኅብረት] ነው፤
ኦነግ [የኦሮሞ ነፃነት ግምባር] ነው፤ የደርግ ቅሪት ነው፤ በማለት ማጥላላት፣
3ኛ/ ተቃዋሚዎችን በወንጀል እየከሰሱ ማጉላላት፣ ማሰቃየት፣ ማሰርና እንዲሰደዱ ማድረግ፣
4ኛ የተቃዋሚው ድርጅት አባላት ከማኅበረሰቡ እንዲገለል ለማድረግ ጎረቤቶቻቸውን ጭምር በመቀስቀስ ለቅሶ
እንዳይደረሱ፣ በሰርግና በተዝካር፣ በደቦና በሌላ የትብብር ሥራ እንዳይገኙ ማድረግ፣
5ኛ/ የመንግሥት ድጋፍ ማለትም የምግብ እርዳታ፣ [የባንክ] ብድር ማዳበሪያ፣ ወዘተ . . . እንዳያገኙ ማድረግ።” 

No comments:

Post a Comment