Monday, January 26, 2015

የነዳጅ ዋጋ ማሽቆልቆልና የዓለም ኢኮኖሚ – በርግጥ ለምን ነዳጅ ቀነሰ?

ከመኩሪያ መካሻ
ካለፈው ሰኔ ወር ጀምሮ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ባልተጠበቀ ፍጥነት እያሽቆለቆለ ይገኛል፡፡ በበርሜል 12ዐ ዶላር የነበረው በ6ዐ በመቶ ወርዶ በአሁኑ ጊዜ በበርሜል 4ዐ ዶላር ደርሷል፡፡ ባለፉት ተከታታይ አምስት ዓመታት ዋጋው ተረጋግቶ ሳይወርድ እንደቆየ ልብ ይሏል፡፡ ባለፈው ህዳር ወር በቪየና የነዳጅ አምራች የሆኑ ሀገሮች (opec) ዋጋው እንዳያሽቆለቁል ስምምነት ላይ ለመድረስ ሞክረው ነበር፡፡ ዳሩ ግን ውይይታቸው ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ እነዚህ የነዳጅ አምራች ሀገራት 4ዐ በመቶ የሚሆነውን የነዳጅ ምርት እንደሚቆጣጠሩ ይታወቃል፡፡ በዚህ የዋጋ መውረድ እጅጉን የተጎዱት ሀገሮች ከፍተኛ ነዳጅ አምራች የሆኑት ሩሲያ፣ናይጀሪያ፣ኢራንና ቬኑዙዌላ ናቸው፡፡ በተለይ ሩሲያ የሩብል ዋጋዋ ክፉኛ ተመትቶ ዝቅተኛ ምንዛሪ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ የነዳጅ ዋጋ መቀነሱ ምክንያት ምን ይሆን?
በመሠረቱ የነዳጅ ዘይት ዋጋ በአብዛኛው የሚወሰነው በአቅርቦትና ፍላጎት ሲሆን በሌላ አንፃር ደግሞ ወደፊት የሚከሰት ሁኔታን (expectation) የሚከወን ይሆናል፡፡ ለኃይል ምንጭነት የሚደረገው የፍላጎት መጠን በጥብቅ የተቆራኘው ከኢኮኖሚያዊ ሁኔታው ጋር እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የኃይል አቅርቦት በብዙ ሀገሮች በአየር ሁኔታ ተፅዕኖ ሥር ሊወድቅ ይችላል፡፡ በብርዳማ አካባቢዎች ለቤት ማሞቂያነት ኃይል ያስፈልጋል፤በሞቃታማ ሥፍራ ደግሞ ለቤት ማቀዝቀዣነት እንዲሁ ኃይል ማግኘት የግድ ይሆናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የጂኦፖለቲካ ሁኔታም ሌላው ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ነዳጅ አምራቾች ዋጋው እንዳሻቀበ ይቆያል ብለው ካሰቡ ኢንቬስት ማድረጋቸውን ይቀጥላሉ፡፡ ዋጋ ሲያሽቆለቁል ደግሞ ወደ ኢንቨስትመንት ድርቅ ሊያመራ ይችላል፡፡ የነዳጅ አምራች ሀገሮች (opec) ሁሌም ቢሆን ወደፊት የሚከሰት ሁኔታን በመፍጠር ይሠራሉ፡፡ ይህም ዋጋው እንዲያሻቅብ ለማድረግ አቅርቦት ላይ ይጫወታሉ፡፡ ከዓለማችን ከፍተኛ የነዳጅ አምራች የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ በቀን 1ዐ ሚልዮን በርሜል ነዳጅ ታመርታለች፡ ፡ ይህም ከዓለም ነዳጅ አምራች ሀገሮች ጋር ሲወዳደር አንድ ሦስተኛ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በነዳጅ ጉዳይ ላይ አራት መሠረታዊ ጉዳዮች ስዕሉን እያበላሹት ነው ማለት ይቻላል፡ ፡ የመጀመሪያው ጉዳይ ፍላጎት ነው፡፡ በዓለም ላይ የኢኮኖሚው ሁኔታ ደካማ በመሆኑ ፍላጎት ዝቅተኛ ሁኗል፡፡ ይህም ከነዳጅ ይልቅ ወደ ሌላ የኃይል ፍላጎት ማድላትን አምጥቷል፡፡ ሁለተኛው ምክንያት በሊቢያና በኢራቅ የሚታየው ትርምስ ነው፡፡ በቀን 4 ሚሊዮን በርሜል የሚያቀርቡ እነዚህ አገሮች የተጠበቀውን ያህል ማምረት አልተቻላቸውም፡፡
ሦስተኛው ምክንያት ግን አሜሪካ ከፍተኛዋ የነዳጅ ዘይት አምራች ሀገር መሆንዋ ነው፡፡ ምንም እንኳን አሜሪካ የነዳጅ ዘይት ኤክስፖርት ባታደርግም ወደ ሀገርዋ የምታስገባውን የነዳጅ አቅርቦት ቀንሳለች፡፡ ስለዚህ አቅርቦቱ እንዲጨምር አስተዋጽኦ አድርጋለች ማለት ነው፡፡
በመጨረሻም ሳዑዲ አረቢያና የገልፍ ሀገራት የገበያ ድርሻቸውን ዋጋ በማረጋጋት አሳልፈው መስጠትን አልፈለጉም፡፡ በተይ ሳዑዲዎች ዝቅተኛ የነዳጅ ዋጋ እንዳይጎዳቸው ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ አቅሙም አላቸው፡፡ በነገራችን ላይ9ዐዐ ቢሊዮን ዶላር በሪዘርቭ አስቀምጠዋል፡፡ በዋጋ ማሽቆልቆሉ ተጠቂ የሚሆኑ አካላት የተለያዩ ናቸው፡፡ የነዳጅ ዋጋ ሊያሻቅብ ይችላል በሚል በሚበደሩ ኩባንያዎችና በሰሜን ንፍቀ ክበብ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ነዳጅ የሚፈልጉት ይጎዳሉ፡፡ ከሁሉ በላይ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ውጋት የሚደርስባት ሩሲያ ናት፡፡ ምክንያቱም ሩሲያ ከከፍተኛ የነዳጅ ዋጋ ሽያጭ በምታገኘው የተለያዩ ማህበራዊ ፕሮግራሞችንና ኢንቨስትመንቶችን ታካሄድ ነበር፡፡ አሁን ግን ዋጋ በማሽቆልቆሉ ይህን ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ለማካሄድ ማጣሪያዋ አጥሯል፡፡ ኢራንም በተመሳሳይ መንገድ የሩሲያ ዕጣ ገጥሟታል፡፡ ለዚህም ነው ብዙ የፖለቲካ ተስፈኞች ሩሲያና ኢራን በነዳጅ ዋጋ ማሽቆልቆል የሚደርስባቸውን ኢኮኖሚያዊ ህመም ዓለማቀፉ ማህበረሰብ የሚያደርስባቸውን ጫና ይቀበላሉ ሲሉ የሚናገሩት፡፡ የፖለቲካ ጨለምተኞች ደግሞ እንደሚሉት እነዚህ ሀገራት ጥግ እንዲይዙ ከተደረጉ ወደ ብስጭትና ስጋት ይገባሉ ሲሉ ግምታቸውን ይሰጣሉ፡፡
ብዙዎቹ ነዳጅን በከፍተኛ ዋጋ እየገዙ ለሚያስገቡ ሀገራት የነዳጅ ማሽቆልቆሉ “እልል በቅምጤ” ነው የሆነላቸው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያም የዚሁ የዋጋ ማሽቆልቆል ተጠቃሚ እንደምትሆን ሳይታበል የተፈታ ነው፡፡ በተለይ የአውሮፖ ሀገሮች፣ሕንድ፣ጃፓንና ቱርክ ንፋስ አመጣሹን የነዳጅ ዋጋ መቀነስ እጅግ ይጠቀሙበታል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃም ጠቅላላ ምርቱ ዕድገት እንደሚያሳይ ኢኮኖሚስት መጽሔት ተንብዮአል፡ ፡ የነዳጅ ዋጋ መውረድ ዝቅተኛውን ኢንፍሌሽን ይበልጥ ያወርደዋል፡፡ የነዳጅ ገዢ የሆኑ ሀገራት ማዕከላዊ ባንኮች /ብሔራዊ ባንኮች/ ሶቬሪን ቦንዶችን /ልዕለ-ቦንዶችን/ በመግዛት ግሽበትን ይዋጉበታል፡፡
ከላይ እንደተጠቀሰው ከፍተኛ ነዳጅ አምራች የሆኑት ሩሲያ፣ ናይጀሪያ፣ ቬኑዚየላ፣ ኢራን ኢኮኖሚያዊ ቁስለት ያጋጥማቸዋል፡፡ ይህም የሚሆነው በጀታቸው የሚቀመረው በሚያገኙት የነዳጅ ሽያጭ በመሆኑ ነው፡፡ በሩሲያ የሩብል ምንዛሪ በጣም አሽቆልቁሏል፡፡ ሁኔታው በዚህ አያቆምም፣ ኢኮኖሚያዊ ድቀቱ ይቀጥላል፡ ፡ ናይጀሪያ የባንክ የትርፍ መጠንን በማሳደግ የገንዘቧን ዋጋ ለማረጋጋት ትሞክራለች፣ ቬኒዮዜላና ኢራንም ከፍተኛ የኢኮኖሚ ድርቅ ይመታቸዋል፡፡ በአጠቃላይ የነዳጅ ዋጋ መቀነስ ለኢኮኖሚው መረጋጋት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡
ይህ መልካም አጋጣሚ በመልካምነቱ የሚታየው የዋጋ ቅነሳው የሚቆይበት ጊዜ ከመራዘም ጋር ይያያዛል፡፡ ለወደፊቱ በዚህ የዋጋ ማሽቆልቆል ውስጥ የሚታዩ ሽኩቻዎች ይኖራሉ፡፡ ዋነኛው ሽኩቻ የሚታየው በነዳጅ ቆፋሪ ኩባንያዎችና ዋጋ እንዲያሻቅብ በሚፈልጉ የነዳጅ አምራች ሀገራት (opec) መሃል የሚከሰተው ግብግብ ነው፡፡ ሳዑዲዎች በአሁኑ ጊዜ የሚከተሉት ስልት ወደፊት የነዳጅ ዋጋ እንዳሽቆለቆለ እንዲቆይ ሊያደርግ ይችላል፡፡ ሳዑዲዎች ከ197ዐዎቹ የነዳጅ ሁኔታ ካገኙት ትምህርት በመነሳት ዋጋ እንዲወድቅ ይፈልጋሉ፡፡
የዋጋው መውደቅ ደግሞ ከፍተኛ ነዳጅ አምራች ሀገር የሆኑትን ከነዳጅ ንግዱ ሊያስወጣቸው ስለሚችል ለሳዑዲዎች ከፍተኛ ጥቅምን ያስገኛል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ደግሞ ለከፍተኛ ነዳጅ ኢምፓርተሮች ጠቃሚነቱ ጉልህ ነው፡፡ የኢኮኖሚ ጠበብት እንደሚሉት 1ዐ በመቶ በነዳጅ ዋጋ ላይ በቀነሰ ቁጥር ዐ.1 በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት ይገኛል ይላሉ፡፡

No comments:

Post a Comment