Sunday, January 17, 2016

የዶ/ር መረራ የቡዳ ፖለቲካ እና መቀበል ያቃተው መራራ እውነት – ግርማ ሠይፉ ማሩ

ዶክተር መረራ “የኢትዮጵያ የታሪክ  ፈተናዎች እና የሚጋጩ ሕልሞች” በሚል አዲስ መፅኃፍ አስነብቦናል፡፡ በአንድ ጋዜጣ ላይ የዶክተር መረራ ከዮኒቨርሲቲ መሰናበት ያመጣው አንድ በጎ ጎን መሆኑን አንብቤያሁ፡፡ እኔም በዚህ እስማማሀለሁ፡፡ ብዙ የሀገራችን ፖለቲካኞች ጋዜጠኛ መቅረፀ ድምፅ ይዞ በሚጠይቃቸው ጥያቄ መልስ ከመስጠት የዘለለ ብዕርና ወረቀት አገናኝተው የሚያምኑበትን የፖለቲካ መስመር እና በግላቸው ያላቸውን ምልከታ ማካፈል ይቸግራቸዋል፡፡ የዶክተር መረራ ከዚህ በፊትም በተመሳሳይ ለንባብ ያበቃው መፅኃፍ ጋር ይህን መፅኃፍ ሲጨመርበት ቢያንስ በፖለቲካ መስመሩ ላይ ግልፅ መረዳት እንዲኖረን ያደርጋል፡፡ ለዚህ ፅሁፍ መነሻ የሆነኝ ግን በዋነኝነት ዶክተር መረራ አውቆ የሚዘላቸው አንድነትን የሚመለከቱ ጉዳዮች ሲሆኑ እግረ መንገዴን ከመፅኃፉ የተረዳሁትን ለማካፈል ጭምር ነው፡፡
ዶክተር መረራ በእኔ መረዳት ዛሬም መኢሶን ነው፡፡ በተቻለው መጠን መኢሶን በመከላከል እና ዋናውን ጥፋት በደርግና ኢህአፓ ትከሻ ላይ ሲጭን ነው የሚታየው፡፡ መቀበል ያቃተው መራራው እውነት መኢሶን ከደርግ ጋር ተባብሮ የደርግን ጡንቻ ማፈርጠሙ ከዚያም ተከትሎ ለተፈጠረው ጥፋት ድርሻውን ማንሳት እንዳለበት በግልፅ ሊያሳየን አለመቻሉ ነው፡፡ ድርሻ መውሰድ ስል ጥፋትን አምኖ ይቅርታ መጠየቅ እና ለእርቅ ዝግጁ መሆን ማለቴ ነው፡፡ በእኔ የፖለቲካ እሳቤ ውስጥ ሂሳብ ማወራረድ የሚል የለም፡፡
ዶክተር መረራ አሁን ኢትዮጵያ የምንላትን ሀገር ቅርፅ ያሲያዙትን ምኒሊክን ጀግንነት በጥያቄ ምልክት ውስጥ በማስገባት እና ከሶማሊያ ጋር አብረው ሀገር ሲወጉ ነበር የሚባሉትን “ዋቆ ጉታን” ጀግና እያደረገ በአክራሪ ኦሮሞ ብሔርተኞች ድጋፍ የመሻት ፍላጎቱን በመፅሃፉ ውስጥ ታዝቢያለሁኝ፡፡ ዶክተር መረራ ወደ መሃል እንምጣ እያለ ጥግ ጥጉን የሚሄድ መሆኑን ማሳያም ጭምር ነው፡፡ እንደሚታወቀው የዶክተር መረራ አብረን እንስራ እስከ “ግንባር” ብቻ ነው፡፡
የዶክተር መረራ የቡዳ ፖለቲካ ብሂል በሁሉም ጉዳይ ችግሮችን ወደሌሎች ማላከክ ባለብን አባዜ ጥሩ ገላጭ ቢሆንም፤ የዚህ የቡዳ ፖለቲካ ሰለባ ዋነኛው ግን ዶክተር መረራ መሆኑ ብዙ ማሳያ ማቅረብ ይቻላል፡፡ በተለይ መድረክ የሚባለውን ስብስብ አንዴም እንኳን ለሚፈጠሩት ችግሮች ኃለፊነት የሚወሰድ አካል አድርጎ አያቀርበውም፡፡ ዶክተር መረራ በሚመራው ድርጅት ውስጥም ያለውን ችግር ለማየት እና ለማስተካከል አይፈልግም፡፡
የዶክተር መረራ “የኢትዮጵያ የታሪክ ፈተናዎች እና የሚጋጩ ሕልሞቸ” የሚለው መፅኃፍ ይህች ሀገር ከፈታና የምትወጣው እና ህልሞች ቅዠት ሳይሆኑ አውን የሚሆኑት “የኦሮሞ ልኢቃን” እና “የአማራ ልሂቃን” የያዙትን ፅንፍ ሲተዉ እና መሃል መንገድ ላይ ሲገናኙ እንደሆነ ይገልፃል፡፡ እኔ በፍፁም ያልገባኝ “የአማራ ልሂቅን” የሚባለው ፍረጃ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊ ብሄረተኝነት የሚያቀነቅኑት ለማለት ከሆነ ሌሎችም አማራ ያልሆኑ በዚህ ረድፍ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ ወይም ደግሞ አማራ ማለት ኦሮሞ ያልሆነ ሁሉ ማለት እንደሆነ በግልፅ ሊነግረን ይገባ ነበር፡፡ ወጣም ወረደ እኔ በመሪነት ሁሉ የተሳተፍኩበትን አንድነት ፓርቲን በአማራ ልሂቀን የሚመራ ተብሎ ተፈርጇል፡፡ ስለዚህ ይህ መሰረታዊ ስህተት ሀገራችን ከፈተና እንድትወጣ የታዘዘላት የዶክተር መረራ መድሃኒት እንደማይሰራ የሚያመላክት ነው፡፡
ዶክተር መረራ የቡዳ ፖለቲካው ሰለባ መሆኑን በደንብ የሚያሳየው “ለአንድነት ሆዴ መቁረጥ የጀመረው፤ በ2205 ክረምት የድጋፍ ማሰባሰቢያ ስብሰባዎችን በአሜሪካ ለማካሄድ ተሰማምተን ከሄድን በኋላ እነ ግርማ ሠይፉ ሙሉ በሙሉ ባልገባኝ ምክንያት የጋራ እንቅስቃሴ እንዳናደርግ ባደረጉ ጊዜ ነበር፡፡ በጊዜው ለአንድነት መሪ ለነበረው ለዶ/ር ነጋሶም ምሬቴን ገልጨ ነበር፡፡ ምሬቴ ለዶ/ር ነጋሶም የገባው ይመስለኛል፡፡ ለማረም ግን አልቻለም፡፡….”  የሚል ክስ በገፅ 147 ላይ አስፍሮዋል፡፡ ተመሳሳይ ክስ በሌለሁበት በመድረክ ስብሰባ ላይ ሰሜን ጠርቶ እንዳቀረበ ሰምቻለሁ፡፡
በመጀመሪያ ደረጃ የድጋፍ ማሰባሰቢያ ስብሰባዎችን በአሜሪካ ለማካሄድ ተሰማምተን የሚለው አውነት አይደለም፡፡ እኔም እርሱም በግላችን አሜሪካ እንደምንሄድ ሲታወቅ ከተቻለ በጋራ ስብሰባ ብናደርግ የሚል ሃሳብ አንሰተን ሙከራ እንድናደርግ በሚል “አዲስ ቪው ሆቴል” ተገናኝተን ተነጋግረናል፡፡ ሙከራ ደግሞ ሊሳካም ላይሳከም ይቸላል፡፡ ይህን ዶክተር ነጋሶ ለአንድነት ድጋፍ ሰጪዎች ገልፀውላቸዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ዶክተረ መረራ ዘወትር እንደሚያደርገው “የኦሮሞ ኮሚኒቲ” ለብቻው ሰብሰቦ ገንዘብ ያሰባሰብ ነበር፡፡ ይህ ገንዘብ ለመድረክ የሚገባ አይደለም፡፡ ከዚህ በሚተርፈው ጊዜ የአንድነት ድጋፍ ሰጪዎች ስብሰባ እንዲጠሩ ጥያቄ ቀረበላቸው፡፡ የአንድነት ድጋፍ ሲጪዎች በጣም በሰለጠነ ሁኔታ ስብሰባ አድርገው በቂ ዝግጅት ሳይደረግ ድንገት የዚህ ዓይነት ስብሰባ መጥራት እንደሚቸገሩ አስታወቁ፡፡ በወቅቱ ደግሞ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል አንድነት ለጀመረው ዘመቻ ድጋፍ እያሰባሰቡ ስለሆነ ተጨማሪ ሌላ ድጋፍ ማሰባሰቢያ ለማድረግ ጊዜ እንደሚወስድባቸው ምክንያታቸውን ገለፁ፡፡ ይህን ለዶክተር ነጋሶም፣ለዶክተር መረራም ተነግሯል፡፡ ዶክተር መረራ ግልፅ ሆኖ ያልገባው ምን እንደሆነ አልገባኝም፡፡ የኦሮሞ ኮሚኒቲን ሰብሰቦ ለድርጅቱ ገቢ እየሰበሰበ፣ የአንድነትን ለመድረክ አድርጉት የሚለውን ዝግጅት ያልተደረገበትን ጥያቄ አንቀበልም ማለት ለምን እንዳሰከፋው አላውቅም፡፡ በግሌ ለመድረክ ገቢ ለመሰብሰብ ዝግጁ መሆኔን በተደጋጋሚ ገልጨለት እያለሁ ግን ለምን ሊከሰኝ እንደፈለገ አላውቅም፡፡
ሌላው ዶክተር መረራ በመድረክ ውስጥ አነድነትን የአማራ ወኪል ለማድረግ የሚሰራውን ሸፍጥ (ኦፌኮ በኦሮሚያ፤ አረና በትግራይ፤ የፕ/ሮ በየነ ድርጅቶች በደቡብ) መታገል ሳይችል “አንድነት ከመድረክ ካልወጣሁ” ብሎዋል በሚል ይከሰናል፡፡ ይህን ሸፍጥ ግልፅ የሚያደርገው መድረክ በ2007 ምርጫ አንድም ዕጩ በአማራ ክልል ያለማቅረቡ ነው፡፡ እውነቱ አንድነት እንደ ፓርቲ ከመድረክ የመውጣት ጥያቄ አንስቶ አያውቅም፤ በግለሰብ ደረጃ የመውጠት ፍላጎት ያላቻው የሉም ማለት አይቻልም፡፡ አሁን ከመድረክ ጋር ለመስራት ሽር ጉድ የሚለው ሰማያዊ ፓርቲ መስራቾች ከአንድነት የወጡበት ምክንያቱ አንዱ የመድረክ ጉዳይ ነበር፡፡ አንድነት የነበረው ጥያቄ መድረክ የእውነት “ግንባር” ወይም “ውህድ” ፓርቲ ይሁን ነበር ጥያቄው፡፡ በግልፅ ዶክተር መረራ የውህደት ተቃዋሚ ሲሆን ሁሉም የመድረክ አባል ድርጅቶች አንድነት ላይ ያላቸው የጋራ ጥያቄ የገንዘብ ምንጫችን ይዋሃድ የሚል ነበር፡፡ በመጨረሻም አንድነት “በሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በጀመረው ህዝባዊ እንቅስቃሴ ከኢህአዴግ እኩል የተረበሹት የመድረክ አመራሮች አንድነትን ከመድረክ አግደው፣ እንደ ኢህአዴግ ይቅርታ ካልጠየቀ አይገባም ሲሉ የአንድነት አባላት ደግሞ መድረክ ሲታዘል ተንጠልጥሎ የቀረ ሰለሆነ ከጫንቃችን ይውረድ ብለው ወስነዋል፡፡ ይህ ደግሞ ተገቢ ውሳኔ ነበር፡፡
አንድነት ከመድረክ መልቀቅ ብዙም ሳይወራ አንድነት በሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ላይ በያዘው ግልፅ አቋም መነሻ በስርዓቱ እንዲፈርስ ሲወሰን ከመድረክ ባንወጣ አንድነት ሳይፈርስ እንደሚቆይ እንረዳለን፡፡ ውሳኔያቸን ግን አሁን መድረክ እና አባል ድርጅቶቹ ባሉበት አቋም በፓርቲ ሰም ከመኖር ለጥቂት ጊዜም ቢሆን ባሳየነው ቁርጠኝነት የበለጠ እንደሰታለን፡፡ አንድነት ከመድረክ ወጥቶም በግዛቸው ሸፈራው መሪነት ቢቀጥል መንግሰት ይህን አሳፋሪ እርምጃ አይወስድም ነበር፡፡ ምክንያቱም ባለበት የሚረግጥ ፓርቲ ማንም አይፈራውም፡፡ ግብ አስቀምጠን የምንሄድበትን አውቀን ስንሄድ ነው ፈተናው የመጣው፡፡ ዶክተር መረራ እንደፃፈው አንድነት የፈረሰው ከባለራዕይ ወጣቶች፣ ከሀረና፣ ከኦፌኮ፣ ወዘተ በመጡ አምስተኛ ረድፈኞች አይደለም፡፡ ከተለያየ ፓርቲ ወጥተው በተለይ ከብሄር ፓርቲ ለቀው አንድነትን የተቀላቀሉ ወጣቶች አንድነት ዶክተር መረራ እንደሚለው የአማራ ልሂቃን ሳይሆን የሁሉም ቤት መሆኑን በመረዳታቸው ነው፡፡ ይህን መራራ እውነት ደክተር መረራ መቀበል የግድ ነው፡፡ አንድነት የሁሉም ቤት መሆኑ ያስፈራው መንግሰት ያለምንም አፍረት አንድነትን ለማፍረስ የተነሳውም በተለይ በኦሮሚያ ስናደርገው የነበረው ያልተጠበቀ ንቅናቄ ጭምር ነው፡፡ አንድትን ለማፍረስ የተሰለፉት ሆዳሞች ደግሞ ከሁሉም ሰፈር የተሰበሰቡ ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ የድርጅት ስራችን ክፍተት መሆኑን እናምናለን፡፡
በመጨረሻ ዶክተር መረራ የአምቦ ወጣቶች እሰኪነግሩት ተሸፍኖበት የነበረው አውነት “የከብት ሌባን የሚጠብቀው ባለቤቱ ነው፤የኮሮጆ ሌባን የሚጠብቀው ህዝብ ነው፡፡” የሚለው ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ በ2007 ምርጫ እሳተፋለሁ ሲል በአደባባይ የተናገርነው “ምርጫ ቦርድን ቁጥር ደማሪ እናደርገዋለን” የሚል ነበር፡፡ አንድም ምርጫ ጣቢያ ላይ ድምፁን የሚጠብቅ ህዝብ ካለሰለፍን ብንሰረቅም አንጮህም ብለን ተነሰተን ነበር፡፡ አሁንም ዶክተር መረራ ዘግይቶም ቢሆን እንደተረዳው የኮሮጆ ሌባን ለመጠበቅ የሚቆም መረጫ በሌለበት ምርጫ ፌዝ ነው፡፡ ለመምረጥ የተመዘገበ፤ ለሚደግፈው ድምፅ የሚሰጥ፣ የሰጠውን ድምፅ በትክክል የሚቆጥር ህዝብ ሲኖር ምርጫ ወደዲሚክራሲ መሸጋገሪያ ይሆናል፡፡ ይህ እንዳይሆን የሚከለክል መንግሰት ደግሞ በሌላ መንገድ ወንበሩን ለመልቀቅ መረጧል ማለት ነው፡፡
ቸር ይግጠመን!!!

No comments:

Post a Comment